Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Saturday, 29 September 2012 09:13

ከቴዲ አፍሮ ሠርግ ጀርባ፣ “ሌላ የሆነ ወግ!

Written by 
Rate this item
(4 votes)

ምንም ጣጣ ሣላበዛ፣ የወጌን ርዕሠ ጉዳይ ልንገራችሁ፤ ከትላንት በስቲያ ማለትም፣ በዕለተ ሀሙስ፣ መስከረም 17 ቀን 2005 ዓ.ም ስለተከበረው የመስቀል በዓል እንዳይመስላችሁ፤ በዚሁ ዕለት በሒልተን ሆቴል ስለተካሄደ የቴዲ ሠርግ ላወጋችሁ ነው፡፡ እናሣ ታዲያ፣ “ሠርግ የዘፋኝም ሆነ የንጉሥ ያው ሠርግ ነው፤ ባታወጋን ምን ሊቀርብን…” እንዳትሉኝማ - አደራ፡፡ እኔም ብሆን የታዋቂውን ዘፋኝ ሠርግ ከመነሻ እስከ መጨረሻ የመዘከር እቅድ የለኝም፡፡ ባይሆን፣ በሠርጉ ላይ በእቅድ ከተከናወኑ ጥቂቱን፣ ያለ እቅድ በሞቅታ ከተከናወኑት ደግሞ ጥቂቱን ላጫውታችሁ ከጅዬ ነው፤ እናም አያቴ “ሲውጥ ይሥቅ” የሚል አባባል ነበራት፤ ሀበሻን ለመግለፅ ይመሥለኛል፤ ካልበላ ያኮርፋል አይነት የጀርባ ፍካሬ ቢጤም ሊወጣለት ይችላል፡፡ ለመዋጥ ወይም በመዋጥ ለከት ካልተበጀ፣ ለመሣቅም በመሣቅም ያው ነው - ለከት ይጠፋል ማለቴ ነው፤ እስኪ ይሁን … ሠርጉን እንደ ገጠር ሙጌራ (ዳቦ) እያገለባበጥን፣ አንደዜ የፊለፊቱን፣ አንደዜ የጀርባውን፣ አንደዜ ገጠመኞቹን አሊያም ግጥመኞቹን እናውጋ፡፡

ከኋላው መጀመር አሠኘኝና ጀመርኩ፡፡ “ቴዲና ኤሚ” ከደርዘን ያለፉ ሚዜዎቻቸውን አስከትለው፣ ከክብር ወንበራቸው ተነሡ፤ የመሠናበቻ ሙዚቃ አዳራሹን እየናጠው ነው፡፡ ቴዲን ለመሠናበት አንዳንድ ፊታቸው ለኢትዮጵያዊው ምታተመስኮት (ኢቴቪ) አዲሥ ያልሆኑ፣ ሞንዳላ እንስቶች፣ በሱፍ ጢቅ ያሉ ጐልማሣና አዛውንቶች ወደ መድረኩ ቀረቡ፡፡ በተለይ ሙሽሮችን በምስል ለመቅረፅ፣ ዘመነኛ ሞባይላቸውን እንደ መሥቀል ችቦ ሽቅብ የወጡ እጆች አቤት መብዛታቸው!? “ሴኪዩሪቲ” የሚል የእንግሊዘኛ ጥሁፍ ሠፋፊ ደረታቸው ላይ የለበጡ፣ በደህናው ቀን ደንዳና ሠውነት ያበጁ ጠብደሎች “ማነው ወንድ ቴዲን እስከ ልዕልቱ የሚጨብጥ!” ብለው ቀውጢ ፈጠሩ፤ ሳይሞቅ፣ ሳይቀዘቅዝ እንደው ግርግር ተፈጠረ፡፡ ከአዳራሹ ወጥቶ እያለ አንድ አስጨፋሪ አንድን ጨፋሪ ወደ ግድግዳው አስጠግቶ በጥፊ ጋጋው! ወቾ ጉድ አልኩኝ፡፡

