Saturday, 14 December 2019 12:12

ኮንዶምን በ ትክክል መጠቀም

Written by  ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
Rate this item
(2 votes)

 አ.ኤ.አ በ2018 ከUNAIDS እንደተገኘው መረጃ ከሆነ በኢትዮጵያ፡-
690 ሰዎች ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ይገኛል፤
የኤችአይቪ ቫይረስ ስርጭት ከ1000 በቫይረሱ ካልተያዙ ሰዎች መካከል አዲስ በቫይረሱ የሚያዙት ሰዎች በሁሉም እድሜና ጾታ ልክ በአንድ ዓመት ውስጥ 0.24. ነበር፡፡
የኤችአይቪ ስርጭትን በሚመለከት እድሜያቸው (ከ15-19) አመት የሆኑ ወጣቶች መካከል ቫይረሱ በደማቸው የሚገኝ 1% ነበር::
23000 ሰዎች በአዲስ በቫይረሱ ተይዘው ነበር፡፡
11000 ሰዎች ከቫይረሱ ጋር በተያያዘ በሚከሰት ሕመም ለህልፈት ተዳርገዋል፡፡
በኢትዮጵያ ከኤችአይቪ ኤድስ ጋር በተያያዘ የሚከሰተው ሞት አ.ኤ.አ ከ2010 ጀምሮ በ45% እንደቀነሰና ከ20000 ሞት ወደ 11000 ዝቅ ማለቱን UNAIDS ይገልጻል፡፡ በቫይረሱ በአዲስ የሚያዙ ሰዎችም ቁጥር በተመሳሳይ ጊዜ ሲታይ ከ29 000 ወደ 23 000 ዝቅ ማለቱን ያሳያል፡፡ በአለም አቀፍ ደረጃ በ2020 ዓ/ም 90-90-90 ማለትም፡-
90% የሚሆኑ ቫይረሱ በደማቸው ያለባቸው ሰዎች ያሉበትን የጤና ሁኔታ እንዲያውቁ ይጠበቃል፡፡
90% የሚሆኑት የኤች አይቪ ቫይረስ በደማቸው ያለባቸው ሰዎች ያሉበትን የጤና ሁኔታ ካወቁ በኋላ የህክምና እርዳታ እንዲያገኙ ይጥራሉ ወይንም ራሳቸውን ያዘጋጃሉ ተብሎ ይታመናል፡፡
90% የሚሆኑ ቫይረሱ በደማቸው ያለባቸው ሰዎች ሕክምና በማግኘታቸው ምክንያት ቫይረሱ ባለበት ደረጃ እንዲገታ ሊያደርጋ ይችላሉ፡፡
የአለም አቀፉ 90-90-90- በ2020/ ግብ በአለም ላይ በደማቸው ውስጥ የኤች አይቪ ቫይረስ ካለባቸው ሰዎች 81%ያሉ የህክምና አገልግሎት የሚያገኙና 73% ያህሉ ደግሞ ቫይረሱ ባለበት ደረጃ እንዲገታ ማድረግ ይችላሉ የሚል እምነት አለ፡፡
በኢትዮጵያ በ2018፡-
79% የሚሆኑ ቫይረሱ በደማቸው የሚገኝ ሰዎች ያሉበትን የጤና ሁኔታ አውቀዋል፡፡
65% የሚሆኑ ቫይረሱ በደማቸው ያለባቸው ሰዎች የህክምና እርዳታ በማግኘት ላይ ነበሩ፡፡
በእድሜያቸው 15 እና ከዚያ በላይ የሚሆኑ ቫይረሱ በደማቸው ከሚገኝባቸው ወጣቶች 66% የሚሆኑት ሕክምና በመውሰድ ላይ የነበሩ ሲሆን እድሜያቸው ከ0-14 አመት የሚሆናቸው ሕጻናት ደግሞ 59% ያህሉ ሕክምና በማግኘት ላይ ነበሩ፡፡
