Print this page
Saturday, 05 December 2015 09:41

“ወደ እውነተኛው ፌደራሊዝም እንመለስ”

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(13 votes)

የአዲስ አበባና የፊንፊኔ ዙሪያ ኦሮሚያ ልዩ ዞን ማስተር ፕላንን በተመለከተ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ ያለውን ዝርዝር አቋም በተመለከተ የፓርቲው ተቀዳሚ ምክትል ሊቀመንበር አቶ በቀለ
ገርባን አዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ በፅ/ቤታቸው ተገኝቶ አነጋግሯቸዋል፡፡

    መንግሥት ማስተርፕላኑ ከተሞችን በመሰረተ ልማት በማስተሳሰር እድገትን ለማምጣት ከፍተኛ ጥቅም አለው ይላል፡፡ ፓርቲያችሁ ደግሞ ማስተር ፕላኑን አልቀበልም ብሏል፡፡ በምን ምክንያት ነው የማትቀበሉት?
እኛ ማስተር ፕላኑን የማንቀበለው በትክክል የህዝቡን የልማት ጥያቄ ለመመለስ የተዘጋጀ ነው የሚል እምነት ስለሌለን ነው፡፡ መንግሥት በዚህ አሳቦ ወደ ኦሮሚያ አጎራባች ከተሞች ዘልቆ እየገባ ለባለስልጣናትና ለስርአቱ አገልጋዮች ተጨማሪ ገቢ ማስገኛ፣ የሀብት መዝረፊያ፣ በህዝብ ላይ ደግሞ ሌላ የጭቆና ቀንበር መጫኛ፤ ማንነቱን፣ ቋንቋውን፣ ባህሉን የማጥፋት ዘመቻ ነው ብለን ነው የምንወስደው ይሄን ለምን አልን? ስርአቱ ሲመሰረት,ኧ በህገ መንግሥት ተደንግጎ እንደሚገኘው ፌደራል ስርአት ነው፡፡ ማዕከላዊ መንግሥት ራሱን ችሎ የተሰጠው የስራ ድርሻ አለ፡፡ ክልሎች በዋነኝነት ራሳቸውን የማስተዳደር፣ ግብር የመሰብሰብ፣ የሰበሰቡትን ግብር ደግሞ እቅድ አውጥቶ በስራ ላይ የማዋል፣ በአካባቢያቸው የሚገኙ ማናቸውንም ነገር የማስተዳደር ስልጣኖች አሏቸው፡፡ ስለዚህ በአካባቢያቸው ሊፈፅሙት ያሰቡትን ልማት ለየትኛው ቅድሚያ እንደሚሰጡ በትክክል በገቢያቸው ላይ ተመስርተው ማርቀቅ ያለባቸው ራሳቸው ናቸው እንጂ ሌሎች ክልሎች ወይም ማዕከላዊ መንግሥት ሊያቅዱላቸው አይችሉም፡፡
አዲስ አበባ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ላሉ ከተሞች እቅድ የማውጣት አቅሙም ስልጣኑም የላትም፡፡ በህገ መንግሥቱ በምንም መንገድ አዲስ አበባ ለነዚህ ከተሞች እቅድ የማውጣት ስልጣን አልተሰጣትም፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ ቻርተርም፣ በኦሮሚያ ክልል ህገ መንግሥትም፣ በሀገሪቱ ህገ መንግሥትም ቢሆን ይሄን ስልጣን አልሰጠም፡፡ የፌደራል መንግሥትም በከተሞች ፕላን ውስጥ ጣልቃ የመግባት  ስልጣን አልተሰጠውም፡፡ እንደዚህ ከሆነ ከተሞች ራሳቸውን አስተዳደሩ ማለት እንዴት ይቻላል? ህዝቡ ምኑ ላይ ነው ራሱን አስተዳደረ የሚባለው? እንደዚህ ከሆነ ትናንት ከ25 ዓመት በፊት ወደነበርንበት ተመልሰን እየገባን ነው ማለት ነው፡፡
አሁን ለተነሳው አይነት ጥያቄ የፓርቲያችሁ ፕሮግራም ምን አይነት ምላሽ ነው የሚሰጠው?
