Saturday, 01 September 2018 15:34

‹‹…አመራር…የማይገባበት ቦ ታ የለም…››

Written by  ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
Rate this item
(3 votes)

 …በአንድ ወቅት ማለትም የዛሬ 35/ሰላሳ አምስት አመት ገደማ ልጅ ለመውለድ በአዲስ አበባ ወደ አንድ ሆስፒታል ተወሰድኩ። እኔ ምጥ ይዞኝ እጮሀለሁ፡፡ ወደማዋለጃው ክፍል ሲያስገቡኝ ሌሎች ሁለት የሚጮሁ ሴቶችም ነበሩ፡፡ ታድያ አንዲት የሙያው ባልደረባ የሆነች ነገር ግን ዶክተር ያልሆነች ወደ ሴቶቹ እየተጠጋች …ዝምበይ አትጩሂ… የመጀመሪያሽ ነው እንዴ? እያለች ትቆጣለች። ታድያ ወደእኔም መጥታ አትጩሂ ብያለሁ… የመጀመሪያ ልጅሽ ነው? ስትለኝ….አ.አ.ይ ሁለተኛዬ ነው…. አልኩዋት፡፡ ታድያ ምን ያስጮህሻል? ምጥን ታውቂው የለም እንዴ? አለችኝ፡፡ ምጥ ደግሞ ታውቂዋለሽ ይባላል እንዴ? ስላት …መለስ ብላ በጥፊ አጮለችኝ፡፡ እኔም በድንጋጤ የባሰውን አለቀስኩ፡፡ ሐኪምዋ ስትመጣ ብነግራትም ምንም እርምጃ አልወሰደችም፡፡ ቢያንስ እንኩዋን አልተቆጣቻትም፡፡ እንደዚህ ያለውን ጊዜ አሳልፈን ዛሬ ያለውን የህክምና መስተንግዶ ስመለከት እጅግ ይደንቀኛል፡፡
ወ/ሮ ሰላምነሽ ኃይሌ…ከጎፋ
ከላይ ያነበባችሁት ልጅ የመውለድ ልምድ በአምዱ አዘጋጅ ጥያቄ ከወ/ሮ ሰላምነሽ የተገኘ መልስ ነበር፡፡ ይህ ቀደም ባለው ጊዜ የነበረው በአሰራር ላይ የሚስተዋል አንዳንድ አስተዳደራዊ ስህተት ዛሬም ጭርሱንም ጠፍቶአል ማለት አይቻልም፡፡ ማንኛውም ሙያ የአስተዳደር ተግባሩ የተስተ ካከለ እንዲሆን የሚጠበቅ በመሆኑ በትምህርት ተቋማት በቀጥታ ለሁሉም የትምህርት አይነቶች ባይሰጥም እንኩዋን ወደሙያው ሲገባ በስልጠና በመታገዝ የአስተዳደር እውቀትን ማዳበር ተገቢ መሆኑን የነገሩን ዶ/ር አደራ አብደላ የSAK የስልጠናና የማማከር አገልግሎት መስራችና ባለቤት ናቸው፡፡
ዶ/ር አደራ እንዳሉት የሰው ልጅ በመጀመሪያ እራሱን ይመራል፡፡ ከዚያም የሰው ልጆችን ይመራል፡፡ ቅድሚያ ትኩረት የሚያገኘው… ሰው ሌሎችን ከመምራቱ በፊት አስቀድሞ  በመልካም አስተሳሰቦች ሆነ ብሎ እራሱ ላይ ልምምድ በማድረግ በአስተሳሰብ፤ በመንፈሳዊ ሕይወት፤ በጤንነት፤ ማህበራዊ ክህሎትን በማዳበር፤ እራሱን በመጀመሪያ መለወጥ ያስፈልገዋል። ከዚህ ባለፈ ሌሎችን ሰዎች ለመምራት በሚመሩት ሰዎች ላይ በጎ ተጽእኖ በማም ጣት የጋራ ራእይና አላማን የማሳካት ሂደት ነው፡፡
የአመራር እውቀትን ለማዳበር ትምህርቱ የትኛው እድሜ ወይንም የትምህርት ደረጃ ላይ ቢጀ መር ይሻላል ለሚለው በጽንሰ ሐሳብ ደረጃ ሲታይ በአለም ላይ እስከአሁን ድረስ ድምዳሜ ያል ተሰጠው ነገር ነው እንደ ዶ/ር አደራ አገላለጽ፡፡
የመሪነት ችሎታ በተፈጥሮ የሚገኝ ነው ብለው የሚያምኑ ንድፈ ሃሳቦች አሉ፡፡
አንዳንድ ንድፈሀሳቦች ደግሞ አመራር ይቀረጻል፤ ያድጋል እንጂ በተፈጥሮ የሚገኝ አይደለም የሚሉም አሉ፡፡  