እ.ኤ.አ. በ2018 የተገኘው መረጃ እንደሚጠቁመው በእርግዝና ላይ ካሉት ሴቶች በደማቸው ውስጥ ቫይረሱ ከሚገኝባቸው 92% የሚሆኑት ፀረ ኤችአይቪ (antiretroviral) ይወስዱ የነበረ ሲሆን በዚህም ምክንያት ቫይረሱ ወደ አረገዙት ልጅ እንዳይተላለፍ ጥረት በመደረጉ ወደ 3700 በሚሆኑ ጨቅላ ሕጻናት ላይ አዲስ የቫይረስ ስርጭት እንዳይኖር አስችሏል፡፡    
ኤችአይቪ ቫይረስን ከሰው ወደ ሰው እንዳይተላለፍ በማድረጉ ረገድ አጋዥ ከሆኑት ውስጥ አንዱ መንገድ የግብረ ስጋ ግንኙነት በሚደረግበት ወቅት ኮንዶምን መጠቀም ነው፡፡ በዚህ እትም ስለኮንዶም አንዳንድ ነገሮችን የጠቆሙን የአምዳችን አንባቢ አቶ ስንሻው ንጉሱ ይባላሉ፡፡ ኑሯቸው በባህር ዳር ሲሆን የአንድ ሆቴል አስተዳዳር በመሆን የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ የእሳቸው መልዕክት የሚከተለው ነው፡፡
‹‹እኔ እንደምታዘበው ከሆነ አንዳንድ ነገሮች በመረሳት ላይ ይመስላሉ፡፡ ኤችአይቪ ኤድስ ስርጭቱ አስጨናቂ በነበረበት ዘመን የኮንዶም አጠቃቀሙም በዛው ልክ በመገናኛ ብዙሀን በማስታወቂያ ከመቅረብ ጀምሮ በተለያዩ አካባቢዎችም ህብረተሰቡ እንዲለምደው የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ነበሩ፡፡ አሁን ግን በሚገርም ሁኔታ ሁሉም ዝም ያለ ይመስላል፡፡ ዝምታውም ከሚታይባቸው ቦታዎች አንዱ የእኛ የሆቴሎች ስራ ነው፡፡ በየክፍሉ የራስጌ መሳቢያ ውስጥ የምናስቀምጣቸው ኮንዶሞች ምንም ጥቅም ላይ ሳይውሉ በነበሩበት ከሳምንት ወይንም አስራ አምስት ቀናት በላይ ይቀመጣሉ፡፡ እንግዶችስ የሉም ወይ የሚል ጥያቄ ቢነሳ ግን መልሱ አልጋዎች ባዶአቸውን አድረው አያውቁም የሚል ይሆናል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የኤችአይቪ ቫይረስ ዛሬም ሰዎች እየተጎዱበት መሆኑ ይነገራል፡፡ ታድያ ሁኔታውን በግሌ ሳስበው ሰዎች ኮንዶምን መጠቀም እየረሱ የመጡ ይመስለኛል፡፡›› ብለዋል፡፡
ወደ ዘጠና አምስት በመቶ (95%) ሕብረተሰቡስ ለኮንዶም ምንነትና ጠቀሜታ ያውቃል፡፡ ነገር ግን የባህርይ ለውጥ መጥቷል ለማለት አያስደፍርም፡፡ የኮንዶም አጠቃቀምን በተመለከተ አሁንም ወደፊትም ምንጊዜም በጠነከረ መልኩ ትምህርቱ መሰጠት አለበት:: ምክንያቱም ከትውልድ ትውልድ እየቀጠለ በየጊዜው ለአቅመ አዳም ወይም ለአቅመ ሄዋን የሚደርሱ ዜጎች ስለሚተኩና ለመረጃውም አዲስ ስለሚሆኑ ተገቢውን የጥንቃቄ መረጃ መስጠት ይገባል፡፡
አቶ ዳኛቸው አለማየሁ በዲኬቲ ኢትዮጵያ የብሄራዊ ሽያጭ አስተባባሪ ከአሁን ቀደም ለዚህ እትም የሰጡት መልስ ነው፡፡
አቶ ዳኛቸው እንዳሉትም የኮንዶም አጠቃቀምን በሚመለከት ሰዎች በትክክል እንዲተገብሩት ለማድረግ ሰዎች ስለጉዳዩ ግንዛቤያቸው አድጎአል ይበቃል የማይባልበት ስለሆነ ትምህርቱን በተለይም እየተተካ ላለው አዲስ ትውልድ ማስተላለፍ ተገቢ ይሆናል፡፡
