Print this page
Saturday, 20 October 2018 13:19

“በግ ያያችሁ ና ወዲህ በሉኝ!”

Written by 
Rate this item
(10 votes)

ሰውዬው ከሰፈሩ ሁሉ በምስኪንነቱ የታወቀ ነው፡፡ ዓመት በዓል በደረሰ ጊዜ ሁሉ፣ አንዱ ይመጣና፤
“ጋሽ ሰመረ፤ በዚህ በዓል ምን ልታርድ ነው ያሰብከው?”
ጋሽ ሰመረም፤
“ካገኘሁ በሬ፣ ካላገኘሁ አንዲት ጫጩት አላጣም!”
ሁለተኛው መንደርተኛ በቀጣዩ በዓል ይጠይቀዋል፤
“ጋሽ ሰመረ፤ በቀጣዩ በዓልስ ምን ልታርድ አስሃበል?”
ጋሽ ሰመረ፤
“በሬ፣ ፍየል፣ በግ … ከጠፋ አንዲት ጫጩት!”
በዓሉ ይመጣል፡፡ አንድ ጫጩት ያርዳል፡፡ እንዲህ እንዲህ እያለ ብዙ ጫጩት እያረደ ከበላ በኋላ ከእለታት አንድ ቀን ሞላለትና አንዲት ኮስማና በግ ገዛ፡፡
በመንደሩ እየተዘዋወረ፤ የየቤቱን በር እያንኳኳም፤
“በግ ያየህ ና ወዲህ በለኝ!
በግ ያየህ ና ወዲህ በለኝ!...” ይል ጀመር፡፡
“አላየንም!” ይሉታል፡፡
ለካስ ጋሽ ሰመረ፤ በጓ ጠፍታበት ሳይሆን አንደኛው ግቢ ውስጥ በአጥር ወርውሯት ኖሯል፡፡
መዘዋወሩን የቀጠለው ግን በሌሎቹ ግቢዎች አቅጣጫ ነው፡፡ ጋሽ ሰመረ በግ እንደገዛ ሰፈሩ ሁሉ ማወቅ አለበታ!
በመጨረሻ በጓን የወረወረበት ግቢ ዘንድ ሲደርስ ሰውነቱ ዛል ብሏል፡፡
በር አንኳኳና ተከፈተለት፡፡
“ማነው?” አሉ፤ አንድ አሮጊት ሴትዮ፡፡
“እኔ ነኝ፡፡ እዚህ ግቢ በግ ገብታብኝ ነበር፡፡ ባለበጉ ነኝ!”
“ውይ ይቺ አቃስታ አቃስታ ክልትው ብላ የሞተችው በግ ያንተ ኖራለች እንዴ?”
ጋሽ ሰመረም፤
“ገደላችኋት? በምን መታችኋት ነው?”
"ደሞ በምን ትመታለች? ለራሷ ኮሳሳ? … እንደመሰለኝ በአጥር የወረወርካት ጊዜ አጥሩ ወግቷት ነው ደሟ አልቆ የሞተችው! … በል ጓሮ ዙርና ሬሳህን ተሸክመህ ሂድ!”
ጋሽ ሰመረም፤
“አይ እማማ! እጄን በጄ ነው በሉኛ!”
አሮጊቷም፤
“አይ ልጄ፤ አሁን ንዴቱም፣ ፀፀቱም አይጠቅምህም! ሚስጥሩ በእኔና ባንተ ማህል ይቆይና፤ አልሞተችም በጌ ብለህ አስበህ በሥነ ስርዓት ይዘሃት ሩጥ!” አሉት፡፡
***
የሞተውን አለ፣ ያለውን ሞቷል ከማለት ያውጣን!
ማስተዋል ያነሰው አድናቆትም፣ ማስተዋል ያነሰው ተቃውሞም ሁለቱም መጨረሻቸው አያምርም፡፡ ታላቁ ፀሐፌ ተውኔትና ገጣሚ ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፤
“ጅላጅል ምላስ ብቻ ናት
ማሞካሸት የማይደክማት
ቀን አዝላ ማታ እምታወርድ
ንፉግን ልመና እምትሰድ”
ይለናል፡፡ በትኩስ ስሜት ውስጥ የሚሰራ ስራ ዋጋ ያስከፍላል፡፡ ጊዜያዊ መፍትሄ ፋታ ሊሰጠን ይችል ይሆናል እንጂ ዘላቂ ድል አያስገኝም፡፡ መሰረታዊ ድህነትን አስወግዶ መሰረታዊ የህይወት ለውጥን አያመጣም! እንደ ኢትዮጵያ በርካታ ችግሮችን ተሸክማ የኖረች አገር፤ አብዛኛው ሰቆቃዋ የሚመነጨው ከኢኮኖሚያዊ ለውጥ ማጣት ነው፡፡
“ድህነት በአፍ አይገባም” የሚለን ሎሬት ፀጋዬ “ማጣት፤ በነብስህ ጫፍ ተንጠራርተህ ሩቅ አልመህ ሁሉን መሳት” ይለናል፡፡ ነጋ ጠባና ለዘመናት ስለ ኢኮኖሚ ውድነት ማውራት የህዝብ መዝሙር እስኪመስል ድረስ ለምደነዋል፡፡ መፍትሄ ሳያገኝ የቆየ ችግር ደግሞ፣ ምንም ያህል ቢድበሰበስ፣ ቀን ቆጥሮ አመርቅዞ እጥፍ ድርብ ሆኖ ብቅ ይልብናል፡፡ ለአንድ ሰሞን የሥጋ ዋጋ ቀንሰናል ብለን ስናበቃ፣ ዛሬ የት እንደደረሰ ማስተዋል ነው፡፡ በቀን ሶስቴ እንመገባለን ብለን፣ ዛሬ ስንቴ እንደምንመገብ ልብ ማለት ነው፡፡ “ትሻልን ትቼ ትብስን አገባሁ” የምንልባት አገር መሆን የለባትም፡፡ “ከባልሽ ባሌ ይበልጣል፤ ሽሮ አበድሪኝ" ማለትም የአፍ አመል ሆኖ ቀሪ ነው!
የኢኮኖሚ ሙያ ምሁራኖቻችን ወገባቸውን ጠበቅ አድርገው፤ “ከእንግዲህ አንራብም!” ብለው ሀሞታቸውን መረር አድርገው፣ እንደ ጥንቶቹ አውሮፓውያን ቆርጠው አገር የሚገነቡ ህዝቦች ማየት አለብን ብለው፤ ምርምር ላይ ማትኮር አለባቸው፡፡ “አፍአዊ ሳይሆን ልባዊ መሆን የሚቻለው እንዴት ነው?” የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ተግተው፣ ለህዝብ መጠቆም፣ ፈር መቅደድ አለባቸው፡፡
ራስን መደለልም ሆነ ሌላውን ማታለል ወንዝ አያሻግርም፡፡ የፖለቲካ ስብከት መሬት አያስረግጥም፡፡ ዲሞክራሲም፣ ፍትህና እኩልነትም የአንድ ሰሞን ሰበካ እንጂ ባዶ ሆድ የሚሞሉ እህል ውሃዎች አይሆኑም፡፡ በየዓመት በዓሉ ባልነበረ በግ፤ “በግ ያያችሁ ና ወዲህ በለኝ” ከሚለው ግብዝ ባለበግ መማር አለብን፡፡ ለሰው ይምሰል ብለን የምናደርገው ነገር፣ የማታ ማታ ዋጋ ያስከፍለናልና እናስብበት!
 


Read 9085 times
Administrator

Latest from Administrator