ኦክላ የተባለው ተቋም ሰሞኑን ይፋ ባደረገው አለማቀፍ የኢንተርኔት ፍጥነት ሁኔታ አመላካች ሪፖርት፣ ከአለማችን አገራት በሞባይል ኢንተርኔት የተባበሩት አረብ ኤሜሬቶች፣ በብሮድባንድ ኢንተርኔት ፍጥነት ደግሞ ሞናኮ 1ኛ ደረጃን መያዛቸውን ፒሲማግ ድረገጽ ዘግቧል፡፡
በብሮድባንድ ኢንተርኔት ፍጥነት ከአለማችን አገራት መካከል ከአንደኛ እስከ አምስተኛ ያለውን ደረጃ የያዙት አገራት ሞናኮ፣ ሲንጋፖር፣ ሆንግ ኮንግ፣ ታይላንድና ሮማኒያ ናቸው፡፡
ከአለማችን አገራት መካከል በሞባይል ኢንተርኔት ፍጥነት የተባበሩት አረብ ኤሜሬቶች፣ ደቡብ ኮርያ፣ ኳታር፣ ቻይና እና ቆጵሮስ እስከ አምስተኛ ያለውን ደረጃ የያዙ አገራት መሆናቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
ከአፍሪካ አገራት በኢንተርኔት ፍጥነት 1ኛ ደረጃን የያዘችው ማዳጋስካር ስትሆን፣ በአገሪቱ አማካይ የኢንተርኔት ፍጥነት 32.07 ሜጋ ባይት በሰከንድ እንደሚደርስም ተነግሯል፡፡
ኬፕ ቨርዲ በሰከንድ 27.53 ሜጋ ባይት፣ ሲሼልስ በሰከንድ 26.76 ሜጋ ባይት፣ ጋና በሰከንድ 23.98 ሜጋ ባይት፣ ደቡብ አፍሪካ በሰከንድ 23.17 ሜጋ ባይት ፍጥነት እስከ አምስተኛ ያለውን ደረጃ የያዙ የአፍሪካ አገራት መሆናቸውንም ዘገባው አመልክቷል።
Sunday, 19 September 2021 00:00
Published in
ከአለም ዙሪያ