Monday, 20 April 2015 15:34

የኢትዮጵያዊያን ስደተኞች መከራ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

በደቡብ አፍሪካ፣ በየመን፣ በጣሊያን
        ከምስራቅና ከምዕራብ አቅጣጫዎች የምንሰማው መረጃና ዘገባ፣ ከደቡብም ከሰሜንም የምናየው የፎቶና የቪዲዮ መረጃ፣ የግርግርና የትርምስ ወሬ ሆኗል። ቀደም ሲል በሳዑዲ አረቢያና በደቡብ ሱዳን፣ ዘንድሮ ደግሞ በተለይ ሰሞኑን በደቡብ አፍሪካ፣ በየመን፣ እንዲሁም ከሊቢያ ወደ ጣሊያን በሚያሻግረው የሜዲትራኒያን ባሕር ላይ የተከሰቱ ቀውሶችን ተመልክታችኋል። በደቡብ አፍሪካ ማክሰኞ እለት በተቀሰቀሰው የጅምላ ዘረኛ ጥቃት፣ ኢትዮጵያዊያን ሰለባ ሆነዋል። የጅምላ ጥቃቱ፤ በአስር ሺ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ፣ ከተለያዩ የአፍሪካ አገራት የመጡ ወደ 3 ሚሊዮን ስደተኞችን ለአደጋ አጋልጧል። በዚሁ ሳምንት፣ በጦርነት በታመሰችው ሊቢያ በኩል አስር ሺ ስደተኞች ወደ አውሮፓ ለመግባት ሲሞክሩ፣ አንድ ጀልባ ተገልብጣ ከአራት መቶ በላይ ስደተኞች ሞተዋል። ይህም ብቻ አይደለም። የጎሳ ግጭትና ሃይማኖታዊ ጦርነት ባመሳቀላት የመን ውስጥ የሚገኙ በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን፣ መግቢያ መውጪያ አጥተዋል።
እንደ ድሮ ቢሆን፣ በሌሎች አገራት የሚፈጠሩ ቀውሶችና ግጭቶች፣ በቀጥታ ሕይወታችንን የመንካት ቅርበት ይኖራቸዋል ብለን ስለማንገምት ያን ያህልም ባላስጨነቁን ነበር። በአፍሪካ የሰሜንና የደቡብ ጠረፎች፣ በአረብና በአውሮፓ አገራት ድንበሮች ላይ የሚፈጠሩ ችግሮች፣ ከሕይወታችን ጋር የቅርብ ግንኙነት ይኖራቸዋል ብለን ካላሰብን ለምን ያስጨንቀናል? በዚያ ላይ፣ እንደ ድሮ ቢሆን፣ ስለ ቀውሶቹ በዝርዝር የምናውቅበት ሰፊ እድል ባላገኘን! አንድ ደቂቃ ከማትሞላ የዜና ቁራጭና ከተባራሪ ወሬ ያለፈ መረጃ አናገኝም ነበር።
ዛሬ ግን እንደድሮ አይደለም። እስከተጠቀምንበት ድረስ፣ የመረጃ ባዕድ ወይም የአፈና ሰለባ የማንሆንበት እድል ተፈጥሯል - የሳተላይት ዲሽና ኢንተርኔት በመሳሰሉ የሳይንስና የቴክኖሎጂ ውጤቶች። የቢዝነስ ድርጅቶች ደግሞ፣ ቴክኖሎጂውን ወደ ምርትና ወደ ንግድ አሳድገው፣ ለአለም አዳርሰውታል። የየትኛውም ሃይማኖትና እምነት ተከታይ አልያም የየትኛውም አገርና ብሔር ብሔረሰብ ተወላጅ ብንሆን ለውጥ የለውም። አፕል እና ሳምሰንግ የመሳሰሉ የሞባይል ቀፎ አምራች ኩባንያዎች፤ እንዲሁም ጉግል፣ ፌስቡክ እና ዩቱብ የመሳሰሉ የቢዝነስ ኩባንያዎች፤ ቴክኖሎጂው እጃችን ውስጥ እንዲገባ አድርገዋል። ቴክኖሎጂውን የመጠቀም ምርጫና ብቃት፣ የግል ምርጫችን እንዲሆን ሰፊ እድል ከፍተውልናል። አይገርምም? በጥቂት ዓመታት ውስጥ የመጣ ተዓምረኛ ለውጥ ነው። ምን ለማለት ፈልጌ ነው?
