Print this page
Saturday, 10 October 2020 16:22

“ከሻይ ቤት ሀርሞኒካ እስከ ዳህላክ ባንድ”

Written by  (በስብሐት ገብረ እግዚአብሔር)
Rate this item
(0 votes)

    አንዳንድ ዘፈን አለ… ድንገት ደርሶ ድፍን አዲስ አበባን የሚያጥለቀልቅ። በየቡና ቤቱ፣ በየመጠጥ ቤቱ፣ በየሻይ ቤቱ በቴፕ ያሰሙታል። ካሴት ያላቸው ታክሲዎች ውስጥም ሲዘፈን ይሰማል። በመንገድ ጐረምሶች ዜማውን ያፏጩታል። ሴቶች ብቻቸውን ሆነው ልብስ እያጠቡ ወይም ወጥ እየሠሩ ለራሳቸው ይዘፍኑታል። ልጆች መንገድ ሲሄዱ ይዘፍኑታል… አልፎ አልፎ ባንድ እግራቸው ብቻ እየነጠሩ። ገና አፋቸውን የፈቱ ሕፃናትም ይኰላተፉበታል። የመንደር ሰካራሞችም ይንገዳገዱበታል። ባጭሩ፣ የከተማው ዘፈን እሱ ይሆናል።
ከጥቂት ወራት በፊት “ናኑ ናኑ ነይ፣ ናኑ ናኑ ነይ፣ ካንቻለኝ ጉዳይ!” እያለ ሲያስተጋባ ነበር የአዲስ አበባ ሕዝብ … ከሙሉቀን መለሰ ተቀብሎ ነበር የዘፈነው።
አንድ የሥራ ጓደኛዬ፤ እድሜዋ ሶስት ዓመት ተኩል የሆነ ልጅ አለችው። አንድ ቀን፣
“አባዬ! ያቺ’ ኮ ስሟ ናኑ ነው” አለችው፤ ወደ አንዲት ኰረዳ እያመለከተች።
“ኧረ?” ሲላት፣
“አዎን” አለች፤ “ብትፈልግ ትላንትና ‘ናኑ ናኑ ነይ፣ ካንቻለኝ ጉዳይ’ ስል ጊዜ መጣች!”
ጓደኛዬ ይህን ከነገረኝ በኋላ፣ “ያንን ሙሉቀንን ባወቅኩት እቺን አጫውተው ነበር” አለኝ።
ሙሉቀን መለሰ አጠር ያለ፣ ወፈር ያለ፣ በጣም ቀይ የሆነ የሃያ ስምንት ዓመት ጐረምሳ ነው። ለሁለት ሰዓት ያህል ሲያነጋግረን እንደገመትኩት ሙሉቀን ሀሳቡን በቀጥታ የሚናገር ሰው ነው። ማለቴ፣ “እንዲህ ያልኩ እንደሆነ እንደዚህ ተብሎ ሊተረጐምብኝ ይችላል” የሚል ሥጋት የለበትም።
“ሙሉቀን ብለው ስም ያወጡልህ ለምንድነው?” አልነው።
“እህቴ ነች ያወጣችልኝ። እናቴ ‘ሙሉሰው’ ነው የምትለኝ። ከኔ በፊት አስወርዷት ነበር። ደሞ ታላላቆቼ አራቱም ሲወለዱ ምጥ ይበዛባት ነበር። እኔ ስወለድ ግን ይህ ችግር አልነበረም። ለዚህ ነው ‘ሙሉሰው’ ያለችኝ። ‘ስማቸው’ ይለኛል አባቴ። የመሬት ሙግት ነበረበት። ጠላቶች ነበሩት። እነሱን ስማቸው ማለቱ ነው።”
ሙሉቀን መለሰ በጐጃም ክፍለ ሀገር አነደድ ወረዳ ውስጥ ዳማ ኪዳነ ምሕረት በምትባል መንደር በ1946 ዓ.ም ተወለደ። አሥር ዓመት ሲሆነው እናቱ ስለሞቱ፣ አዲስ አበባ ይኖሩ የነበሩ አጐቱ እንዲማር ብለው አመጡት። ኰልፌ ሰፈር ጳውሎስ ትምህርት ቤት ገባ። ግን ብዙ አልተማረም። ያጐቱ ሚስት ይጠሉት ስለነበረ ብስጭት በዛበት።
