Saturday, 10 October 2015 15:54

የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ በኢትዮጵያ ስጋ ላይ የጣለችውን ማዕቀብ አነሳች

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ኢትዮጵያ አምና ወደዚያው ከላከችው ስጋ 58.8 ሚ ዶላር አግኝታለች
     የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ የኢትዮጵያ የስጋ ምርት ወደ ግዛቷ እንዳይገባ ከአንድ ሳምንት በፊት ጥላው የነበረችውን ማዕቀብ ማንሳቷን ተርኪሽ ዊክሊ ድረገጽ ትናንት ዘገበ፡፡
ከሳምንት በፊት ከኢትዮጵያ ሰባት ስጋ ላኪ ኩባንያዎች ወደ አገሪቱ ከገባው 36 ቶን የበግ ስጋ ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ችግር ተከትሎ አገሪቱ የኢትዮጵያ የስጋ ምርት ወደ ግዛቷ እንዳይገባ ገደብ ጥላ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ከሚመለከታቸው የኢትዮጵያ መንግስት አካላት ጋር በመነጋገር ችግሩን መፍታት መቻሉን ገልጧል፡፡
ይህን ተከትሎም የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ የኢትዮጵያ የስጋ ምርት ወደ ግዛቷ እንዳይገባ የጣለችውን ማዕቀብ ማንሳቷንና አገሪቱ ያሳለፈችው ውሳኔ በዘርፉ የተሰማሩ ኢትዮጵያውያንን እንዳስደሰተ ዘገባው አስረድቷል፡፡
የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ የኢትዮጵያን የስጋ ምርት በስፋት በመግዛት ቀዳሚዋ አገር እንደሆነችና ኢትዮጵያ ወደ ተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ከምትልከው የምግብ ኤክስፖርት ምርት በአመት በአማካይ 30 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እንደምታገኝም ገልጧል፡፡
ኢትዮጵያ ባለፈው አመት ወደ የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ከላከችው 11.692 ቶን የስጋ ምርት 58.8 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷንም ዘገባው አክሎ አስታውሷል፡፡

Read 2097 times