Saturday, 26 May 2012 12:27

የሳቻ ባሮን ዘ ዲክታተር አነጋጋሪ ሆኗል

Written by  ግሩም ሠይፉ
Rate this item
(0 votes)

በመላው ዓለም ለእይታ ከበቃ ሳምንት የሆነው የሳቻ ባሮን ኮሜዲ ‹ዘ ዲክታተር› በገቢ ባይሳካለትም በአስቂኝ ትእይንቶቹ እና በአወዛጋቢ ጭብጡ አነጋጋሪ መሆኑን ዘ ሆሊውድ ሪፖርተር አወሳ፡፡  ዘ ዲክታተር በቀድሞው የሊቢያ መሪ ሙአመር ጋዳፊና በኢራቁ ሳዳም ሁሴን ባህርያት ላይ ተመስርቶ የተሰራ ሲሆን በልቦለድ የተፈጠረች የሰሜን አፍሪካ አገር ሞዲያናም ስላለው አምባገነን መሪ ጄነራል አላዲን የህይወት ታሪክ የሚያጠነጥን ፊልም ነው፡፡የፊልሙ ዲያሬክተር ላሪ ቻርለስ ፊልሙ ከእስልምና ሃይማኖትና ከአረቡ አለም መንግስታት ጋር እንዳይያያዝ ጥንቃቄ ተደርጓል ብሎ ቢናገርም ሳቻ ባሮን በትወናው መረን የለቀቁ ቀልዶችንና ትእይንቶችን አብዝቷል በሚል ለትችት ተዳርጓል፡፡ ፊልሙ በምሰራቅ አውሮፓዎቹ አገራት ታጃኪስታን፤ቱርኪኔሚስታንና ቤለሩስ እንዳይታይ መታገዱም ታውቋል፡፡

በ65 ሚሊዮን ዶላር በጀት የተሰራው ዘ ዲክታተር በመጀመርያ ሳምንቱ ያስገባው ገቢ 17.4 ሚሊዮን ዶላር ብቻ እንደሆነ ያመለከተው የቦክስ ኦፊስ ሞጆ መረጃ የኮሜዲ ፊልሙ እጅግ አዝናኝ ይዘት ቢኖረውም በገበያው “ዘ አቬንጀርስ” “እና ዘ ባትል ሺፕ” ፊልሞች ያገኙትን ትኩረት መፎካከር እንደተሳነው ገልጿል፡፡ ሳቻ ባሮን ኮሀን በዘ ዲክታተር ፊልም ላይ ለመተወን 20 ሚሊዮን ዶላር እንደተከፈለው ያወሳው የፎርብስ ዘገባ በበኩሉ ተዋናዩ ባለፉት 12 ወራት ማዳጋስካር 3 እና ሪዮ በተባሉ የካርቱን ፊልሞች በድምፅ ተዋናይነት ተሳትፎ ዓመታዊ ገቢው 30 ሚሊዮን ዶላር በመድረስ ከእነ ብራድ ፒት እኩል ክፍያ የሚያገኝ ምርጥ ተዋናይ አድርጎታል ብሏል፡፡እንግሊዛዊው ኮሜድያን ሳቻ ባሮን የካምብሪጅ ምሩቅ ሲሆን አሊ ጂ፤ቡርኖና ቦራት በተባሉ ገፀባህርያቱ ይታወቃል፡፡ ኮሜድያኑ ለሶሻል ሚዲያ እና ለመገናኛ ብዙሃናት ብዙም ትኩረት አለመስጠቱ ሊያገኝ የሚችለውን ገቢ ቀንሶበታል ያለው የፎርብስ ሀተታ ብዙውን ጊዜ በገፀባህርያቱ ተደብቆ አደባባይ መውጣቱ ሊኖር የሚችለውን ዝና ቀንሶበታል በሚል ትንታኔውን አቅርቧል፡፡ቦክስ ኦፊስ ባይነምበርስ ባሰፈረው አሃዛዊ መረጃ በአንድ የፊልም ስራ ከ15 ሚሊዮን ዶላር ጀምሮ ክፍያ የሚጠይቀው ሳቻ ባሮን በአጭር የትወና ዘመኑ በሰራባቸው 10 የሚደርሱ ፊልሞች 2.02 ቢሊዮን ዶላር ዓለም አቀፍ ገቢ አግኝቷል፡፡

 

 

 

Read 1287 times Last modified on Saturday, 26 May 2012 12:35