የትራፊክ አደጋ በመላው አለም እያደረሰ ያለው ጥፋት እየከፋ መሆኑንና በአለማችን በየአመቱ 1.35 ሚሊዮን ሰዎች በመኪና አደጋ ሰበብ ለሞት እንደሚዳረጉ ተመድ አስታውቋል፡፡
ካለፈው ሰኞ ጀምሮ በመከበር ላይ የሚገኘውን አለማቀፍ የመንገድ ደህንነት ሳምንት አስመልክቶ ተመድ ባወጣው መግለጫ እንዳለው፣ በመኪና የሚከሰት የመቁሰል አደጋ በአለም አቀፍ ደረጃ ከ5 እስከ 29 አመት የእድሜ ክልል ውስጥ የሚኖሩ ሰዎችን ለሞት በመዳረግ ቀዳሚነቱን ይዟል፡፡
አነስተኛ ገቢ ባላቸው አገራት ለትራፊክ አደጋ የመጋለጥ እድል ከፍተኛ ገቢ ካላቸው አገራት ጋር ሲነጻጸር በሶስት እጥፍ እንደሚበልጥ የጠቆመው መግለጫው፣ በአለማችን ከፍተኛው የትራፊክ አደጋ ስጋት ያለው በአፍሪካ መሆኑንና አውሮፓ አነስተኛ የትራፊክ አደጋ ስጋት እንዳለባት አመልክቷል፡፡
በመላው አለም በትራፊክ አደጋ በየአመቱ ለሞት ከሚዳረጉት መካከል እግረኞችና የብስክሌት አሽከርካሪዎች 26 በመቶውን ሲይዙ፣ የሞተር ብስክሌት አሽከርካሪዎችና የመኪና ተሳፋሪዎች ደግሞ 28 በመቶ ድርሻ እንዳላቸው መግለጫው አስታውቋል፡፡
Published in
ከአለም ዙሪያ