Saturday, 06 November 2021 00:00

በአማራ ክልል በህወኃት ወረራ ምክንያት 6 ሚሊዮን ዜጎች ለረሃብ አደጋ ተጋልጠዋል

Written by 
Rate this item
(2 votes)

 ከ1 ሚሊዮን በላይ ተፈናቅለዋል
                                  
                 በአማራ ክልል በሚደረገው ጦርነት ምክንያት ከ6 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ለረሃብ አደጋ መጋለጡን የአማራ ክልል አደጋ መከላከል ምግብ ዋስትናና ልዩ ድጋፍ የሚሹ አካባቢዎች ማስተባበሪያ ኮሚሽን አስታወቀ።
በህውኃት ወራሪ ሃይል ጦርነት በተሳተፈባቸውና በወረራ በተያዙ የክልሉ የረሃብ አደጋ ማንዣበቡን ነው የክልሉ አደጋ መከላከል ኮሚሽን መረጃ ያመለከተው።
በተለይም አሁንም ጦርነት እየተካሄደ ባለበት የዋግህምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዝቋላና  ጋዝጊብሳ ወረዳዎች ብቻ በምግብ፣ በመጠጥ ውሃና መድኃኒት  እጥረት፣ 13 ሰዎች መሞታቸውን የኮሚሽኑ  መረጃ ይጠቁማል።
የህውኃት ወራሪ ሃይል በሰሜን ወሎ ዞን መቄት ወረዳን በያዘበት ወቅትም 90 ሰዎችና 13 ወላድ እናቶች በመድኃኒትና በሌሎች ግብአቶች እጥረት ህይወታቸው እንዳለፈ፤ ጦርነቱን በመሸሽ ከቤት ንብረቱ የሚፈናቀለው ሰው ቁጥርም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መሆኑን፤ በዚህም በአሁኑ ወቅት የተፈናቃዮች ቁጥር ከ1 ሚሊዮን መብለጡን ነው መረጃው ያመለከተው። አብዛኛው ተፈናቃይም በተደጋጋሚ መፈናቀል ያጋጠመው መሆኑን አንዳንዶችንም እስከ 4 ጊዜ ድረስ ለመፈናቀል መገደዳቸውን ኮሚሽኑ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጠው መግለጫ አመልክቷል።
የአማራ ክልል በወረራው ምክንያት በነዋሪዎች  ላይ የተጋረጠውን አደገና በ6 ሚሊዮን ዜጎች ላይ ረሃብ ማንዣበቡን በተመለከተ በኢትዮጵያ ለአሜሪካ ኤምባሲ፣ ለዓለም ህፃናት አድን ድርጅት፣ ለዓለም ምግብ ፕሮግራም፣ ለአሜሪካ ተራድኦ ድርጅት፣ ለተባበሩት  መንግስታት የሰብአዊ ድጋፍ ማስተባበሪያና ለአለማቀፍ ቀይመስቀል ማህበር በተደጋጋሚ ቢያመለክትም እስካሁን ምላሽ አለማግኘቱን አስታውቋል።

Read 9588 times