አዲስ አበባ የሚገኘው “ጎተ የጀርመን የባህል ማዕከል የተመሠረተበትን 50ኛ ዓመት በተለያዩ ዝግጅቶች ማክበር ጀመረ፡፡ ረቡዕ ምሽት በተጀመረው የክብረ በአሉ መክፈቻ በብሉናይል ፊልምና ቴሌቪዥን አካዳሚ የተዘጋጀ የ15 ደቂቃ ዶክመንታሪ ፊልም ለእይታ በቅቷል፡፡ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር እንዲሁም የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ የከፍተኛ ትምህርት አማካሪ ፕሮፌሰር እንድርያስ እሸቴ በተገኙበት መክፈቻ በኢትዮጵያ የጀርመን አምባሳደር ሊስለር ሳይረስ ተቋሙ ባለፉት አምስት አስርት ዓመታት የጀርመንን ባህል እና ቋንቋ ለኢትዮጵያውያን ለማቅረብ ያደረገውን ጥረት እና ስኬት አድንቀዋል፡፡ እስከ ሰኔ በሚዘልቀው የወርቅ ኢዩቤልዩ ዝግጅት የፎቶግራፍ እና የሥዕል አውደርእይ፣ አውደ ጥናቶችና መሠል ዝግጅቶች እንደሚኖሩትም ማወቅ ተችሏል፡፡