Saturday, 13 May 2023 20:06

“ኮስፓ” የተሰኘ ድርጅት ህፃናትን ከጎዳና በማንሳት ሥራ ላይ መሰማራቱን አስታወቀ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

በአዲስ አበባና በሻሸመኔ ስራውን በይፋ ጀምሯል


       “ኮንሰርኒንግ ኦፍ ክርኤቲቭ ፕሮቫይዲንግ ኦሶሴሽን (ኮስፓ)” የተሰኘው ድርጅት ኑሯቸውን በጎዳና ላይ ያደረጉ ህፃናትን በማንሳትና በመንከባከብ እንዲሁም ወደ ትምህርት፣ ወደ ስራና ወደ ቤተሰብ መልሶ በመቀላቀል ስራ ላይ በይፋ መሰማራቱን አስታወቀ፡፡
ድርጅቱ ትላንት ግንቦት 4 ቀን 2015 ዓ.ም ረፋድ ላይ በጊዮን ሆቴል ዳሽን አዳራሽ ለሚዲያ ባለሙያዎች በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ነው ይህን ያስታወቀው፡፡
በበጎ አድራጎትና ማህበራት ኤጀንሲ በ2012 ዓ.ም በአገር በቀል በጎ አድራጎት ድርጀትነት እንደተመሰረተና በአገር ወዳድ ምሁራን እንደተቋቋመ የተነገረለት ድርጅቱ፤ ከዓለም ባንክና ከሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር ስምምነት ተፈራርሞ በአዲስ አበባና በሻሸመኔ ከተማ በይፋ ስራ መጀመሩም በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ተብራርቷል፡፡
እንደ ሀላፊዎቹ ገለፃ፤ ኮስፓ የጎዳና ልጆችን ከጎዳና ላይ አንስቶ የማገገሚያ ማዕከል በማስገባት የአካልና የስነልቦና ህክምና ድጋፍ እንዲያገኙ ከማድረግ በተጨማሪ፣ ልጆቹ ለጎዳና ህይወት የተዳረጉበትን ሥረ-መሰረት በመለየት፣ በልጆቹ ቤተሰብ ላይም ጥናትን መሰረት ያደረገ ስራ እንደሚሰራ ተገልጿል። በዚህም መሰረት ልጆቹ ከቤት የወጡት በኢኮኖሚ ችግር ነው በቤተሰብ ቀውስ፣ ወይስ በድርቅ፣ በጦርነትና ተያያዥ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ ችግሮች የሚውለውን በጥናት በመለየት፣ ቤተሰባቸው ከዚህ ችግር ወጥቶ በኮስፓ ማዕከል በአዕምሮም በአካልም አገግመው የሚመለሱ ልጆቻቸውን እንዲቀበሉ ብሎም ድጋሚ ወደ ጎዳና እንዳይለቀቁ እስከማድረግ ድረስ በመስራት ችግሩን ከምንጩ ለማድረቅ እንደሚሞከር ተብራርቷል።
ኮስፓ እ.ኤ.አ እስከ 2030 ዓ.ም ድረስ በሀገሪቱ አሉ ተብለው የሚገመቱ ከ150ሺህ በላይ የጎዳና ተዳዳሪዎችን በግማሽ ለመቀነስ እንደሚሰራ አቅዶ እየተንቀሳቀሰ ሲሆን፤ ተልዕኮውም በሂደት አገሪቱ ላይ የጎዳና ልጆች የማይታዩበትን ሁኔታ መፍጠር እንደሆነ ጠቅሶ ይህ እንዲሳካ ለዚህም ትልሙ ስኬት የየከተሞቹ አስተዳደሮች ማህበረሰቡና ሚዲያው በጋራ አብሮ በትብብር እንዲሰራ ጥሪ አቅርቧል።
 ኮስፓ በአሁኑ ሰዓት 20 የጎዳና ተዳዳሪ ልጆችን አንስቶ በሻሸመኔ ማዕከሉ እየተንከባከበ ሲሆን በተለያዩ ከተሞች ስራውን የማስፋት እቅድ እንዳለውም ሃላፊዎቹ ገልጸዋል። ህፃናት ወደ ጎዳና የሚወጡበትን ሁኔታ ለመቀነስም በተከታታይ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን  በትጋት እንደሚሰራ በመግለጫው ተብራርቷል።



Read 1056 times