Saturday, 26 December 2020 12:14

አዲሱ የኮሮና ቫይረስ ዝርያ አለምን ለአዲስ ስጋት ዳርጓታል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

  •    ከ40 በላይ አገራት ከብሪታኒያ የሚደረጉ በረራዎችን አግደዋል
       በኮሮና ቫይረስ ሳቢያ በቀውስ ማዕበል ስትናጥ አንድ አመት ያህል ከተጓዘች በኋላ እንደምንም ከማዕበሉ ልትወጣበት በምትችለው የክትባት ግኝት በተስፋ ቀና

ማለት የጀመረችው አለማችን፣ አሁን ደግሞ ሌላ አዲስና ከቀድሞው የከፋ የኮሮና ቫይረስ ስርጭት ስጋት ተደቅኖባት በድንጋጤ ክው ብላለች፡፡
ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ ከወደ ብሪታኒያ የተሰማው ዜና፣አስደንጋጭና አለምን ወደባሰ ስጋት የከተተ ነበር፡፡ ለንደንን ጨምሮ በአንዳንድ አካባቢዎች ከነባሩ
ቫይረስ በበለጠ ሁኔታ በፍጥነት የሚስፋፋ አዲስ የኮሮና ቫይረስ ዝርያመገኘቱ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ ቫይረሱ ድንበር ተሻግሮ በተቀረው አለምም ሌላ
የወረርሽኝ ማዕበል ይፈጥራል የሚል ስጋት ማየሉን መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል፡፡
ጀርመን፣አየርላንድ፣ፈረንሳይ፣ጣሊያን፣ኔዘርላንድናቤልጂየምን ጨምሮ ጉዳዩ ያሳሰባቸው አገራት ወደ ብሪታኒያየሚያደርጉትን የአየርበረራ ለማቋረጥና አዳዲስ
የጉዞ ገደቦችን ለመጣል ደግመው ማሰብ አላስፈለጋቸውም፡፡ጉዳዩ አሳሳቢ ሆኖ በቀጠለባቸው ያለፉት ቀናት ሁሉም የአውሮፓ ህብረት አባል አገራት በሚባል
ደረጃ የጉዞ ገደቦችን ቢጥሉም፣ የህብረቱ ኮሚሽን ግን አገራቱ በብሪታኒያ ላይ የጣሉትን የጉዞ እገዳ እንዲያነሱና ወሳኝ ጉዞዎችን እንዲያስጀምሩ ጥሪ አስተላልፏል፡፡
ህንድ፣ ኢራንና ካናዳን ጨምሮ ከበፊቱ ቫይረስ ጋር ሲነጻጸር ከፍተኛ ስርጭት እንዳለው እንጂ ገዳይነቱ ምን ያህል የከፋ እንደሆነ አሁንም ገና ያልተረጋገጠው አዲሱ
ቫይረስ ያሰጋቸው ከ40 በላይ የሚሆኑ የአለማችን አገራት ከብሪታኒያ ወደግዛታቸው የሚደረጉ የአውሮፕላን በረራዎችን ማገዳቸውን የዘገበው ቢቢሲ፣ አዲሱ
ቫይረስ ዴንማርክ ውስጥ መታየቱን ተከትሎ ስዊድን ወደ ዴንማርክ የሚደረግ ጉዞን ማገዷንም አስነብቧል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ቦሪስ ጆንሰን ባለፈው ቅዳሜ በሰጡት መግለጫ፤ አዲሱ ቫይረስ ከቀድሞው ጋር ሲነጻጸር የመዛመትና የስርጭት ፍጥነቱ በ70 በመቶ ያህል
እንደሚጨምር መናገራቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ አዲሱ ቫይረስ ራሱን የሚያባዛበት መንገድ ከቀድሞው የተለየ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ  ለቁጥጥር ያስቸግር
ይሆናል የሚል ስጋት ማጫሩንና በቀጣይም ራሱን እየለወጠ ከመተንፈሻ አካል ውጭ ያሉ ሴሎችንም ሊያጠቃ የሚችልበት እድል መኖሩንም አክሎ ገልጧል፡፡
የአለምጤናድርጅት ቫይረሱ በጊዜ ሂደት ዝርያውን ለውጦ በአዲስ መልኩ መከሰቱ የሚጠበቅ መሆኑን በመጥቀስ፣ የብሪታኒያው ቫይረስ ከቁጥጥር ውጭ
አለመውጣቱን ቢያስታውቅም፣ ቫይረሱ በዴንማርክ፣ አውስትራሊያ፣ ኔዘርላንድና ጣሊያን ውስጥ መገኘቱንና ወደሌሎች አገራት ሳይዛመት አይቀርም የሚል
ጥርጣሬን ማጫሩንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
አዲሱ የብሪታኒያ ኮሮና ቫይረስ ዝርያ አለምን ማስጨነቅ ከጀመረ ከቀናት በኋላ ደግሞ፣ ከዚህም የተለየ ሌላ አዲስ የኮሮና ቫይረስ ዝርያ በደቡብ አፍሪካ መገኘቱንና
አገራት በደቡብ አፍሪካ ተጓዦች ላይ እገዳ መጣል መጀመራቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
የተለያዩ አገራት ለነባሩ የኮሮና ቫይረስ ሊሰጧቸው ያሰቧቸው ክትባቶች አዲሱን ቫይረስ በመከላከል ረገድ ሙሉ ለሙሉ ባይሆንም ውጤታማ ናቸው መባሉን
አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ በሌላ በኩል፤ኮሮና ቫይረስ ከመላው አለም አህጉራት ወረርሽኙ ድርሽ ሳይልበት ወደቆየው አንታርክቲካ ከሰሞኑ መግባቱንና
በአህጉሩ በሚገኘው ቤርናርዶ ኦ ሂጀን የተሰኘ የቺሊ ባህር ሃይል የምርምር ማዕከል ወታደሮችን ጨምሮ 36 ያህል የቫይረሱ ተጠቂዎች መገኘታቸውንም ዘገባው
አመልክቷል፡፡ ቫይረሱ ወደ አህጉሪቱ የገባው በቺሊየባህርሃይልመርከብ ተሳፍረው ወደ ምርምር ማዕከሉ ከገቡ መንገደኞች እንደሆነ መነገሩንም ዘገባው
ጠቁሟል፡፡



Read 12169 times