Print this page
Saturday, 15 August 2015 15:45

“በኦሮሚያ ክልል ከ70 በላይ አርሶ አደሮች የብሔር ጥቃት ደርሶባቸዋል” ሰመጉ

Written by 
Rate this item
(12 votes)

በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ኖኖ ወረዳ ነዋሪ የሆኑ ከ70 በላይ አማርኛ ተናጋሪ ገበሬዎች፣ ቤት ንብረታቸው ተቃጥሎ ከመኖሪያ ቀዬአቸው መፈናቀላቸውን የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ (ሰመጉ) በሪፖርቱ አመለከተ፡፡ የአንድ ሰው ሕይወት መጥፋቱንም አረጋግጫለሁ፤ ብሏል፡፡
ሰመጉ ጉዳዩን ሲመረምር መክረሙን ጠቁሞ፣ “ብሔር ተኮር ማፈናቀልና እንግልት በአስቸኳይ ይቁም” በሚል ርዕስ ይፋ ባደረገው 136ኛ ሪፖርቱ የወረዳው የጸጥታ ሓላፊዎችና ባለሥልጣናት የብሔር ግጭቱን መቀስቀሳቸውን አስታውቋል፡፡
እንደ ሪፖርቱ፣ የወረዳው ባለስልጣናትና የፀጥታ ኃላፊዎች አርሶ አደሮቹን፣ “እናንተ የዚህ የአካባቢው ተወላጅ ሳትሆኑ ሀብት እያፈራችሁ የአካባቢው ተወላጆች ግን ከእናንተ ያነሰ ገቢ ነው ያላቸው፤ … ይህን ገቢ ያገኛችሁት በኛ መሬት ነው፤ የክልሉ ተወላጆች ባለመሆናችሁ ክልሉን ለቃችሁ ውጡ፤” በማለት በተለያዩ ጊዜያት ንብረታቸውን በመንጠቅና ለእስራት በመዳረግ እንግልት ሲፈፅሙባቸው ቆይተዋል፡፡ በተለይ መጋቢት 27 ቀን 2007 ዓ.ም አንድ የአካባቢው ተወላጅ ተገድሎ መገኘቱን ተከትሎ የወረዳው የፀጥታ ኃላፊ “ግድያው የተፈፀመው በአማራ ብሄር ተወላጆች ነው” በማለታቸው ግጭት ተቀስቅሶ፤  ሚያዚያ 9 ቀን 2007 ዓ.ም 85 አርሶ አደሮች ለእስራት መዳረጋቸውን፣ የአማራ ተወላጅ አርሶ አደሮች መኖሪያ ቤቶች እንዲቃጠሉ መደረጉን እንዲሁም የታሠሩትን የነዳጅ በሚል 300 ብር ከእያንዳንዳቸው በመቀበል እንደተለቀቁ ሰመጉ አጣርቻለሁ፤ ብሏል፡፡   በግጭቱ የአንድ ሰው ሕይወት ሲጠፋ 10 ሰዎች ላይ ቀላልና ከባድ የአካል ጉዳት መድረሱን፣ 99 የሳር ክዳን ቤቶችና 25 የቆርቆሮ ቤቶች በእሳት ተቃጥለው መውደማቸውን የዘረዘረው ሰመጉ፤ መኖሪያ ቤታቸው ለተቃጠለበቸውና በተለያዩ ቦታዎች ተበታትነው ለሚገኙ ዜጐች አስቸኳይ ሰብአዊ እርዳታ እንዲያገኙ ጠይቋል፡፡ መንግሥትም ለተፈጸመው የሰብአዊ መብት ጥሰት፣ የተጠናና የማያዳግም የመፍትሔ ርምጃ ከሕዝብ ጋር በመመካከር እንዲወሰድ የሰብአዊ መብቶች ጉባኤ አመልክቷል፡፡ 

Read 5518 times
Administrator

Latest from Administrator