Saturday, 18 July 2020 15:41

ቤተ ክርስቲያኒቱ በሁከቱ የደረሱባትን ጉዳቶች የሚያጣራ ኮሚቴ አቋቋመች

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(1 Vote)

   • በሻሸመኔ 19 ምዕመናን መገደላቸውና ቤተ ክርስትያን መቃጠሉ ተጠቁሟል

          የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያን ተከትሎ፤ በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በተፈጠሩ ሁከቶች  በቤተ ክርስቲያኒቱና ምዕመኖቿ ላይ የደረሱ ጉዳቶችን የሚያጠና ኮሚቴ ማቋቋሟ ታውቋል፡፡
ከዓመት በፊት በቅዱስ ሲኖዶስ የተቋቋመው የቤተ ክርስቲያኒቱን የሰላምና የእርቅ ኮሚቴን ጨምሮ ከምዕመናንና ከተለያዩ አካላት የተውጣጣና ችግሩ ወደተፈጠረባቸው አካባቢዎች በማቅናት የጉዳት መጠኑን አጥንቶ ሪፖርት እንዲያቀርብ የሚጠበቀው ኮሚቴ የሚመራው በጠቅላይ ቤተክህነት ስራ አስኪያጅ መሆኑንም ተጠቁሟል፡፡
በሁከትና ግርግሩ ለተፈናቀሉ ምዕመናንም  አስቸኳይ እርዳታ እንዲሰባሰብ በቤተ ክርስቲያኑ የበላይ አካል አቅጣጫ የተቀመጠ ሲሆን ለዚህም ራሱን የቻለ ድጋፍ አሰባሳቢ ኮሚቴ መቋቋሙንም ኮሚቴውም በሊቀጳጳስ እንደሚመራ ተመልክቷል፡፡
ከተቋቋመው ኮሚቴ ጋርም የሃገር ሽማግሌዎች መማክርትም በጋራ እንደሚንቀሳቀስ ምንጮች ያመለከቱ ሲሆን፤ ኮሚቴው ሪፖርቱን በቀናት ውስጥ ያቀርባል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ኮሚቴው በዋናነት ጥናቱን የሚያደርገው በምዕምናንና ቤተ ክርስቲያን ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደርሷል የተባሉባቸው አርሲ ዞን፣ አሳሳ፣ አርሲ ነገሌ፣ አዳሚቱሉ፣ አርሲ ሮቤ፣ ባቱ (ዝዋይ)፣ ምዕራብ ሃረርጌና ጅማ አካባቢዎች እንደሆነም ታውቋል፡፡
በሻሸመኔ የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ የሃገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ያሬድ በቅዱስ ሲኖዶስ ለተቋቋመው የቤተ ክርስቲያኒቱ የሰላምና እርቅ ብሔራዊ ኮሚቴ አስቀድመው ባቀረቡት ሪፖርት፤ በሻሻመኔ በተከሰተው ሁከትና ግርግር አንድ ቤተ ክርስቲያን መቃጠሉን 19 ምዕምናን መገደላቸውንና ከ3ሺህ በላይ የሚሆኑ መፈናቀላቸውን አስታውቀዋል፡፡
በሻሸመኔ የደረሰውን ጨምሮ ከላይ በተጠቀሰው የክልሉ አካባቢዎች በቤተ ክርስቲያንና በምዕመናን ላይ የደረሰው ጉዳት ተጠንቶ ለመንግስት እንደሚቀርብና መንግስትም ዘላቂ መፍትሄ እንዲያበጅ እንደሚጠየቅ ተጠቁሟል፡፡
የሰላምና የእርቅ ኮሚቴው ባለፈው ዓመት ለስራ ማስኬጃ የተመደበለት 10 ሚሊዮን ብር ሙሉ በሙሉ ለተጎጂ ምዕመናን ድጋፍ እንዲውልም ቤተ ክርስቲያኒቱ መወሰኗ ታውቋል፡፡

Read 10763 times