ዶ/ር አደራ እንደሚሉት ሁለቱንም መንገዶች ትክክል ናቸው ብሎ መቀበል ይቻላል፡፡ ነገር ግን በተፈጥሮ ሊገኝ የሚችል ነው በሚለው ብቻ መቆም ሳይሆን በትምሀርት ሊያድግ ሊደገፍ የሚገባው ነገር ነው የሚለው ይበልጥ የሚያስማማ ነው። የአስተዳደር ችሎታ በተፈጥሮ የሚገኝ ነው ሲባል አንዳንዶች ሊታደሉት የሚችሉ ሲሆን የእነሱም የመሪነት ችሎታ በተለያዩ አቅጣጫ ዎች እገዛን ሊያገኝ የሚገባው ይሆናል፡፡ ስለዚህም በአገራችን በተለያዩ የትምህርት ደረጃዎች በስልጠና የሚሰጥ ሲሆን ወደስራ ገበታ ለተሰማሩትም ባለሞያዎች ስልጠናው እንደፍላጎቱ ይሰጣል ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር ESOG አስተባባሪነት የአስተዳደር ስልጠናው ለማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች በደብረዘይት ለሶስት ቀናት ያክል ከAug/ 23-25 ተሰጥቶአል። በስልጠናው ላይ ተሳታፊ ከነበሩት ሐኪሞች መካከል ዶ/ር ሽፈራው ነጋሽ እና ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ ስለ ስልጠናው እና ከሙያቸው ጋር ያለውን ግንኙነት በሚመለከት ሀሳብ ሰጥተዋል። ዶ/ር ሽፈራው የማህጸንና ጽንስ ሕክምና እንዲሁም የማህጸን ካንሰር ሕክምና (Gynecology Oncology) እስፔሻሊስት በተጨማሪም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በተባባሪ ፕሮፌሰር ማእረግ የህክምና ትምህርት መምህር ናቸው፡፡ ዶ/ር ሽፈራው የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር ESOG የቦርድ አባል ናቸው፡፡
ዶ/ር ሽፈራው እንደሚሉት Transformational leadership በሚል የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ባለ ሙያዎች የሆንነው ሰዎች መሰልጠናችን በተለይም በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ሙያን በማስተማር ላይ ለምንገኘው እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ የአመራር ብቃትን የማሳደግ ችሎታ በዚህ ሙያ ለተሰማሩ ባለሙያዎች የሚሰጠው ጥቅም በመጀመሪያ ሐኪሙ እራሱን የሚመራበት አቅም እንዲኖረው ማድረግ ነው። ከዚያም ሲያልፍ ቤተሰብን፤ ሕብረተሰብን፤ በተለያዩ ማህበራዊ አገልግሎቶች ውስጥ የሚኖረውን የአመራር ብቃት ለማሳደግ ይጠቅ ማል፡፡ ይህ የአመራር ብቃት በእርግጥ አስቀድሞውኑ ከተፈጥሮ፤ ከቤተሰብ፤ ከትምህርት ቤት… ከመሳሰሉት መገኘቱ እሙን ነው፡፡ ነገር ግን በተለይ አመራር ማለት እንዲህ ነው ተብሎ ትም ህርቱ በግልጽ ባለመሰጠቱ የሚጎድል ነገር መኖሩ እሙን ነው፡፡ ከዚህ በተረፈ ግን በተለይም በስራ ቦታ የተሰማሩ ባለ ሙያዎችን ማፍራት፤ የስራ ቦታውን በተለያየ ደረጃ መምራት፤ የሕክምና ትምህርትቤቱ ዲን መሆን የመሳሰሉት አመራርን የሚጠይቁ ስራዎች አሉ፡፡ ያ ብቻም ሳይሆን በየደረጃው ሁሉም ባለሙያ የሚመራው በኃላፊነት የሚጠየቅበት… ከጥበቃ፤ የጽዳት ሰራተኛ፤ ተላላኪዎችን ጨምሮ የሚያሰማሩ የቅርብ አለቆች ሁሉ ሊያውቁት የሚገባ ጥበብ ሲሆን ጠቅለል አድርጎ መስሪያ ቤቱን ከላይ እስከታች ድረስ ለሚቆጣጠሩት እና ለሚመሩት ደግሞ የበለጠ ጠቃሚ ነው፡፡ ከዚህም በተ ጨማሪ አገልግሎቱን ፈልገው ለሚመጡ ታካሚ ዎችም በተገቢው መንገድ የአመራር አሰጣጥ ሁኔታ ይኖ ራል፡፡ ስለዚህ መምህራን፤ ሐኪሞች፤ ተመራማሪዎች፤ መሪዎች እና ተመሪዎች ስለሆንን ይህ ስልጠና በቀጥታ ከሙያው ጋር የተገናኘነው ብለን ተቀብለነዋል ብለዋል ዶ/ር ሽፈራው ነጋሽ።
ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና እስፔሻሊስት፤ የማህጸን ካንሰር ህክምና (Gyne- cology Oncology) ባለሙያ ናቸው፡፡ እንዲሁም በቅዱስ ጳውሎስ ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ትምህ ርት ክፍል ኃላፊ ናቸው፡፡ ዶ/ር ታደሰ እንዳሉት አመራር እራስን ከመምራት ጀምሮ የማይገባ በት ቦታ የለም፡፡ ሁሉም ነገር የራሱ መንገድ እንዳለው የተረዳንበት ስልጠና ነው፡፡ በመሰልጠን ላይ የምንገኘው ባለሙያዎች ምናልባት የአመራር ችሎታ በተፈጥሮ ይገኛል ከሚ ለው ወይንም ከቤተሰብ፤ ከትምህርት ቤት የእርስ በእርስ ግንኙነት የተረዳነው ነገር በመኖሩ እንጂ በዚህ መልክ ዝርዝር ነገር ውስጥ ገብተን ተምረነዋል ለማለት የሚያስደፍር አጋጣሚ የለም ብለዋል፡፡
ዶ/ር ታደሰ አክለው እንደገለጹት ሕክምና ለህዝብ የሚሰጥ አገልግሎት ነው፡፡ ይህ አገልግሎት በስነስርአት ካልተመራ ለህዝቡ አስፈላጊውን አገልግሎት መስጠት አይቻልም፡፡ የህክምና ተማሪ ዎችን በማስተማር ላይ የምንገኝ ሲሆን ጤናማ አስተዳደር በሌለበት ተማሪዎችን ለሚያስፈልገው እውቀት ለማብቃት እና የሚፈለግባቸውን ግዴታ እንዲወጡ ለማድረግ አይቻልም፡፡ ስለ ዚህም በአጠቃላይ ለህብረተሰቡ በቂ የሆነ የህክምና አገልግሎት የሚሰጥ ኃይልን ለማግኘት የአመራር ብቃት ወሳኝነት ያለው መሆኑን ከስልጠናው መረዳት ይቻላል፡፡
ያልተስተካከለ አመራር ባለባቸው ተቋማት የሚታዩ የአገልግሎት አሰጣጦች ቢበላሹ ጉዳቱ ለህብረተሰቡ ብቻ ሳይሆን ለሐኪሙም ጭምር ነው፡፡ ይህንን ሕክምና ለመስጠት ገንዘብ እና ጊዜ የፈጀ እና የሚ ማረውን ሰው አካል በተለይም አስተሳሰብን የፈተነ በመሆኑ የዚህ ድካም ውጤት መና ሲሆን ለባለሙ ያውም ከባድ ነው፡፡ ሕብረተሰቡም በተሳካ አመራር በሚመራ የህክምና አገልግሎት ሊጠቀም ካልቻለ ውጤቱ ወደ መጥፎ ሊያዘነብል እንደሚችል እሙን ነው፡፡ ይህ ከሆነ እንደግለሰብ ጉዳት…. እንደ ተቋም ትልቅ ውድቀት፤ እንደ ሐገር ደግሞ ጤነኛ እና ደስተኛ ያልሆነ ህብረ ተሰብን ማፍራት ያስከትላል፡፡ ስለዚህ የምንመራውን ድርጅት በአመራር ጥበብ ካልመራነው በስተቀር በቂ አገልግሎት ማግኘት አይቻልም፤ በቂ አገልግሎት ካልተገኘ ደግሞ ህብረተሰብ አይደሰትም፤ ያልተደሰተ ህብረተሰብ ደግሞ ወደፊት አይራመድም፡፡ ይህ ደግሞ ሐገርን ወደፊት እንድት ራመድ አያስችላትም፡፡ ስለዚህ አገልግሎቱን የሚሰጡ ሰዎችን በተመሳሳይ እይታ በመቅረጽ የወደፊት ራእይን ለማሳካት የአመራር ጥበብ አስፈላጊ ይሆናል፡፡ ይህን የአመራር ችሎታን ለማዳበር የሚረዳ ስልጠና ማግኘት በአንድነት ወደሚፈለገው ግብ ለመድረስ የሚያበቃ በመሆኑ በጣም ጥሩ ነው ብለዋል ዶ/ር ታደሰ ኡርጌ፡፡

Read 2992 times