እንግዲህ ኰልፌ አንድ የጡረታ ቤት ነበረ። ባንድ ጐኑ የልጆች ማሳደጊያ ነበረው። የሚረዱ አሉ ሲባል ሰምቶ ሙሉቀን ሄዶ ጠየቀ። ተቀበሉት።
“የበላይ አስተዳዳሪዋ ይወዱኝ ነበር። ‘ኤልቪስ’ ነበር የሚሉኝ። በሁለት ወር እንደዚህ ልብስ ይዘውልኝ ይመጡ ነበር። ውጭ አገር ልኬ አስተምርሃለሁ ብለውኝም ነበር። ይንከባከቡኝ ነበር። እወዳቸው ነበር። ውለታቸው በጣም ትዝ ይለኛል።”
እዚያው የሙዚቃ ትምህርት ቤት ተከፈተ። አቶ ተፈራ አቡነ ወልድ ነበሩ አስተማሪው።
ሙሉቀን ስድስት ወር ያህል እንደተማረ እህቱ ስለታመመች ወደ አገር ቤት ሄደ። ያን ጊዜ ነው አዲስ አበባ ውስጥ አክስት እንዳሉት ያወቀው። እሳቸው ይዘውት መጡና ከሳቸው ጋር መኖር ጀመረ። ቤታቸው የካ ሚካኤል ነው። እንግዲህ ሙሉቀን ወደ ሙዚቃ ትምህርት ቤቱ አልተመለሰም።
አክስቱ የወታደር ሚስት ናቸው፣ ጠላም ይነግዳሉ። ኑሮአቸው ጐስቋላ ነው። ልጁ አልተመቸውም።
አንድ ቀን ወደ ምድር ጦር ሙዚቃ ክፍል ሄደ። ሊቀጠር። አልተቀበሉትም። ግን በእርዳታ መልክ ሻይ የማፍላት ሥራ ሰጡት።
“ምድጃዋ የኤሌክትሪክ ነበረች። ባንድ ቀን ውስጥ ሶስት ጊዜ ኮረንቲ ያዘኝ” አለ።
ስድስት ወር ያህል ከሰራ በኋላ ትቶት ወጣ። ጥቂት ወራት ተንከራተተ።
ከአቡነ ጴጥሮስ ሐውልት ወረድ ብሎ አንድ ሻይ ቤት ነበረ። የሻይ ቤቱ ባለቤት ሙሉቀንን ይወደዋል፤ ይረዳዋል። ሀርሞኒካ የሚጫወት ጓደኛ አለው ሙሉቀን። ሻይ ቤቱ ቁጭ ይሉና ጓደኛው ሀርሞኒካውን ይጫወታል። ሙሉቀን ይዘፍናል።
አንድ ቀን ሙሉቀንና ጓደኞቹ አብረው ሲጫወቱ ያመሹና ወደ ሶስት ሰዓት ላይ አንዱን ጓደኛቸውን ለመሸኘት ይነሳሉ። ደጃች ውቤ ሰፈር ሲደርሱ የውቤ በርሀ ልዩ ልዩ ቀለማት መብራቶች በርተው ሙሉቀንን በጣም ያስደንቁታል። አንዱ ቤትማ ከሌሎቹም የበለጠ አሸብርቋል። ጓደኛሞቹ ይኸ ቤት ምንድነው ብለው ሲጠያይቁ፣ ይኸማ ‘ፈጣን ኦኬስትራ’ የሚጫወትበት ‘ፓትሪስ ሉሙምባ ናይት ክለብ’ ነው ይሏቸዋል።
ፊት ለፊቱ ካለው ሱቅ ሄደው፣
“ባለቤቱ ማነው የዚህ ናይት ክለብ?” ብለው ጠየቁ።
“ወይዘሮ አሰገደች አላምረው ናቸው” አለ ባለሱቁ።
“ሥራ ይሰጡኝ ይሆን ወይ?” ብሎ ጠየቀ ሙሉቀን።
“ፃፍና ጠይቃቸው” አለው ባለሱቁ፤ወረቀትና እስክሪፕቶ እየሰጠው።
