“ያልተገነባ አንሸጥም” በሚል መርሁ የሚታወቀው ኖህ ሪል እስቴት መካከለኛ ገቢ ላላቸው ሰዎች የገነባውን 200 ባለ 4 ፎቅ የመኖሪያ አፓርትመንቶች ነገ ለባለቤቶቹ እንደሚያስረክብ አስታወቀ፡፡
ባለፈው ረቡዕ ድርጅቱ በቤስት ዌስተርን ሆቴል በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፣
“ኖህ ጋርደን ፌዝ 1” በማለት የሰየማቸው 200 ቤቶች፣ ድርጅቱ ከገነባቸው 21 ፕሮጀክቶች አንዱ መሆኑን ጠቅሶ፣ የመኖሪያ አፓርትመንቶቹ ባለ 4 ፎቅ መሆናቸውን ገልጿል፡፡
አፓርትመንቶቹ በአንድ ፎቅ ላይ ሁለት ወይም ሦስት የመኝታ ክፍሎች ሲኖራቸው ዋጋቸውም ከ1.1ሚ እስከ 2.5 ሚሊዮን ብር ስለሆነ፣ መካከለኛ ገቢ ያለው ሰው ሊገዛቸው የሚችላቸውና ከባንክ ጋር በ3 ዓመት የሚከፈል የቤት መግዣ ብድር (ሞርጌጅ) መመቻቸቱ ታውቋል፡፡
ኖህ ሪል እስቴት በዚህ ዓመት 2019) ሌሎች 3 ፕሮጀክቶችን ለማስረከብ ማቀዱን ጠቅሶ ለባለቤቶቹ የተላለፉትን አፓርትመንቶች የንጽህናና የጥገና ተግባራት ሙሉ ለሙሉ የሚያከናውነውን RUC የተባለ የመኖሪያ አካባቢ አስተዳደር ማቋቋሙን ገልጿል፡፡