Monday, 31 August 2015 08:44

የአዲስ አበባ ሰፈሮች የአድራሻና አቅጣጫ መጠቆሚያ ሊዘረጋላቸው ነው

Written by 
Rate this item
(4 votes)

     በመዲናዋ ባሉ ክፍለ ከተሞች በተመረጡ 10 ወረዳዎች ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ዘመናዊ የሰፈሮቹ የአድራሻና አቅጣጫ መጠቆሚያ ስርአት ሊዘረጋላቸው እንደሆነ እያካሄደ መሆኑን የአዲስ አበባ አስተዳደር የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ አስታወቀ፡፡
የቢሮው የኮሙኒኬሽን የሥራ ሂደት መሪ አቶ ማርቆስ አለማየሁ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ ዝርጋታው አቅጣጫ ጠቋሚ ምልክቶችን፣ ብሎክና የቤት ቁጥር ታፔላዎችን ያካትታል፡፡ የአድራሻ ስርዓቱ በዋናነት ለፖስታ አገልግሎት፣ የእሳት አደጋ መኪኖች ፈጥነው እንዲደርሱ እንዲሁም የአምቡላንስ አገልግሎት ለማግኘትና ወንጀልን ለመከላከል ወሳኝ መሳሪያ ይሆናል ተብሏል፡፡
ስርአቱን ለመዘርጋትም ካርታ የማዘጋጀት ስራ ሲከናወን የቆየ ሲሆን ታፔላዎቹ ደረጃቸውን ጠብቀው እንዲመረቱ ከብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን፣ ከህብረት ማኑፋክቸሪንግ ማሽን ኢንዱስትሪ ጋር የ40 ሚሊየን ብር ውል መገባቱን የጠቆሙት አቶ ማርቆስ፤ አሁን የስራው የመጀመሪያ ምዕራፍ ወደ ሆነው ምልክት ተከላ ተሸጋግሮ ስራው እየተገባደደ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
ከአስሩም ክፍለ ከተሞች አንድ አንድ ወረዳ የተመረጠ ሲሆን ለአብነትም ጉለሌ ወረዳ 10፣ የካ ወረዳ 13፣ ቂርቆስ ወረዳ 2 እና አዲስ ከተማ ወረዳ 9ን ጠቅሰዋል፡፡ የእነዚህ ወረዳዎች ተከላ እንደተጠናቀቀም 30 የሚሆኑ ወረዳዎች ላይ ወደ ተግባር ለመግባት በዝግጅት ላይ ነን ብለዋል - የሥራ ሂደት መሪው፡፡

Read 4586 times