Sunday, 14 May 2023 09:40

ሳፋሪኮም የመጀመሪያውን የመኪና ሽልማት ለባለዕድለኛው አበረከተ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

•   አንድ ባጃጅና 2 ሞተርሳይክሎችንም ለአሸናፊዎች ሸልሟል

ሳፋሪኮም ከወር በፊት ከ1ሚሊዮን በላይ ደንበኞችን ተሸላሚ የሚያደርግ "ተረክ በጉርሻ" የተሰኘ አገር አቀፍ የሽልማት መርሃ ግብር በይፋ ማስጀመሩ የሚታወስ ሲሆን፤በዛሬው ዕለት የመጀመሪያዎቹን የከፍተኛ ሽልማቶች አሸናፊዎች ይፋ በማድረግ፣ የመኪና የባጃጅና የሞተር ሳይክሎች ሽልማቶችን አበርክቷል፡፡

 የዕጣው አሸናፊ ተሸላሚዎች  የአዲስ አበባውን  የመኪና አሸናፊ፣ የአዳማውን የባጃጅ አሸናፊ እንዲሁም የአፋርና የድሬዳዋውን የሞተርሳይክል  አሸናፊዎች  ጨምሮ ከመላው አገሪቱ በርካታ ስልኮችና ታብሌቶችን ያሸነፉ ደንበኞች እንደሚገኙበት ሳፋሪኮም አስታውቋል፡፡

ኩባንያው በዛሬው ዕለት ረፋድ ላይ አውቶብስ ተራ፣ ማማድ ህንጻ ላይ በሚገኘው  የሳፋሪኮም አከፋፋይ ሱቅ ባዘጋጀው አሸናፊዎችን ይፋ የማድረግ  ሥነሥርዓት ላይ ነው፣ ለባለዕድለኞች  ሽልማታቸውን ያበረከተው፡፡

ሳፋሪኮም ባዘጋጀው በዚህ "ተረክ በጉርሻ" የተሰኘ አገር አቀፍ የሽልማት መርሃግብር፣ የመጀመሪያውን የመኪና ሽልማት ያሸነፈው የአዲስ አበባው፣ የጉርድ ሾላ ነዋሪ፣ ሙባረክ ሱሩር መሆኑ ታውቋል፡፡

ሙባረክ እንዴት ሽልማቱን እንዳሸነፈ ተጠይቆ በሰጠው ምላሽ፤"የሳፋሪኮም መስመርን ለጥቂት ጊዜ ስጠቀምበት ቆየሁና እኔ ሌሎች ዘመዶችን ለመጠየቅ ወደ ገጠር ስሄድ እዚህ ላለ ዘመዴ ሰጠኹት፡፡ በ0700 700 700 ሲደወል ዘመዴ ነበር የመለሰው፤ከዚያም ሽልማቱን ማሸነፌን አስታወቀኝ፡፡ መኪናውን ማሸነፌን ስሰማ በጣም ነው ደስ ያለኝ፡፡ የዕጣ ሽልማት መጀመሩን አውቅ ነበር፤ነገር ግን መኪና አሸንፋለሁ የሚል ሃሳብ ወደ አዕምሮዬ መጥቶ አያውቅም፡፡ እጅግ አስደሳች ዕድል ነው፤ድንገተኛ! ሁሉም ሰው እንደኔ የማሸነፍ ዕድል እንዲያገኝ የሳፋሪኮም መስመርን እንዲጠቀም እመክራለሁ፡፡" ብሏል፡፡

የአዳማው ናኦሊ መሃመድ፣ ሁለተኛውን የባጃጅ ሽልማት ያሸነፈ ሲሆን፤ ሁለት ሞተርሳይክሎችን ደግሞ የድሬዳዋው አሸናፊ ታደሰ አሰፋና የአፋር ክልሉ ሙክታር ሞሃመድ አሸንፈዋል፡፡

ሁለተኛውን የደንበኞች የአሸናፊዎች ቡድን ለመሸለም በመብቃታቸው በስሜት መጥለቅለቃቸውን የገለጹት የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ሪጂናል የሽያጭ ማናጀር አቶ ቢኒያም ዮሐንስ፤ አገር አቀፉ የዕጣ ሽልማት መርሃ ግብር ተጨማሪ በርካታ ደንበኞቹን መሸለሙን እንደሚቀጥል አስታውቀዋል፡፡

የዛሬ ወር ገደማ የዕጣ ሽልማት መርሃግብሩ ይፋ ከተደረገ ወዲህ፣ ተጨማሪ 400ሺ ደንበኞች  ዕለታዊ የአየር ሰዓት ሽልማቶች ማሸነፋቸውንም ኩባንያው በመግለጫው አስታውቋል፡፡

ሳፋሪኮም በመጪዎቹ ሰባት ሳምንታት ለበርካታ ተጨማሪ ደንበኞቹ፤ ሁለት መኪኖችን፣ 5 ባጃጆችን፣በርካታ ስልኮችንና ታብሌቶችን እንዲሁም የአየር ሰዓቶችን እንደሚሸልምም አስታውቋል፡፡

የሽያጭ ሃላፊው አቶ ቢኒያም ዮሐንስ ባስተላለፉት መልዕክትም፤ "እንደ ሳፋሪኮም ደንበኛ አገልግሎታችንን ስትጠቀሙ በየዕለቱ ተጨማሪ እሴት ታገኛላችሁ፤ማንኛውም ሰው የ07 ኔትዎርኩን በመቀላቀልና የሳፋሪኮም መስመርን በየዕለቱ በመጠቀም የዕጣ ሽልማቶች የማሸነፍ  ዕድሉን ማሳደግ ይችላል" ብለዋል፡፡

Read 1873 times