Monday, 31 August 2015 09:11

የግጥም ጥግ

Written by 
Rate this item
(10 votes)

አረማሞ
ተደባልቆ በቃይ
ሲናር አረማም
ሲዘራ ካልዘሩ
ምርጥ ዘር አክሞ
ገለባ ነው ትርፉ
ቀን ቆጥሮ ለከርሞ፡፡
ሙግት
ያኮረፈ ሌሊት
…መንጋቱን የረሳ
ውስጤ እያደመጠ
…የነፍሴን ጠባሳ
እርምጃ ውልክፍክፍ
…ጉዞውም የአንካሳ
የጨለማ ሙግት
…የንጋት ወቀሳ፡፡
ጀንበሩ ወልደዮሐንስ
(ከኒዮርክ ቡፋሎ)
* * *
“አንተ” - ማለት!...
“አንተ” ማለት፡-
ብዙ ነህ!
ብዙ - ብዙ! … የብዙ - ብዙ!
“አንተ” ማለት ….
አገር ነህ፣
አገር ከነጉዝጓዙ፡፡…
ያገር ጉዝጓዙ…
አቤትና አቤት … አቤት! ብዛቱ፡…
ጂባው፣ አጐዛው - ጀንዴው - ቁርበቱ፡፡…
ተራራው - ሸለቆው - ዱሩ፣
እንኮይ - መስኩ፣
መብሰክሰኩ…፤
እሾህ አሜኬላው - ቆንጥሩ…
ባንድ ሌማት
እሬት!
ምሬት!
የአጋም ፍሬው --- ጣዝማ ማሩ፣
ደግሞም፡-
አድባር! አውጋር! … ያለ መጣፍ፣
አማኝ - እምነት
በመጣፍም
ያለ መጣፍ፡፡…
መቼም - ሰው “አገር ነውና”
አገርም “ሰብዓ ምርቱ”
ታሪክ - ቋንቋ - ባህል - ቀኖናውና
- ትውፊቱ፣
እሱ ነው! የማንነትህ እትብቱ፡፡…
ከእኒህ - መነቀል…
ማለት፡-
ከሥር - መመንገል!
ካናት - መቃጠል!
ከእግር - መመንቀል!
ማለት ነው፣
አገር እንደ ሰው!!
ሰማህ!?
(ወንድዬ ዓሊ)

Read 3270 times