Saturday, 13 May 2023 20:58

የሱዳን ተፋላሚዎች ሰላማዊ ሰዎችን ያለመጉዳት ስምምነት ተፈራረሙ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

 “አገሪቱ የህዝቡ እንጂ የሱዳን ሠራዊት አይደለችም” ፕሬዚዳንት ሙሴቪኒ


     የሱዳን መደበኛ ጦር ሰራዊትና የፈጥኖ ደራሽ ሃይሉ፣ በሰላማዊ ሰዎች ላይ ጉዳት ላለማድረስ የመጀመሪያውን ስምምነት በሳኡዲዋ የወደብ ከተማ ጂዳ መፈራረማቸውን የቻይናው CGTN የሳኡዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርን ጠቅሶ ዘግቧል፡፡
የሱዳን ሲቪሎችን ከጉዳት ለመጠበቅ ባለፈው ሐሙስ የተፈረመው የጂዳ የቃል ኪዳን ዲክላሬሽን ስምምነት የተመቻቸው፣ በሳኡዲ አረቢያና በአሜሪካ መንግስታት መሆኑ ታውቋል፡፡
የሱዳን ህዝብን ጥቅም ማስቀደምና ለሲቪሎች በማናቸውም ጊዜያት ጥበቃን እንዲሁም የሰብአዊ እርዳታ ነፃ እንቅስቃሴን ማረጋገጥን በመሳሰሉ ሰብአዊ መርሆዎች ላይ የሚያተኩረው ዲክላሬሽኑ፣ ለጊዜው ምንም አይነት የተኩስ ማቆምን ባያካትትም፤ሁለቱ ሃይሎች በተጨማሪ ውይይት ለአጭር ጊዜ የተኩስ ማቆም ስምምነት እንደሚሰሩ ተጠቁሟል፡፡ በተጨማሪ ውይይት ይደረስበታል ተብሎ የሚጠበቀው የአጭር ጊዜ የተኩስ አቁም ስምምነት፤ ለሳምንታት ተቋርጠው የቆዩትን የውሃና ኤሌክትሪክ የመሳሰሉ መሰረታዊ አገልግሎቶችን ለነዋሪዎች ሊመልስ ይችላል ተብሏል፡፡ለአራት ሳምንታት ያህል በዘለቀውና በሱዳን የጦር ሰራዊትና በፈጥኖ ደራሽ ሃይሉ መካከል ተባብሶ በቀጠለው የካርቱም ጦርነት፣ እስካሁን ቢያንስ 604 ሰዎች እንደ ሞቱና 5ሺ 127 ለጉዳት እንደተዳረጉ የዓለም ጤና ድርጅት ሰሞኑን አስታውቋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ የኡጋንዳው ፕሬዚዳንት ዮዌሪ ሙሴቪኒ፤ የሱዳን ተፋላሚ ሃይሎች የተኩስ ማቆም እንዲያደርጉ በድጋሚ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ የሱዳን ጄነራሎች በጦርነት የምትታመሰውን አገሪቷን እንደ ግል ጉዳያቸው ከመቁጠር እንዲቆጠቡም አስጠንቅቀዋል፡፡
“ህዝቡ እንደ አገር ባለቤትነቱ ሰላም አግኝቶ፣ መሪዎቹን እንዲመርጥ የተኩስ ማቆም ወሳኝ ነው” ያሉት የኡጋንዳው ፕሬዚዳንት፤ “አገሪቱ የሱዳን ጦር ሠራዊት አይደለችም፤ የህዝቡ እንጂ፡፡” ብለዋል-በትዊተር ገፃቸው ባስተላለፉት መልእክት፡፡
ፕሬዚዳንቱ ይህን መልእክታቸውን ባለፈው ረቡዕ ያስተላለፉት በሱዳን፣  የሽግግር ሉአላዊ ም/ቤት ሊቀመንበር ልዩ ልዑክ፣ ዳፋላህ አል-ሃጂ አሊን፣ በሳምንቱ መጀመሪያ በኢንቴቤ ቤተ መንግስት ተቀብለው ካነጋገሩ በኋላ መሆኑን የኬንያው ዴይሊ ኔሽን ጠቁሟል፡፡ ፕሬዚዳንት ዮዌሪ ሙሴቪኒ የሱዳን አመራር የማንነት ፖለቲካ ውስጥ እንዳይገባም አስጠንቅቀዋል፡፡  



Read 1072 times