Print this page
Sunday, 24 November 2019 00:00

በ5 አመታት ውስጥ ከአለማችን አህዮችገሚሶቹ ለቻይና ይታረዳሉ ተባለ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

  በቻይና ከአህዮች ቆዳ የሚሰራ መድሃኒት ፍላጎት በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱን ተከትሎ፣ በአሁኑ ወቅት በመላው አለም ከሚገኙ 45.8 ሚሊዮን አህዮች መካከል ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ለዚሁ አገልግሎት ይታረዳሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ዴይሊ ሜይል ዘግቧል፡፡
በቻይና ኢጃኦ ተብሎ የሚጠራውንና ከጉንፋን ጀምሮ የተለያዩ አይነት በሽታዎችን እንደሚያድንና እርጅናን እንደሚከላከል የተነገረለትን መድሃኒት ለማምረት በየአመቱ አምስት ሚሊዮን ያህል አህዮች እንደሚታረዱ የጠቆመው ዘገባው፤ የመድሃኒቱ ምርት ከ2013 እስከ 2016 በነበሩት አመታት ብቻ በ20 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን አመልክቷል፡፡
በቻይና ከ1992 አንስቶ በነበሩት አመታት የአህዮች ቁጥር በ76 በመቶ መቀነሱን ያስታወሰው ዘገባው፤ ይህን ተከትሎም አገሪቱ ከሌሎች የደቡብ አሜሪካ፣ አፍሪካና እስያ አገራት በርካታ ቁጥር ያላቸው አህዮችን ለመግዛት መገደዷንና በዚህም በአገራቱ ውስጥ ህገ ወጥ የአህዮች ንግድና እርድ ሊስፋፋ መቻሉን አመልክቷል፡፡
በቻይና እያደገ የመጣው የአህዮች ፍላጎት በሌሎች በርካታ አገራት የአህዮች ዝርፊያን በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደጉን የጠቆመው ዘገባው፤ ይህም አህዮችን ለእርሻና ማጓጓዣ በመጠቀም ኑሯቸውን የሚገፉ በአለማችን የሚገኙ ከ500 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ህልውናን አደጋ ላይ እንደጣለው ገልጧል፡፡
ቦትስዋና፣ ማሊና ሴኔጋልን የመሳሰሉ በርካታ የአለማችን አገራት፣ ህገ ወጥ የአህዮች ንግድና እርድን ለመከላከል ጥብቅ ህጎችንና መመሪያዎችን አውጥተው እየተገበሩ እንደሚገኙ ያመለከተው ዘገባው፤ ባለፉት 12 አመታት ገደማ የአህዮች ቁጥር በኪርጌዚስታን በ53 በመቶ፣ በብራዚል በ28 በመቶ፣ በቦትሱዋና በ37 በመቶ መቀነሱንም ጠቁሟል፡፡

Read 3413 times
Administrator

Latest from Administrator