ለነገሩ እኔም፣ ነገር ወዳድ ሀበሻ ስለሆንኩ እንጂ፣ ከሠርጉ ሥነ ሥርአት እኮ ስንት የሚያምር፣ ስንት የሚገርም አጋጣሚ ነበር!? ኧዲያ! ከዕለቱ ዝግጅት “የሠቀለውን” ገጠመኝ ልንገራችሁ፤ አሁን ከምሽቱ፣ 4፡30 አካባቢ ነው፤ አንዲት እናት ወደ  መድረክ ወጡ፡፡ ፊታቸው በደሥታ ይፍለቀለቃል፤ ማይክ ተሠጣቸው፡፡ እጃቸው አልተንቀጠቀጠም - ድምፃቸውም፡፡ እኝህ እናት ድንቅ የመድረክ ንጉሥ ወልዶ ማሣደግ ብቻ ሣይሆን፣ በመድረክ ላይ መንገሥ ይችሉበታል ለካ! ወይ እቺ “ትገርም” ሀገር፡፡ እኝህ እንስት፣ ታዳሚው አመሥግነው በደሥታ ሢቃ በማይኮለታተፍ፣ ንፁሕ ልሣን ለሙሽሮቹ የመጀመሪያዋ ሥጦታ አቅራቢ መሆናቸውን በጥበብ ገለፁ፡፡ አልፎ አልፎ በቀለም ምጣኔያቸው መዛባት ገርደፍደፍ ከሚሉ ጥቂት ስንኞች በቀር፣ ከቀረበበት ጊዜና ከተከፈለበት ጥልቅ ሰዋዊ ፍቅር አንፃር ሲመዘን ጥበብዊነቱ የጐላ አንድ ተራኪ ግጥም አቀረቡ - የቴዲ አፍሮ እናት ወይዘሮ ጥላዬ፡፡

በዚህ ተራኪ ግጥም ታዲያ፣ የዚህን ጐበዝ የሕይወት ታሪክ በወፍ በረር አስቃኙን፤ በመጨረሻም፣ የዕለቱ ሥጦታቸው ይህ ያቀረቡት ግጥም መሆኑን በትሁት አንደበት አስረገጡ፤ የአብራካቸውን ክፋይ ታዋቂውን አርቲስት “ቴዎድሮስ” ብለው ሥም ለማውጣት፣ ብላቴናው ከያኒ ሲወለድ ከቤታቸው ግድግዳ ላይ፣ የታዋቂው ባለ ራዕይ መሪያችን የአፄ ቴዎድሮሥን ምሥል አይተው፣ እንደ አፄው ባለታሪክ እንዲሆንላቸው በእናትነታቸው ተመኝተው መሆኑን ሢናገሩ፣ እኛ “ኧረገኝ እንዴት ሸጋ ገጠመኝ ነውሣ!” አለማለት ይከብደናል - በዚህ አዳራሽ ውስጥ ተገኝተን፡፡

ታዋቂ ልጅዋን ድራ ሥጦታዋ ግጥም መሆኑን የገለፀች ሌላ የአለማችን እንሥት ትኖር ይሆን? ይሆናል፡፡ አለያ፣ ያለ በቂ ጥናት ከመሬት ተነሥቶ፣ “በሃገራችን በልጇ ሠርግ ግጥም ያቀረበች የመጀመሪያዋ እናት” የሚል ደፋር ገለፃ በማቅረብ ከአንዳንድ ማህበራዊ ሂሥ ተንታኞች ጋር መጋጨት አልፈልግም፤ ጥፌ፣ (በዕውቀቱ ስዩም “የመጀመሪያው” የማለት ልክፍት እንዳለብን የሚገልጽ ትችት መፃፉን ልብ ብትሉልኝስ)