እዚያው ቆሞ ደብዳቤውን ፃፈ። ጓደኛሞቹ ከፍርሃት ጋር እየታገሉ ከዚያ ከአስደናቂ ቤት ገቡ። ሙሉቀን ደብዳቤውን ለኦኬስትራው መሪ ሰጠው።
አነበበውና ሳቀበት።
“ምንድነው እሱ?” አሉ ወይዘሮ አሰገደች ከወዲያ ቁጭ ብለው።
ሰውየው ነገራቸው። ደብዳቤውን ተቀብለው አነበቡ።
“ፈትነው። ካለፈ ጥሩ … አለዚያም ሌላ ሥራ እሰጠዋለሁ” አሉ። የልጅ መልኩና ጎስቋላ ሁኔታው ሀዘኔታቸውን ቀስቅሶ ሳይሆን አይቀርም።
ያን ጊዜ ሙሉቀን እንደ ጥላሁን ገሰሰና እንደ ዓለማየሁ እሸቴ እያደረገ ይዘፍን ነበር። ባዶ እግሩንና በቁምጣ ሱሪ መድረኩ ላይ ወጣና ‘ለውነት እሞታለሁ፣ አልሳሳም ለነብሴ’ን እና ‘እንክርዳድ’ን ዘፈነ።
የናይት ክለቡ ሴቶች (በጣም ብዙ ናቸው) ዘፈኑን ወደዱለትና ያን ጊዜውኑ አንድ አራት መቶ ብር የሚሆን አዋጡለት።
“በበነጋታው ካኪ ልብስ ተገዛልኝ፤ ሱፍ ልብስ ተለካሁ። ቢትልስ ጫማ አደረኩ … እግሬን ታጥቤ!” አለ።
እዚያው ክፍል ተሰጠው። ምግብም ከዚያው ነው። የዘፈን ሥራ ጀመረ።
ወደ ናይት ክለቡ የሚመጣው ሰው እየበዛ ሄደ። ወይዘሮ አሰገደች ሙሉቀንን ኮንትራት (ውል) አስፈረሙት። እሱ ማታ ማታ ሊዘፍን፣ እሳቸው በወር ዘጠና ብር ሊከፍሉት።
“ዘጠና ብር! ሚልዬነር የሆንኩ ነው የመሰለኝ!” አለን።
የቀድሞው አሜሪካን ቤተ መጻሕፍት አጠገብ ‘ዙላ ናይት ክለብ’ የሚባል ነበር። የዚህ የዙላ ባለቤቶች መጥተው አነጋገሩት ሙሉቀንን። በወር ሦስት መቶ ብር እንክፈልህ፣ ለኛ ዝፈን አሉት። እሺ ብሎ ሄደ።
ሴትየዋ ኮንትራት አፍርሷል ብለው አሳሰሩት። ሦስተኛ ፖሊስ ጣቢያ። አንዱ ፖሊስ እሳቸውን ለማስደሰት ብሎ ሙሉቀንን በጥፊ ሲለው ጊዜ ታዲያ በጣም ተቆጡት።
“እንድታስፈራሩልኝ ነው እንጂ እንድትጎዱት አይደለም” አሉ።
ከቤታቸው አልጋ መጣለትና ተረኛው መኰንን ክፍል ተነጥፎለት እዚያ አደረ። በነጋታው ተፈታ። ‘ዙላ ናይት ክለብ’ ገባ።
“ጋሽ ሰሎሞን ተሰማ የደረሰውን ‘የዘላለም እንቅልፍ’ እና አቡበከር አሸኬ የደረሰውን ‘ያላየነው የለም’ … ሁለቱን ዘፈን ይዤ በቴሌቪዥን ቀረብኩ።”
አዲስ አበባ ሙሉቀን መለሰን ሊያውቀው ጀመረ።

የፖሊስ ኦርኬስትራ አስተዋዋቂ ሻለቃ ወርቅነህ ዘለቀ (የቅጽል ስማቸው ‘ይቀጥላል’)፣
“አንድ አራት መቶ ብር እንክፈልህ፣ ና እኛ ጋ!” አሉት።
እሺ ብሎ ሄደ። የወር ደሞዙ ይመጣል ታድያ – አንድ መቶ ብር ብቻ! እወጣለሁ ቢል ጊዜ፣ “ፈርመሃል!” ብለው አስፈራሩት። ልጅ ነዋ!
