Print this page
Saturday, 04 September 2021 13:25

መንግሥት ከአገር ውስጥና ከውጭ የተበደረው ውዝፍ የዕዳ መጠን 2.4 ትሪሊዮን ብር ደረሰ

Written by 
Rate this item
(0 votes)


            መንግሥት ከአገር ውስጥና ከውጭ አበዳሪ ምንጮቹ ላለፉት ዓመታት የተበደረው ውዝፍ የዕዳ መጠን 2.4 ትሪሊዮን ብር ደረሰ። የአገሪቱ አጠቃላይ የአገር ውስጥና የውጭ ውዝፍ ዕዳ እ.ኤ.አ. እስከ ጁን 30 ቀን 2021 ድረስ 2.4 ትሪሊዮን ብር ሆኖ መመዝገቡን ይፋ ያደረገው፣ የገንዘብ ሚኒስቴር ሰሞኑን ያወጣው የዕዳ መግለጫ ሰነድ ነው።
ብሔራዊ ባንክ ላለፈው አንድ ዓመት ባደረገው የብር ምንዛሪ ተመን ለውጥ ምክንያት የብር የመግዛት አቅም በከፍተኛ ደረጃ በመውረዱ፣ አጠቃላይ የአገሪቱ ውዝፍ ዕዳ በ221.5 ቢሊዮን ብር እንዲያሻቅብ ምክንያት እንደሆነም ሰነዱ ያመለክታል። አጠቃላይ የአገሪቱ የዕዳ መጠን በውጭ ምንዛሪ ሲሰላ 55.6 ቢሊዮን ዶላር እንደደረሰም ሰነዱ ያመለክታል።
ከአጠቃላይ ውዝፍ ዕዳ ውስጥ የአገር ውስጥ አጠቃላይ ውዝፍ ዕዳ መጠን 1.14 ትሪሊዮን ብር ሲሆን፣ የአገር ውስጥ የዕዳ መጠን ባለፈው ዓመት 918.9 ቢሊዮን ብር ነበር።
በተመሳሳይ ከውጭ የተበደረው አጠቃላይ ውዝፍ ዕዳ መጠን ወደ 1.29 ትሪሊዮን ብር ያሻቀበ ሲሆን፣ ባለፈው ዓመት መጨረሻ ላይ ተመዝግቦ የነበረው የውጭ የዕዳ መጠን 1.01 ትሪሊዮን ብር እንደነበር ሰነዱ ይገልጻል።
መንግሥት ከአጠቃላይ የውጭ ውዝፍ ዕዳውን ለማቅለል በዘንድሮው በጀት ዓመት መዝጊያ ድረስ 73.1 ቢሊዮን ብር ወይም 1.8 ቢሊዮን ዶላር ለውጭ አበዳሪዎቹ ከፍሏል። ይህም ባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ከከፈለው 64.03 ቢሊዮን ብር ከፍ ያለ ቢሆንም፣ በወቅቱ በነበረው የምንዛሪ ተመን መሠረት ግን ሁለት ቢሊዮን ዶላር በመሆኑ ባለፈው ዓመት የከፈለው የዕዳ መጠን ብልጫ አለው።
በሌላ በኩል መንግሥት ዘንድሮ 1.4 ቢሊዮን ዶላር በተጨማሪ ከዓለም ባንክ ተበድሯል። ነገር ግን በዚሁ ዓመት 1.8 ቢሊዮን ዶላር የዕዳ ክፍያ በማድረጉ ምክንያት የተጣጣው የብድር ገቢ፣ በዓመቱ መጨረሻ ዜሮ ወይም በዓመቱ ከተገኘው የውጭ ብድር ፍሰት በ432 ሚሊዮን ዶላር ብልጫ ያለው ገንዘብ ለዕዳ ክፍያ ውሏል።
የዛሬ አምስት ዓመት ማለትም እ.ኤ.አ. በ2016/17 የነበረው የአገሪቱ አጠቃላይ የውጭ የብድር ዕዳ መጠን 23.3 ቢሊዮን ዶላር፣ ወይም በወቅቱ የብር ምንዛሪ ተመን 539.5 ቢሊዮን ብር እንደነበር መረጃው ያመለክታል።
ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ የውጭ የዕዳ መጠኑ ከ23.3 ቢሊዮን ዶላር ወደ 29.5 ቢሊዮን ዶላር ከፍ ብሏል፡፡ ይሁን እንጂ በሰኔ ወር 2013 ዓ.ም. በነበረው የብር ምንዛሪ ተመን ሲሰላ ግን 1.29 ትሪሊዮን ብር እንደሆነ መረጃው ያስረዳል።
በተመሳሳይ የዛሬ አምስት ዓመት የነበረው አጠቃላይ የአገር ውስጥ የዕዳ መጠን 522.8 ቢሊዮን ብር የነበረ ሲሆን፣ በሰኔ ወር በ2013 ዓ.ም. ላይ የዕዳ መጠኑ ከእጥፍ በላይ በመጨመር 1.14 ትሪሊዮን ብር ደርሷል።
የዛሬ አምስት ዓመት የአገሪቱ አጠቃላይ የአገር ውስጥና የውጭ ዕዳ መጠን 1.06 ትሪሊዮን ብር የነበረ ሲሆን፣ በአምስት ዓመታት ውስጥ ወደ 2.4 ትሪሊዮን ብር አሻቅቧል።
ከአጠቃላይ የዕዳ መጠን ውስጥ 1.29 ትሪሊዮን ብር የሚሆነው የዕዳ መጠን በዶላር ተመንዝሮ ለውጭ አበዳሪዎች የሚመለስ በመሆኑ፣ የአገሪቱ የውጭ ምንዛሪ ግኝትን ማሻሻል ከተቻለ አሳሳቢ እንደማይሆን ባለሙያዎች ያስረዳሉ።
(ሪፖርተር)


Read 985 times
Administrator

Latest from Administrator