በነገራችን ላይ የቴዲ እናት መልዕክት ተኮር በሆነ ተራኪ ግጥማቸው፣ ካነሷቸው ርዕሠ ጉዳዮች ውስጥ ቢያንስ ሁለቱን ላስታውሣቸው፡፡ ከአራት ሠዓት በኋላ ያውም ውስኪ በሚቀዳበት አዳራሽ ውስጥ፣ ሙሽሮቹም ሆነ ሚዜዎቹ፣ ታዳሚውም ሆነ ሙዚቀኛው በወጉ ላያደምጡት ይችላሉና ማስታወሤን ውደዱልኝ፤ 1ኛ. የሚወዱት ባለቤታቸውን የአርቲስት ካሣሁን የአብራክ ክፋይ ቴዎድሮስ ካሣሁንን ከአደራ ጋር ለታዋቂዋ ሞዴል ለወ/ሪት አምለሰት ማሥረከባቸውን 2ኛ. በቅርቡ ሙሽሮቹ የአብራካቸውን ክፋይ እንዲያሣዩዋቸውና አያት ለመሆን በጣም የጓጉ መሆናቸውን ነበር በጥበባዊ አጽንኦት ያሳሰቡት! ሥለዚህ ወዳጆቼ፣ እነ ቴዲ ወንድ ከወለዱ ክርሥትና የማነሣው እኔ እንድሆን ይፈቀድልኝ ብልሣ? መልካም ነው…

አዳራሹ መቼም በአንጋፋም፣ በጐልማሣም፣ በወጣትም ሙዚቀኞች ደምቆ ነበር ብሎ ማውጋት አይገባም፤ እንዲህ እንደሚሆን ይጠበቃላ፤ ኧረ! ቆይ ግን አራት ላዳ ታክሢዎች ተቀጣጥለው ቢሰለፉ የማይበልጧቸው ሽንጣም መኪኖች ሥማቸው ማን ነበር? ከምር የሙሽሮቹ መኪኖች ቀልብ ይስባሉ…! አንጋፋው ከያኒ አለማየሁ እሸቴም፣ የ42 ዓመት የትዳር ገጠመኙን አውስቶ ከሙዚቃው በፊት ያቀረባት የመግቢያ ምርቃት ልክ ነበረች! ሰው ኑሮውን ሢመሠክር እኮ ያምርበታል፤ ከራስ የሕይወት ልምድ ሥለሚቀዳ ይታመናል ወይም ያሣምናል፤ የአንጋፋው አርቲሥት ሙዚቃውም እንደ አብዛኞቹ አቅራቢዎች በጣም ማራኪ ነበር፡፡ ቢያንሥ ደግም፣ የአንጋፋው የመድረክ ሰው የፋንቱ ማንዶዬን ከሁለት ዘመን ያጣቀሰ ዳንሥ በፍቅር አስኮምኩሞናል፤ ሰዓቱ እኮ ታዲያ 5፡40 ነበር - ከምሽቱ፡፡

እኔ እምለው ግን፣ አንዳንድ ሀበሻ ልካችንን አናውቅምሣ!? መቼም በዚህ አዳራሽ ሙሽራዋን፣ ሚዜዎቿን ጨምሮ እንደ ሙሽራ መኪኖቹ ሽንጣም ሸንጣም ለግላጋ ውብ እንስት ማየት በፍፁም ብርቅ አልነበረም - በእውነት! አርቲስት ሸዋንዳኜ “የቀረብኝ በዚች ዓለም …” እያለ አዳራሹን ቀውጢ ሲያደርገው፣ የሙሽሪት ሚዜዎች አረንጓዴ ጐርፍ ሠርተው ሽንጣቸውን በውዝዋዜ ያሞናድላሉ፤ በተለይ አንደኛዋማ የጉድ እኮ ነው!... መቀመጫዋን የምትወዘውዘው! ታዲያላችሁ ከጥቂት ዓመታት በፊት በተለይ በምታተመስኮቱ (ኢቴቪ) ፊታቸውን ከሚያስጐበኙን ታዋቂ ሰዎች መካከል አንዷ ሴት፤ ባሏ፣ ወንድሟ ወይም “ወዳጇ” ይሁን በወጉ ካላወቅሁት ሸጋ ወጣት ጋር ጥግ ላይ ተቀምጣለች፤ ካጠገቧ ያለው ወጣት ከጐኗ ተቀምጦ አይኑ ብቻ ሣይሆን ሁለመናው ወገቧን ከምታሾረው ሚዜ ላይ አርፎ፣ ካጠገቡ ያለችውን ውብ ሴት እረስቷል፤ ለነገሩ በእኛ ሃገር የወጣትነት መለኪያን “የኢህአዴግ ወጣት ፎረም አባላት” ሥለበረዙብን እንጂ፣ ሰውዬው እንኳ ወጣት ነው ማለት ይከብዳል - ባይሆን ጐልማሣ እንጂ፡፡