እኛ አሁን በአገሪቱ ውስጥ እየተተገበረ ያለው የፌደራል ስርአት ነው አንልም፡፡ ምክንያቱም በአንድ ክልል ውስጥ የሚደረግን ነገር ሌላ ክልል ውስጥ በተመሳሳይ መልኩ ይገኛል፡፡ ይሄ ማለት እቅዶች ሁሉ ከላይ ወደታች የሚፈሱ፣ በትዕዛዝ መልክ የሚተላለፉ ናቸው ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ በአንድ የትግራይ ወረዳ ውስጥ ያለ የመንግሥት አሰራር በኦሮሚያ ውስጥ ወይም በደቡብ ውስጥ ይገኛል፡፡ ይሄ የሆነው ምንጩ ማዕከላዊው ስለሆነ ነው፡፡ ፌደራሊዝም ግን ፅንሰ ሀሳቡ ይሄ አይደለም፡፡ ለምሳሌ አሜሪካን ብንወስድ በአንዱ ስቴት በህግ የሚከለከል ነገር ሌላኛው ጋ ይፈቀዳል፡፡ አንዱ ስቴት የሞት ቅጣት ተግባራዊ ሊያደርግ ይችላል፤ ሌላው ጋር ፈፅሞ የተወገዘ ይሆናል፡፡ ይሄ የሆነው እንግዲህ ስቴቶች ራሳቸውን በራሳቸው የማስተዳደር መብታቸው ሳይሸራረፍ በመተግበሩ ነው፡፡ በአንፃሩ እኛ ጋ ግን ክልልና ፌደራሉ የሚለያዩበትን ነጥብ አናገኝም፡፡ አንድ ክልል የራሱ እቅድ ማውጣት ቢችልም አሁን ባለው አሰራር ይሄ የለም፡፡ አንድ ክልል ስንት ት/ቤቶች ስንት የጤና ኬላ እንደሚያስፈልጉት አያውቅም። ያንን የሚያቅድለት ማዕከላዊ መንግሥት ነው፡፡ ይሄ ከፌደራሊዝም ፅንሠ ሀሳብ ጋር ይቃረናል፡፡ የፓርቲያችን የፌደራል ስርአት ግን እነዚህን በትክክል አቃንቶ የሚተገብር ነው፡፡
በአንድ በኩል አዲስ አበባ የኦሮሚያ ክልል ዋና ከተማም ነች። ከዚህ ቀደምም የኦሮሚያ ነች የሚል ጥያቄ ተነስቷል፡፡ በሌላ በኩል የኦሮሞ ነች የምትባለው ይህቺ ከተማ ከሌሎች የኦሮሚያ ከተሞች ጋር እንድትተሳሰር መንግስት ያወጣውን እቅድ ትቃወማላችሁ፡፡ እነዚህን ነገሮች እንዴት ነው የምታስታርቁት?
 እኛ ጥያቄያችን ህገ መንግሥቱን መሰረት ያደረገ ነው፡፡ ህገ መንግሥቱ ላይ ኦሮሚያ ከፌደራል መንግሥቱ መቀመጫ አዲስ አበባ ልዩ ጥቅም ታገኛለች፤ ዝርዝሩም በሌላ ህግ ይገለፃል የሚል አለ፡፡ ዝርዝሩ ግን ሳይገለፅ 20 ዓመት አለፈ፡፡ በኦሮሚኛ ቋንቋ የሚያስተምሩ ት/ቤቶችም የሉም፡፡ አሁን ያለው አሰራር ህጎች የሚተረጎሙት በባለስልጣናቱ ምቾት ላይ ተመስርተው ነው፡፡ ለራሳቸው እስካልጠቀመ ድረስ በህገ መንግስቱ እንደተጠቀሰው፤ ከከተማዋ የኦሮሞ  ህዝብ የተለየ ጥቅም እንዲያገኝ አልፈለጉም፡፡ በተቃራኒው ግን የአዲስ አበባን ቆሻሻና ሌሎች ችግሮች የመሸከሙ ኃላፊነት ያለው ኦሮሚያ  ላይ ነው፡፡
በ1997 ምርጫ ጊዜ ኢህአዴግ አዲስ አበባን ሌላ አካል የሚረከብ ስለመሰለው፣ የኦሮሚያ መቀመጫ አዲስ አበባ እንዲመስል አደረገ። በዚያ ምክንያት በፊት የተከለከሉ ጥቅሞችን ክልሉ እንዲያገኝ አንድ ፕሮፖዛል እንዲሰራ አደረገ፡፡ አዲስ አበባ ከምታገኘው ገቢ ምን ያህሉ ወደ ኦሮሚያ መግባት እንዳለበት፣ በኬላችን ላይ ቀረጥ እንዲከፈልና ኦሮሚያ ገንዘብ እንድታገኝ፣ በአዲስ አበባ ውስጥ ካሉት የምክር ቤት መቀመጫ ውስጥ ደግሞ ኦሮሚያ ያለ ውድድር የተወሰኑ መቀመጫዎችን እንድታገኝ የመሳሰሉ ፕሮፖዛሎች ቀርበው ነበር፡፡ የተባለው ድርጅት ከተማዋን ሳይረከብ ሲቀርና መልሶ ኢህአዴግ ከተማዋን ሲይዝ የተዘጋጀውን ፕሮፖዛል  መልሶ ጣሉት አላቸው፡፡ ስለዚህ ኦሮሚያ በፊትም ማግኘት የነበረበትን ጥቅም አላገኘም፤ ይባስ ብሎም አዲስ አበባ ውስጥ ያለው መሬት በማለቁ ሌላ ጥቅም ፍለጋ ወደ ኦሮሚያ መሬት እጃቸውን መዘርጋት ጀመሩ ማለት ነው፡፡
ፓርቲያችሁ በአዲስ አበባ ጉዳይ ያለው አቋም ምንድን ነው?