ሙሉቀን መለሰ ለፖሊስ ኦርኬስትራ በተቀጠረ በሦስት ቀኑ መቀሌ ከኦርኬስትራው ጋር የ “ወይዘሪት ትግራይ” የቁንጅና ውድድር ይደረግ ነበር። ሙሉቀን የጥላሁን ገሰሰን ዘፈኖች ዘፈነ። በጣም ወደደው ሕዝቡ። የኦርኬስትራው አባሎችም አለማየሁ እሸቴ ሄዶባቸው ስለነበረ ሙሉቀንን “ምትኩ” አሉት።
ተስፋዬ አበበ የደረሳቸውን ሦስት ዘፈኖች (“እምቧይ ሎሚ መስሎ” “እናቴ ስትወልደኝ መች አማከረችኝ” እና “ልጅነት” የተባሉትን) ሙሉቀን በሕዝብ ፊት ይዘፍን ጀመር። በነዚህ ዘፈኖች ታዋቂነትን አተረፈ። ጋዜጣ ላይም “ኮከብ ድምጻዊ ተጫዋች” ብለው ጻፉለት።
ከፖሊስ ኦርኬስትራ ጋር ሦስት ዓመት አገልግሎ ወጣ … የማታ ክበቦች እንደገና መጫወት ጀመረ።
ዛሬ በግዮን ሆቴል በ‘ዳህላክ ባንድ’ እየታጀበ ይዘፍናል። አንድ አስር የሚሆን የሙሉቀን መለሰ ሸክላ ወጥቷል። ከአብዮቱ ወዲህ ዘፈኖቹ በካሴት ተሰራጭተዋል።
ከዘፈኖችህ በጣም የምትወደው የትኞቹን ነው? ብለን ጠየቅነው።
“እኩል ነው የማያቸው። ግን … በጣም የሚያረኩኝ … በዜማውና በዘፈኑ … ‘ሰውነቷ’ እና ‘ሆዴ ነው ጠላትሽ’ … እ …… በሙዚቃ ጥራትና ባሠራር ደግሞ፣ ሙላቱ አስታጥቄ ያቀነባበራቸውና ከዳህላክ ባንድ ጋር የዘፈንኳቸው ‘ቼ በለው’ እና ‘ውቢት’።”
ከድምፃውያን ተጫዋቾች ማንን ታደንቃለህ? አልነው።
“ዓለማየሁ እሸቴን። ደረጃው በጣም ከፍተኛ ነው። ካሉን ዘፋኞች ሁሉ የበለጠ የሙዚቃ እውቀት አለው። ሁላችንም በዘልማድ የምንዘፍን ሲሆን፣ እሱ ግን ሙዚቃን በማወቅ ከኛ ብልጫ አለው። ፕሮፌሽናል ኢንተርናሽናል (በአለም አቀፍ ደረጃ ባለሙያ) ዘፋኝ ያለን እሱ ነው ብዬ የምኰራበት ሰው ነው።
“በድምፅ ደሞ እንደ ምኒልክ ወስናቸው ያለ ዘፋኝ የለንም። የኦፔራ ዘፋኝ ድምጽ ነው ያለው … ጥላሁን፣ ዓለማየሁ፣ ምኒልክ፣ ብዙነሽ፣ ሂሩት፣ ማህሙድ – እነዚህን የሚተኩ ድምጻውያን መብቀል አለባቸው። ይኸ የአገሪቱ ኃላፊነት ነው … ይህን ሙያ ሲበዛ ነው የምወደው። በየዕለቱ ይበልጥ እያወቅከው … እየተማርከው ትሄዳለህ። ማቆሚያ የለውም … ሙዚቃን በትምህርት ሳይሆን በልማድ ነው የማውቀው።
“አንደኛ የሚባል ዘፋኝ የለም። ሊኖርም አይችልም። ቢበዛ ‘የዓመቱ ኮከብ’ መባል ይችላል እንጂ … እያንዳንዱ ዘፋኝ የራሱ አይነት ልዩ ተሰጥዎ አለው።”
 (የሙሉቀን መለሰ ቃለመጠይቅ፤ በስብሐት ገብረ እግዚአብሔር፤1 973 ዓ.ም)
ምንጭ – (“ኪነት ዓምድ”፤ ፀደይ መጽሔት፤ ኅዳር ፲፱፻፸፫ ዓ.ም)


Read 1892 times