Print this page
Sunday, 13 May 2018 00:00

እድለ ቢስ ሰው ግመል ላይ ተቀምጦ ውሻ ይነክሰዋል!

Written by 
Rate this item
(6 votes)

ዴሞስቴን የተባለ የግሪክ ፈላስፋ ህዝብ በተሰበሰበበት ንግግር ለማድረግ እየተሳነው ስለተቸገረ፤ የንግግር ልምምድ ለማድረግ ወደ አንድ ወንዝ አጠገብ ይሄዳል፡፡
ወንዙ በከፍተኛ ፍጥነት እየተወረወረ ቋጥኝ ላይ ያርፍና ኃያል ድምፅ ይፈጥራል፡፡ ዴሞስቴን ደግሞ ይህንን ድምፅ ለማሸነፍ እጅግ ነጎድጓዳማ ድምፅ ያወጣል፡፡
ወንዙ በቀጣይ ጩኸቱን ተያይዞታል፡፡ ፈላስፋውም የፉክክር ንግግሩን ያምባርቃል፡፡ ፈላስፋው ይህን ልምምዱን ለተወሰነ ወቅት ካካሄደ በኋላ ወደ ህዝብ መሰብሰቢያው አደባባይ ተመለሰ፡፡ ስብሰባው ተዘጋጀለት፡፡
ወደመናገሪያው መድረክ ወጥቶ፤
“የአቴና ህዝብ ሆይ!” አለና ቀጠለ፤ “ዛሬ ስለአቴና ችግር በሰፊው ልነገራችሁና ላስረዳችሁ ነው ፊታችሁ የቆምኩት!” አለ በጣም ጮክ ብሎ፡፡
ህዝቡ ጆሮ አልሰጥ አለው፡፡ እርስ በርሱ እያወካ፣ ጨርሶ መደማመጥ ጠፋ፡፡ ዴሞስቴን በተቻለው ድምፅ ጮሆ እየተናገረ ነው፡፡ ሰሚ ግን ጠፋ፡፡
በመጨረሻ፤ የሞት ሞቱን ጮሆ፡-
“የአቴና ህዝቦች ሆይ፤
የአንዲት አህያ ታሪክ ልነግራችሁ ነው፤ አሁን …”
ቀስ በቀስ የህዝቡ ጩኸት ቀነሰ፡፡ በመካያውም ፀጥ እርጭ አለ፡፡ ጀመረ ዴሞስቴ፡-
“ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንዲት የምትከራይ አህያ የነበረችው አንድ ሰው ነበረ፡፡
በዚያው ወቅት አንድ ነጋዴ የሚከራይ አህያ ፍለጋ ወደ ባለአህያው መጥቶ፤
“ባለ አህያ?” ይለዋል፡፡
ባለ አህያ - “አቤት፤ ምን ልታዘዝ?”
ተከራይ - “የሚከራይ አህያ ፈልጌ ነበር?”
ባለ አህያ - “ውሰዳታ!”
ተከራይ - “ስንት ነው ሂሳብ?”
ባለ አህያ - “ለስንት ቀን?”
ተከራይ - “ለሶስት ቀን”
ባለ አህያው ዋጋውን ነግሮ, አህያዋን አስረከበውና ተከራይ ቀብድ ከፍሎ፣ አህያዋን ይዞ ሄደ፡፡
አንድ ቀን አልፎ ሁለተኛው ቀን ላይ ባለ አህያው ተከራይ በሄደበት መንገድ ወደ ገበያ ለመሄድ ጉዞ ጀመረ፡፡ ፀሐዩ በጣም ያቃጥላል፡፡ ምንም የጥላ መጠለያ የሌለበት፣ ጭው ያለ ሜዳ ነው፡፡ የአህያዋ ተከራይ አህያዋን አቁሞ፣ ጥላዋን ተጠልሎ ተቀምጧል፡፡
ባለአህያው ቀረብ ብሎ፤
“አስጠጋኝና አብሬህ ጥላው ስር ልቀመጥ” አለው
ተከራዩ - “አይቻልም”
ባለአህያ - “አህያዋኮ የራሴ ናት”
ተከራይ - “ትሁና! ዛሬን ጨምሮ እስከ ሦስት ቀን ድረስ የራሴ ናት”
ባለአህያ - “እንዲያውም፣ አህያዋን እንጂ ጥላዋን አልተከራየኸኝም - ለጥላዋ አስከፍልሃለሁ!”
ተከራይ - “ለሱ ሌላ ውል መፈራረም ይኖርብናል”
በዚህ ሁኔታ ሲጨቃጨቁ ቆዩ … አለና ዴሞስቴን ንግግሩን አቆመው፡፡
ህዝቡ፡-
እባክህ ጨርስልን! የዚህን መጨረሻ ሳናዳምጥ በጭራሽ ወደ ቤታችን አንሄድም!! እያለ አደባባዩን በጠበጠ!
“የአቴና ህዝብ ሆይ!
እጅግ አሳሳቢ የሆነውን የአቴና ችግር ላሳውቃችሁ ስናገር አልሰማ ብላችሁ፣ የአንድ አህያ ተረት መጨረሻ ለማወቅ ጓጉታችሁ ትጮሃላችሁ! ታሳዝናላችሁ! የአህያዋን ተረት መጨረሻ የምነግራችሁ፣ የአገራችሁን አቴናን ጉዳይ ነግሬያችሁ ሳበቃ ነው” ብሎ ለመናገር የፈለገውን ነገር ልባቸው እንደተንጠለጠለ ጨረሰላቸው፡፡
