Saturday, 10 October 2020 12:19

የብሔራዊ መግባባት መድረክን የሚያመቻች ተቋም ተመሠረተ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(1 Vote)

      ከሁለት ወር በኋላ ሁሉን አቀፍ የብሔራዊ መግባባት መድረክ ይጀመራል

            በሀገሪቱ ሁሉን አቀፍ ብሔራዊ መግባባት ለማምጣት የወሰነ “ማይንድ ኢትዮጵያ” የተሰኘ ተቋም በፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ም/ቤት፣ በዴስቲኒ ኢትዮጵያ እና በሃሳብ ማዕድ በተሰኙ አካላት ተቋቋመ፡፡
ማይንድ ኢትዮጵያ (Multise ctutral Initative for national dialogue) ወይም ሁሉን አቀፍ ብሔራዊ ምክክር ኢንሼቲቭ ኢትዮጵያ የተሰኘው ይህ ተቋም በሀገሪቱ ያሉ የዘመናት የፖለቲካ እና የማህበራዊ ምስቅልቅሎች ላይ ባለድርሻ አካላትን በሙሉ በማወያየት ታላቅ ሀገራዊ መግባባት መድረክ የማዘጋጀት አላማ ይዞ መነሳቱን የፓርቲዎች የጋራ ም/ቤት ም/ሰብሳቢ አቶ ግርማ በቀለ ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል።
ተቋሙ ዋነኛ አላማው ሁሉን አቀፍ ሀገራዊ መግባባትና ብሔራዊ እርቅ መፍጠር መሆኑን ለዚህም ከወዲሁ ቅድመ ዝግጅቶች እያደረገ መሆኑንና በታህሳስ የመጀመሪያ ሳምንት ላይ ሁሉን አቀፍ የብሔራዊ መግባባት መድረክ ለመፍጠር መዘጋጀቱን ነው አቶ ግርማ ያስረዱት፡፡
በዚህ የብሔራዊ መግባባት ሂደት በሀገሪቱ የተፈጠሩ የፖለቲካ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ምስቅልቅሎሽ እና የሀገሪቱን ህልውና አደጋ ላይ የጣሉ አካሄዶች በሙሉ ተፈትሸው መፍትሔ እንዲያገኙ ይደረጋል ተብሎም ይጠበቃል።
ማይንድ ኢትዮጵያን የፈጠሩት ተቋማት በየራሳቸው ብሔራዊ መግባባት መድረክ እንዲዘጋጅ አላማ አድርገው የሚንቀሳቀሱ ሲሆን ይህን ተቋም የመሠረቱትም በጋራ አቅምና ጉልበት አላማቸውን ለማሳካት በማሰብ መሆኑን አቶ ግርማ ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡
የሚዘጋጀው መድረክ እስካሁን ፓርቲዎች ሲያደርጉት ከነበረው ውይይት የተለየ እና ፓርቲዎች ብቻ ሳይሆን ሁሉን አቀፍ መሆኑንና ምሁራን የሚዲያ ባለሙያዎች፣ ሴቶች፣ አርሶ አደሮች ምሁራን የከተማ እና የገጠር ነዋሪዎች የሚሳተፉበት የተለየ መድረክ ይሆናል ተብሏል፡፡
የብሔራዊ ምክክር መድረኩ ዋነኛ አላማው በሀገሪቱ ብሔራዊ መግባባትን ለማምጣት ያሰበ እንደመሆኑ መድረኩ በአንዴ የሚጠቃለል ሳይሆን በየጊዜው ደረጃ በደረጃ ተከታታይነት ባለው መልኩ የሚከናወን ይሆናል ተብሏል፡፡
የታሪክ አረዳድ ላይ ያሉ ልዩነቶች፣ በህገ መንግስት ላይ ያሉ የአረዳድ ልዩነቶች ምሁራን በዋናነነት ተሳታፊ የሚሆኑበት ይሆናል የተባለ ሲሆን ብሐራዊ ምክክሩ በዘንድሮ አመት የሚዘጋጀውን ብሔራዊ ምርጫ ብቻ ታሳቢ ያደረገ አይደለም ዘመን ተሻጋሪ ነው ተብሉል፡፡
ተቋሙ መድረኩን ከማመቻቸት ባለፈ አጀንዳ አንመርጥም የውይይት አጀንዳ የሚመርጡት የመድረኩ ተሳታፊዎች ይሆናሉ ተብሏል፡፡ የውይይት መድረኩ የበርካታ ሀገራትን ተሞክሮ ያካተተ ሳይንሳዊ የውይይት ሂደቶችን የተከተለ ተደርጐ የሚቀረጽ ይሆናልም ተብሏል፡፡


Read 4211 times