በቻርተሩ ጊዜ በተደረገው ስምምነት መሰረት፤ አዲስ አበባ ሙሉ በሙሉ የምትገኘው በኦሮሚያ ውስጥ ነው በሚል ነው የታለፈው፡፡ የኦሮሚያ ናት የሚል አልተቀመጠም፡፡ ነገር ግን በጣም ወሳኝ የሆነ ቁጥር በዚህች ከተማ እንዳለ ይታወቃል፡፡ መጀመሪያም ትንሽ የኦሮሚያ መንግስት ከመሆን ጀምራ ነው አሁን ወዳለችበት ደረጃ ያደገችው፡፡ ይህ እድገቷ ዛሬም እንዲቀጥል እንፈልጋለን፡፡ እዚህ ውስጥ የኦሮሞ ፍላጎትም እንዲንፀባረቅ እንፈልጋለን፡፡ የሌሎችን ህዝቦች ጥቅም በማይጎዳ መንገድ አንዳንድ የኦሮሞ ተቋሞች እንዲከፈቱ እንፈልጋለን፡፡ ነገር ግን አሁን ከያዘችው ወሰን አልፋ ወደ የትኛውም የኦሮሚያ ክልል የመስፋፋት ህጋዊ የሆነ መሰረት ስለሌ ያንን እንቃወማለን፡፡
ማስተር ፕላኑ መሰሪ ነው የምንለው፣ መሬትን የመሻማትና የመቀራመት ጉዳይ ስለሆነ ነው፡፡ ማንነትን በማጥፋት ሌሎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ስለሆነ ነው፡፡
ፕላኑ ማንነትን ያጠፋል የምትሉትንና ሌሎች ለተቃውሞ መነሻ የሆኗችሁን ጉዳዮች በተጨባጭ ማስረጃ አስደግፋችሁ ማቅረብ ትችላላችሁ?
አንደኛ ነገር ፕላኑ ሉአላዊነትን ይፃረራል፡፡ አንድ ገበሬ ከመሬቴ አልነሳም ሲል የግድ ትነሳለህ ማለት የመብት መደፈር ነው፡፡ የሰብአዊ መብት ጥሰት ነው። ሌላ ሙያ የሌለው ካፒታሉ መሬት ብቻ የሆነን ህዝብ ማፈናቀል፣ የኢኮኖሚ መሰረቱን ማሳጣት ብቻ ሳይሆን ማንነቱን፣ ቋንቋውን፣ ባህሉን የሚያሳጣ ነው፡፡ በእነዚህ አካባቢ የዛሬ 25 ዓመት ኦሮሚኛ ሲነገር ነበር፡፡ ዛሬ አንድ የኦሮሚኛ ቋንቋ የማይሰማባቸው ቦታዎች ሆነዋል፡፡ በዚህ ነው ማንነትን ያጠፋል የምንለው፡፡ ህዝቦች ማንነታቸውን እንደጠበቁ አብሮ በመኖር እናምናለን፤ ነገር ግን አንዱ የአንዱን ማንነት እያጠፋ አይሆንም፡፡ አሁንም ይሄን አካሄድ መቃወማችንን እንቀጥላለን፡፡
መንግሥት አሜሪካንን በመሳሰሉ የሰለጠኑ ሀገራት የክልል  ከተሞችን በእንዲህ ያለው ፕላን የማስተሳሰሩ ጉዳይ የተለመደ መሆኑን በመጥቀስ፣ የከተሞች በልማት መተሳሰር ምን ክፋት አለው ይላል፡፡ ለዚህ የናንተ ምላሽ ምንድነው?