አንደኛ፤ በጭፍን እምነት፣ በጭፍን “ባህል” እና በጭፍን ፕሮፖጋንዳ ምትክ፤ ለአእምሮ ክብር የሚሰጥ ሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና የመረጃ ነፃነት ሲስፋፋ.... ሁለተኛ፤ በመንግስት ገናና የኢኮኖሚ ቁጥጥር፣ በድጎማና በጥገኝነት ፋንታ፤ ለብልፅግና ክብር የሚሰጥ ቢዝነስ፣ ንግድና ትርፋማነት ሲያድግ... ሦስተኛ፤ በጅምላ ፍረጃ፣ በቡድናዊነትና በብሔረተኝነት (በዘረኝነት) ምትክ የእያንዳንዱ ሰው ማንነት እንደየግለሰቡ ብቃት፣ ባህርይና ሰብእና የመመዘን ፍትሃዊነትና የእኔነት ክብር ሲስፋፋ፣ የሰው ልጅ ድንቅ ተዓምሮችን ይሰራል። እነዚህ ሦስቱ ነጥቦች (ሳይንስ፣ ካፒታሊዝም እና የግል ማንነት) መሰረታዊዎቹ የስልጣኔ እሴቶች መሆናቸውን ልብ በሉ።
ለነገሩ፤ በየአቅጣጫው የምናየው የኢትዮጵያዊያን ስደትም፤ ከእነዚሁ ሦስት የስልጣኔ እሴቶች ጋር የተቆራኘ ነው። የዚህን ወይም የዚያን ሃይማኖት እምነትንና ቀኖና ፈልገው አይደለም የሚሰደዱት። የአገር ወይም የብሔር ብሔረሰብ ጥንታዊ ባህልን፣ ቋንቋንና የጅምላ ማንነትን ፍለጋ አይደለም የሚሰደዱት። ለመንግስት ቁጥጥር ለመገዛት፣ አልያም የመንግስት ጥገኛ ሆነው ድጎማ ለመቀበል ጓጉተው፣ ወይም የሃብት ልዩነት የሌለበት አለም ናፍቋቸው አይደለም የሚሰደዱት። በተቃራኒው፤ ለሃይማኖትና ለእምነት ልዩነት ቦታ ባለመስጠት ነው የሚሰደዱት። የጥንታዊ ባህልና የተወላጅነት ልዩነቶችን ወደ ጎን በማለት ነው የሚሰደዱት። ለመንግስት ድጎማና ለሃብት ክፍፍል ቦታ ባለመስጠትም ነው የሚሰደዱት።
ይልቅስ፣ በሃይማኖት ላይ ሳይሆን በአእምሯቸው ላይ ተማምነው፣ በተወላጅነት ላይ ሳይሆን በግል ብቃታቸው ላይ ተማምነው፣ በመንግስት ድጎማ ሳይሆን በራሳቸው ጥረት ሃብት አፍርተው ሕይወታቸውን ለማሻሻል ነው የሚሰደዱት - የመበልፀግ መልካም ምኞታቸውን እውን ለማድረግ። በአጭሩ፤ ሦስቱ የስልጣኔ እሴቶችን የተላበሱ ናቸው። ነገር ግን፣ የስልጣኔ ፊታውራሪዎች ናቸው ማለት አይደለም። በጭራሽ። እንደአብዛኛው ሰው ሁሉ፣ ስደተኞችም በአብዛኛው ከስልጣኔ እሴቶች ጋር፣ ፀረ ስልጣኔ አዝማሚያዎችንም አዋህደው የያዙ ናቸው። እንዴት በሉ።
ዘመኑ የስልጣኔ ዘመን አይደለም። ከስልጣኔ እሴቶች በተቃራኒ፣ ሦስት የስልጣኔ እንቅፋቶች በዓለም ዙሪያ ያንሰራሩ የመጡበት ዘመን ላይ ነው የምንገኘው - የጭፍን እምነት ስብከትን የሚያራግብ የሃይማኖት አክራሪነት፣ የሃብት ክፍፍል ዲስኩር የሚዘወተርበት የመንግስት ገናናነት፣ ጥንታዊ ባህልን በማምለክ የሚለፈፍበት ዘረኝነት፣ እንደ አሸን ሲፈሉ የምናየው ለምን ሆነና! በእነዚህ ሦስት ፀረስልጣኔ አቅጣጮች ምክንያት የሚከሰቱ ቀውሶችን ነው በአለም ዙሪያ የምናየው - (የአውሮፓ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ቀውስ፣ የመካከለኛው ምስራቅ ሃይማኖታዊ ሽብርና ጦርነት፣ የአፍሪካ የዘረኝነትና የጎሳ ትርምስ)። ኢትዮጵያውያን ስደተኞችም በየቦታው ሰለባ እየሆኑ ነው።  
