Sunday, 05 January 2020 00:00

የዛምቢያው መሪ ደመወዛቸውን በ20 በመቶ ሊቀንሱ ነው

Written by 
Rate this item
(2 votes)

  የሁሉም ከፍተኛ ባለስልጣናት ደመወዝ እንዲቀነስ መመሪያ ሰጥተዋል

              የዛምቢያው ፕሬዚዳንት ኤድጋር ሉንጉ የራሳቸውን ጨምሮ የሁሉም ሌሎች የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት ደመወዝ በከፍተኛ ሁኔታ እንዲቀነስ የሚያስገድድ ጥብቅ ውሳኔ ማሳለፋቸውን አፍሪካን ኒውስ ዘግቧል፡፡
በርካታ ቁጥር ያላቸው ዜጎች በድህነት በሚማቅቁባት አገር ውስጥ ከፍተኛ ባለስልጣናት ከሚገባቸው በላይ ደመወዝ እየተከፈላቸው ነው ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ የእሳቸውን ጨምሮ የሁሉም የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት ደመወዝ እንዲቀነስ መመሪያ ማስተላለፋቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡
በመመሪያው መሰረት፤ ፕሬዚዳንት ሉንጉን ጨምሮ በከፍተኛ የደመወዝ እርከን ውስጥ የሚገኙ ቁልፍ የአገሪቱ ባለስልጣናት ከደመወዛቸው ላይ እስከ 20 በመቶ የሚደርስ ቅናሽ ይደረግባቸዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፤ ቅናሹ በእየ እርከኑ እስከ 10 በመቶ እንደሚደርስም አመልክቷል፡፡
የመንግስትን ወጪ ለመቀነስ ታጥቆ የተነሳው የፕሬዚዳንት ሉንጉ መንግስት፤ በቀጣይም ከፍተኛ ባለስልጣናት ለስብሰባና ለሌሎች ጉዳዮች ወደ ውጭ አገራት የሚያደርጉትን ጉዞ እንዲያቋርጡ አዲስ ትዕዛዝ ይሰጣል ተብሎ እንደሚጠበቅም የተነገረ ሲሆን ከደመወዝ ቅናሹና ከመሰል ቁጠባዎች የሚገኘው ገንዘብ ድሃ ዜጎችን ለመደጎም ለታሰቡ ፕሮጀክቶች እንደሚመደብ ተጠቁሟል፡፡

Read 2977 times