እናላችሁ፣ ውቧ ሴት ወሬዋን እንዲያደምጣት ካጠገቧ ያለው ጐረምሣ ሣይሆን ጐልማሣ ፊቱን በእጇ ብትመልሠውም፣ እሱ ግን መች በጄ ቢላት! ነብሯ ሴት ታዲያ በአንድ እጇ ያለውን የወይን ብርጭቆ ጠበቅ አርጋ ይዛ ይመሥላል፣ ከመቀመጫው በርሮ ከተወዛዋዥዋ ሚዜ እንትን (ሆድ ውስጥ) ለመግባት የፈለገ የሚመሥለውን ስሜተ ሥሥ ጐልማሣ ጆሮ  ግንዱን በጥፊ ሥታቃጥለው፣ ለእነሱ እኔ ክው አልኩ፡፡ ሰውዬው ዘወር ብሎ በሀይል ይመላለሣል፤ ነብሯ እንስት ከወይኗ ተጐነጨች፡፡ ከጥጋቸው ያሉ ሰዎች በሞቅታ እየተሣሣቁ ሲገለማመጡ፣ ጐልማሣው ከወንበሩ ተነስቶ ወጣ፤ ነብሯ በኩራት ወይኗን መቀንደብ ቀጠለች - አይኗ ብቻ ሣይሆን ፊቷም ቀልቷል፡፡

እኔ ግን ተውሼ ያመጣኋትን ካሜራ እያሥተካከልኩ ነበር፤ ውዝዋዜውም ሆነ ጥፊው ይደገምልኝና ቢያንስ ፎቶ ላንሣው አይባል ነገር!? ኤዲያ! የሀበሻ ጣጣው ብዙ ነው እንጂ እቺን ነበር በስም ጠቅሼ ባደንቃትም ሆነ ባከፋት ደሥ ባለኝ! አንባቢዎቼም ትዝብቴን በወጉ ትጋሩኝ ነበር፤ ምን ይሆናል “በኢትዮጵያዊ ጨዋነትም” በሉት፣ በሃበሻ ፍርሃትና የሀሜት ልክፍት ከመናገር ተቆጥቤያለሁ!

ወዳጆቼ ከሠርጉ ጀርባ ያሉ አጋጣሚዎች ብዙ ናቸው፤ እኝህ ታዋቂ ሰዎች ለካ እንደኔ ቢጠው የአንበሣ ወተት ማጊ (የሀበሻ አረቄን “የአንበሳ ወተት” ሲል የሰማሁት ማን ነበር?)፣ መለኪያ ሢጨብጡ ለካ አሪፍ ተጫዋች ብቻ ሣይሆን አጫዋችም ናቸውሣ!?

በየትኛውም መለኪያ ግን፣ የሠርጉ ሥነ ሥርአት፣ ታዳሚው፣ በተለይ ቴዲ ሢዘፍን የፈጠረው አጠቃላይ ድባብ እጅግ በጣም አስደሣች እንደነበር አለመመሥከር ንፉግነት ነው - ቅልብጭ ያለ አሪፍ ዝግጅት፡፡ ከታዳሚው መካከልም፣ የአለማችን (የፕላኔታችን) ታላላቅ ሰዎች ነበሩበት - ለምሣሌ ሀይሌ ገብረስላሴ፡፡  በመጨረሻም፣ በኢትዮጵያዊ ወግ ልማድ ቴዲ እና ኤሚ፣ “ሠርጋችሁ የአብርሃም የሣራ ይሁን ውለዱ፤ ክበዱ” ብዬ ልመርቅ፡፡ እንዴ…የእኔስ እድሜ ለአቅመ መራቂነት ይበቃ ይሆን? የወጣትነት መለኪያውን እድሜ እስኪ ልፈልግ! “ወግ ነው ሲዳሩ ማልቀስ” ትለኝ ነበር አያቴ - እንዳሻት፡፡

 

 

Read 6754 times Last modified on Saturday, 29 September 2012 09:17