ስለኮንዶም አጠቃቀምና ጥቅም ሲገለጽ ጥቅሙ በተለያዩ መንገዶች ለሚደርሱ የጤናና የህይወት መቅሰፍቶች መፍትሔ ስለሆነ ነው የሚሉን Cashmere Leshkari የተባሉ ሕንዳዊት የህክምና ባለሙያ ናቸው፡፡
ኮንዶምን መጠቀም፡-
ያልተፈለገ እርግዝናን ለመከላከል ይረዳል፡፡
በግብረ ስጋ ግንኙነት ምክንያት ከሚከሰቱ ተላላፊ በሽታዎች ለመከላከል ይረዳል፡፡
ኤችአይቪን ጨምሮ ከተለያዩ ቫይረሶች ራስን ለመከላከል ይረዳል፡፡
የቤተሰብ እቅድ ዘዴን እውን በማድረጉ በኩልም ውጤታማ ነው፡፡
ኮንዶምን በመጠቀም ረገድ ስሜትን ወይንም ፍላጎትን ከማጣት ጀምሮ አጠቃቀሙን በትክክል አለመተግበርም ለችግር ወይንም ላልታሰበ የጤና መጓደል ሊያጋልጥ እንደሚችል ሕንዳዊቷ የህክምና ባለሙያ ይገልጻሉ፡፡ በግብረ ስጋ ግንኙነት ጊዜ የወሲብ ስሜትን በማሟላት ረገድ የኮንዶሞቹም አይነት የተለያየ በመሆኑ ማማረጥ እንደሚቻል አቶ ዳኛቸው የሰጡት ምክር የሚከተለው ነበር፡፡
‹‹ኮንዶሞች በተለያየ ስያሜና ዋጋ ሊሰራጩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ሁሉም ጥራታቸውን የጠበቁ ናቸው፡፡ ስለዚህ ጥራታቸው እንደ ተጠበቀ ሆኖ የኮንዶሞቹ ስያሜ እና ሲፈበረኩም አንዳንድ ልዩነቶች ሊኖራቸው ይችላል፡፡ ኮንዶሞቹ በመአዛቸው ሊለያዩ ይችላሉ፡፡ አንዳንዶቹ ሲሰሩ በሚኖራቸው ፈሳሽ አይነት ሊለያዩ ይችላሉ፡፡ ሌሎቹ ደግሞ ፍላጎትን እንዲጨምሩ ክርክር ነገሮች ያላቸው ሊሆኑ ይችላሉ:: ስለዚህ ተጠቃሚው የሚፈልገውን አይነት አስቀድሞ መለየትና መጠቀም ይችላል፡፡››
ኮንዶምን ማግኘት ቀላል መሆኑን ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል Cashmere Leshkari የዘረዘሩዋቸውን እናስነብባችሁ፡፡
ኮንዶም ካለመድሀኒት ማዘዣ ሊገዛ የሚችል የጤና መጠበቂያ ነው፡፡
ኮንዶምን ለመጠቀም ከሐኪም ዘንድ መቅረብ አያስፈልግም፡፡
ኮንዶም የሚጠቀሙትን ሰዎች ተፈጥሮ አይለውጥም፡፡
ኮንዶም በነጸነት የትም ሊገዛ የሚችል ምርት ነው፡፡ በሱቆች፤ ግሮሰሪዎች፤ እንዲሁም ሊጠቀሙባቸው በሚሄዱባቸው ሆቴሎች እንደፍላጎታቸው የሚያገኙት ነው፡፡
ጥቅሞቹም፡-
ኮንዶም በግብረ ስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ በሽታዎችን ኤችአይቪን ጨምሮ ለመከላከል ይረዳል፡፡
ኮንዶም ማንኛውም በሽታ ከሰው ወደ ሰው እንዳይተላለፍ ለማድረግ ያስችላል፡፡
ኮንዶም ያልተፈለገ እርግዝናን ለመከላከል ይረዳል፡፡
ኮንዶምን በመጠቀም ረገድ ሊደረጉ የሚገባቸውን ጥንቃቄዎች ኮንዶም በሚሸጥባቸው ፓኮዎች ውስጥ በዝርዝር የተቀመጠ ስለሆነ ያሉትን መረጃዎች በትክክል በመከተል ተገልጋዮች እንዲጠቀሙበት ያስፈልጋል፡፡

Read 15081 times