*   *   *
የሚያዳምጥ ህዝብ ማግኘት መታደል ነው፡፡ የሰማውን በልቦናው አሳድሮ ወደተግባር የሚለውጥ ህዝብ ማግኘት ደግሞ የመታደል መታደል ነው፡፡ ይህንን ለማግኘት ተጣጥሮ የአመለካከት ለውጥ ማምጣት ግድ ይላል፡፡ የለውጥ መንገዱ አዳጊ ሂደት እንጂ፤ በዚህ ጊዜ ለውጥ አመጣለሁ ብሎ ቀን ቆርጦ፣ መሳሪያ መርጦ በመቀመጥ የሚሆን አይደለም፡፡ ለውጥን ለማምጣት ለዋጩ ራሱ መለወጥ አለበት፡፡ የለውጡም ዓይነት መወሰን አለበት፡፡ ለውጡ ሥር - ነቀልና የመጨረሻው ዓይነት ከሆነ፣ ትራንስፎርሜሽን ነውና የቁርጡ ቀን ነው፡፡
የሥር - ነቀል ለውጥ ካደረገ፤ ከዚህ ቀደም የነበረው ምንነቱ ወዲያውኑ ተወገደ፣ ሞተ፣ ማለት ነው” ይለናል፤ ፈላስፋው ኤፒኩረስ፡፡
ሉክሩቲየስ የተባለው ሌላው ፈላስፋም፤
“ምንም ዓይነት ለውጥ ይሁን ለውጥ ከመጣ የቀድሞው ተንኮታኮተ፤ ስለዚህም ተደመሰሰ” ይላል፡፡ ይህ ማለት መሰረታዊ ለውጥ ተከስቷል እንደ ማለት ነው፡፡
ዞሮ ዞሮ በሀገራችን በኢትዮጵያ ለውጥ ይመጣ ዘንድ ከልባችን መመኘታችን አግባብነት አለው፡፡ ሁኔታዎች በአንድ ጊዜ ይከሰታሉ የሚል የዋህነት ግን አይኖርብንም፡፡ በየዘርፉ ያሉትን ችግሮች አንድ በአንድ በማየትና በመመርመር መላ ማበጀት ከጅምላ ዘመቻ ወይም ከሁሉን ባንዴ ርብርብ ያወጣናል፡፡ በሂሳብኛ አነጋገር integration by parts ብልት ብልቱን፣ በመጠን በመጠኑ እየቀመሩ ማዋሃድ እንደማለት ነው፡፡ የአገር አንድነትም መላው ይሄው ነው፡፡
ባለሙያዎቹን ወደ ስራውና ወደ ማዕዱ ማቅረብ ዋና ነገር ነው፡፡ አትሙት ላለው መላ አለው! ባለሙያ ሥራውን በፍቅር ይሰራ ዘንድ አዎንታዊ ድባብ (working atmosphere) ይፈልጋል፡፡ ቀዳሚው ፍቅር ነው፡፡ ከፍትፍቱ ፊቱን ይሻል፡፡ ውስጣዊ የሥራ ፉክክር ያወፍራል እንጂ አያቀጭጭም፡፡ መንፈስን ያጠነክራል እንጂ አያኮሰምንም፡፡ ይህም የአመለካከት ጉዳይ ነው፡፡ የበኩሌን ባዋጣ ሙሉው ስዕል ምሉዕነቱ ይረጋገጣል ብሎ የማሰብ ጉዳይ ነው፡፡ መማር የወረቀት ቀበኛ መሆን አይደለም፡፡ የሥራ መሰላል እንጂ፡፡ በመሰላሉ ጫፍ ወጣን ማለትም ሁሉን ቁልቁል እያዩ መኩራራት አይደለም፡፡ we shall never starve ብሎ የመቁረጥ ወኔ የሚፈልግ አያሉ የረሀብ ቢፌ እፊታችን ተደቅኗል! በጭራሽ ርሃብ አናማርጥም! ሁሉንም እናስወግዳለን እንጂ! መድኃኒቱ የየመስካችንን ኃላፊነት በቆራጥነት መወጣት ነው፡፡ እኔ ቆሜ ይህች አገር አትሸራረፍም ማለት ነው! ለዳተኝነት ቦታ አልሰጥም፣ ፍርሃት ደጄን አይረግጥም፣ አስፈላጊውን መስዋዕትነት ልከፍል ዝግጁ እሆናለሁ! ተበታትነን የትም አንደርስም! አጅ ለእጅ እንያያዝ! እንማከር፤ እንሰባሰብ፣ እንደራጅ!
“ካልተሳፈሩበት፣ ቶሎ ተሸቀዳድሞ፡፡
ጊዜ ታክሲ አይደለም አይጠብቅም ቆሞ!!
“የሚለውን አንዘንጋ! “ማነህ ባለሳምንት!” መባል አይቀርም፡፡ ያገኘነውን አጋጣሚ በወጉ መጠቀም ነው ብልህነት! አለበለዚያ፤ “ዕድለ-ቢስ ሰው፣ ግመል ላይ ተቀምጦ ውሻ ይነክሰዋል” የሚለውን ተረት እየተረትን፣ የሌሎች መጫወቻ ሆነን እንቀራለን፡፡ ምዕራባውያንና ምሥራቃውያን ወዳጆቻችን እንደ ወዳጅ የሚያስቡልን የሚመስሉት እስከጠቀምናቸው ድረስ ብቻ መሆኑን አንርሳ!   

Read 9014 times
Administrator

Latest from Administrator