Saturday, 06 March 2021 13:34

ኦነግ ጠቅላላ ጉባኤ አድርጎ በምርጫው ለመሳተፍ አልሟል

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(3 votes)

 ኦፌኮ ራሱን ከምርጫው ማግለሉን አረጋግጧል

             የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ከዘንድሮ አገራዊ  ምርጫ ሙሉ ለሙሉ መውጣቱን ያረጋገጠ ሲሆን በእነ አራርሶ ቢቂላ የሚመራው ኦነግ በበኩሉ፤ በቅርቡ ጠቅላላ ጉባኤ አድርጎ በምርጫው የመሳተፍ ፍላጎትና ዝግጁነት እንዳለው ለአዲስ አድማስ አስታውቋል።
ኦነግ ምናልባት በቀጣይ ሳምንት ውስጥ ጠቅላላ ጉባኤ አድርጎ የድርጅቱን ህልውና ካስጠበቀ በኋላ፣ የምርጫ ቦርድ ትብብርና በጎ ፈቃደኝነት ከተገኘ፣ እጩዎች አቅርቦ በምርጫው ለመሳተፍ ዝግጁ መሆኑን የፓርቲው ቃል አቀባይ አቶ ቀጄላ መርዳሳ ገልጸዋል።
በአመራር ቀውስ ምክንያት እስካሁን ለምርጫው እጩዎች ማቅረብ እንዳልቻለ የሚገልጸው በእነ አቶ አራርሶ የሚመራው ኦነግ፤ የአመራር ቀውሱን መፍቻው መንገድ ጠቅላላ ጉባኤ ስለሆነ ጉባኤውን ለማካሄድ እየተንቀሳቀሰ መሆኑንና በቅርቡ ጉባኤውን አድርጎ ወደ ምርጫው እንደሚመለስ አስታውቋል፡፡
ምርጫ ቦርድ ለመጨረሻ ጊዜ ያራዘመው የእጩዎች ምዝገባ ከትናንት በስቲያ የካቲት 25 ቀን 2013 ዓ.ም ያበቃ ቢሆንም በአመራር ቀውስ ውስጥ ለቆየውና ችግሩን ለመፍታት ጥረት እያደረገ ለሚገኘው ኦነግ፣ በልዩ ሁኔታ ጊዜ ተራዝሞለት  እጩዎች ለማቅረብ ይፈቀድለት ዘንድ ለቦርዱ ጥያቄ ማቅረቡን አቶ ቀጀላ ገልጸዋል፡፡
ለጥያቄው እስካሁን ቁርጥ ያለ ምላሽ ከቦርዱ ያላገኘ ቢሆንም ፣ጉዳዩ በጥቂት ቀናት ውስጥ ይታያል የሚል እምነት እንዳላቸው የገለጹት አቶ ቀጄላ፤ ኦነግ በእርግጠኝነት በምርጫ መሳተፍ አለመሳተፉን የሚያረጋግጠው የምርጫ ቦርድ ተባባሪነት ነው ብለዋል። ቦርዱ ጊዜ ሰጥቶን እጩ እንድናቀርብ ከፈቀደልን እናስመዘግባለን ያሉት አቶ ቀጄላ፤ የፓርቲው ሊቀ መንበር አቶ ዳውድ ኢብሳ እስካሁን ድረስ ተቀራርቦ በመነጋገር ችግሩን ለመፍታት ፍላጎት እንዳላሳዩም ጠቁመዋል፡፡
በሌላ በኩል፤ ቀደም ሲል በምርጫው እርስ በእርስ ላለመፎካከር ከኦነግ ጋር ከስምምነት ላይ ደርሶ የነበረው የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ፤ በምርጫው እንደማይሳተፍ ሰሞኑን በሰጠው መግለጫ  አረጋግጧል።
በኦሮሚያ ጽ/ቤቶች እንደተዘጉበት፣ ወሳኝ አመራሮችን ጨምሮ በርካታ አባላቱ እንደታሰሩበት ሲገልጽ የቆየው ኦፌኮ፤ የፖለቲካ ምህዳሩ በእስርና ወከባ በጠበበት ሁኔታ ለምርጫ ውድድር መቅረብ አልችልም ሲል አስታውቋል።
ኦፌኮ እስከ ረቡዕ ዕለት አንድም እጩ አለማስመዝገቡን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከምርጫው በፊት የታሰሩ ፖለቲከኞች ሁሉ ተለቀው፣ የብሔራዊ መግባባትና እርቀ ሰላም ውይይት መካሄድ እንዳለበትም ፓርቲው በመግለጫው አስገንዝቧል።


Read 12021 times