 አንደኛ ነገር የአሜሪካንን ተሞክሮ እዚህ የምናመጣ ከሆነ አይሰራም፡፡ ህዝቡ ተመሳሳይ አይደለም፡፡ ተመሳሳይ የኑሮ ደረጃ ላይ ያለ ህዝብ፣ ከሞላ ጎደል አንድ ቋንቋ የሚናገር ህዝብ፣ ተመሳሳይ ስነ ልቦና ያለውና ቢቀላቀል ማንነቱ በምንም አይነት ሁኔታ የማይበረዝስ ነው የአሜሪካው፡፡ በኛ ሁኔታ ግን መጀመሪያውኑ ፌደራል ስርአቱ መሰረት አድርጎ የተነሳው የተለያዩ አይነት ህዝቦችን ነው፡፡ የተለያየ ቋንቋ፣ ባህልና ስነ ልቦና ያላቸው ህዝቦች ተጋርተው የሚኖሩባት ሀገር በመሆኑና እያንዳንዱ ህዝብ ማንነቱን፣ ቋንቋና ባህሉን የሚፈልግ በመሆኑ ነው ፌደራሊዝም ያስፈለገው፡፡
አሁን በተኬደበት አቅጣጫ ግን እነዚህ ከተሞች በምን ቋንቋ ሊጠቀሙ ነው? አስተዳደሩስ ምን ይሆናል? አሁን ለምሳሌ ቡራዩና ላይ ት/ቤቶች ቢሰሩ፣ መሰረተ ልማቶች ቢስፋፉ እኛ እንደግፋለን ነገር ግን የኛ መሰረታዊ ጥያቄ ለቡራዩ አዲስ አበባ ልታቅድ አትችልም ነው፡፡ ፌደራል መንግሥትም ቢሆን ለከተሞች የማቀድ ስልጣን በህገ መንግሥቱ አልተሰጠውመ፡፡
ይሄ በፌደራል መንግሥት የሥልጣን እርከን ውስጥ አይደለም፡፡ እንደዛ ከሆነ ከተሞች ለምን የራሳቸው አስተዳደር አስፈለጋቸው?
የኛ አጠቃላይ አቋም አንዱን ካንዱ መቀላቀል የሚለው ለምዕራባውያን እንጂ እንደኛ አይነት የተለያየ ቋንቋ፣ ባህል ያለው ማህበረሰብ ውስጥ ሊሰራ አይችልም ነው፡፡ መንግሥት በፌደራል ደረጃ የሚሰራቸው ሀገራዊ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች አሁንም መሰራት አለባቸው ነገር ግን ከተማ ነክ የሆኑትን ከተሞች አንዱ ካንዱ እየተቀበለ ነው መስራት ያለበት፡፡
ለምሳሌ የአሜሪካ ከተሞች እነ ዋሽንግተን ዲሲን ስንመለከት፣ ዲሲ ራሷ የተመሰረተችው ከተለያዩ ስቴቶች በተቆራረጠ መሬት ላይ ነው፡፡ በኋላ ግን አንዱ ስቴት የተወሰነን የዲሲ መሬት የራሴ ነው ብሎ ወስዷል፡፡ እርግጥ ነው አሁን በዲሲና በቨርጂኒያ መካከል ልዩነት ላይታይ ይችላል፤ ነገር ግን ሁለቱ ከተሞች የተሰመረ ድንበርና የየራሳቸው አስተዳደር አላቸው፡፡
ወደኛ ሁኔታ ስንመጣ ግን አሁን የአዲስ አበባ ኮንዶሞኒየም ቤቶች የሚሰሩት የኦሮሚያ ግዛት ውስጥ ነው፡፡ ይሄን የኦሮሚያ ክልል አያውቀውም። ገላን ላይ ያወጣውን ውሃ የአዲስ አበባ ህዝብ ሲጠጣ፣ ገላን ላይ ያለው ህዝብ ግን ውሃ እየተጠማ ነው ያለው፡፡ ስለዚህ ይሄ የተቀናጀ አይደለም፡፡ አንዱን ወገን ጎድቶ አንዱን የሚጠቅም አይነት ነው፡፡ ይሄን ዓይነት በህዝቦች መካከል ያለውን አብሮ የመኖር ባህል የሚንድ እንቅስቃሴ መቆም አለበት እንላለን፡፡ በኦሮሚያ ውስጥ ያሉ ማናቸውም ህዝቦች፤ ከኦሮሞ ህዝብ እኩል መብታቸው ሊከበርላቸው እንደሚገባ እናምናለን፡፡ የኛ ጥያቄ ወደ እውነተኛው ፌደራሊዝም እንመለስ ነው፡፡   

Read 13536 times