ለነገሩ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየባሰበት ቢመጣም፣ አምናም ተመሳሳይ ነገሮችን እንዳየን የምንረሳው አይመስለኝም። “የአገርን ሃብት ትቀራመታላችሁ፤ የስራ እድልን ታጣብባላችሁ፤ ሃይማኖትን የሚቃረን ባህርይ ታስፋፋላችሁ” በሚል፣ ከመቶ ሺ በላይ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ከሳዑዲ ዓረቢያ ሲባረሩ አይተናል። በጥንታዊ የባህል ልዩነትና በጎሳ ተወላጅነት የተቧደኑ የደቡብ ሱዳን ታጣቂ ጎራዎች ከፈጠሩት ጦርነት ጋር በተያያዘም፣ “መጤዎች የአገራችንን ወይም የጎሳችንን ሃብት ይመዘብራሉ” በሚል በርካታ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ለአደጋ መጋለጣቸውን እናስታውሳለን። ዘንድሮም ተመሳሳይ ነው።
ከላይ እስከ ታች በጦርነት እየነደደች ባለችው የመን ውስጥ፤ በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ተስፋቸው ምን ሊሆን እንደሚችል አስቡት። እንደ ሌላው ዓለም በኢኮኖሚ የተቃወሰችው የመን፣ አንደኛውን ለይቶላት በጎሳ ግጭትና እና በሃይማኖታዊ ጦርነት ስትታመስ ይሄውና ዓመት ሊሆናት ነው። እንዲያም ሆኖ፣ በዓመት ውስጥ ከ60ሺ በላይ ኢትዮጵያዊያን ባህር አቋርጠው የመን ገብተዋል። የአገሪቱ ጦርነት ከመርገብ ይልቅ እየተባባሰ ከመምጣቱም በተጨማሪ፣ ውስጥ ውስጡን ሺዓ እና ሱኒ በሚል ሲፎካከሩ የቆዩት የኢራንና የሳዑዲ ዓረቢያ ጎራዎች አሁን በይፋ ገብተውበታል። ኢራን የጦር መርከቦችን ስታሰማራ፣ ሳዑዲ በበኩሏ በጦር አውሮፕላኖች የድብደባ ዘመቻ ስታካሂድ ሰንብታለች። እንዲያም ሆኖ፣ የዩኤን መረጃ እንደሚያመለክተው በመጋቢት ወር ብቻ ከ3ሺ በላይ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች የመን ገብተዋል። ያሳዝናል፤ ግራ ያጋባል። ግን አዲስ ክስተት ካለመሆኑም በተጨማሪ፤ እልባትና መፍትሄ የሚገኝለት አይመስልም።
በደቡብ አፍሪካ፣ የኢትዮጵያዊያን ስደተኞችን ሕይወት የቀጠፈው የሰሞኑ ዘረኛ ጥቃትም፣ ድንገተኛ አዲስ ክስተት አይደለም። ለአመታት ሲንተከተኩ በዘለቁ ፀረ ስደተኛ ስሜቶች፣ በተለይ ደግሞ ከጥቅምት ወር ጀምሮ በየአካባቢው ሲቆሰቆሱ በቆዩ ጥቃቶች ምክንያት የተጨነቁ በርካታ የረድኤት ድርጅቶች፣ “ይሄ ነገር አደገኛ ነው” እያሉ ለማስጠንቀቅና ለመምከር ሲሞክሩ ከርመዋል። አንዳንዶቹም፣ “የተወሰኑ ስደተኞች ወንጀል ስለፈፀሙ፣ ስደተኞችን በጅምላ አትጥሉ። እያንዳንዱን ስደተኛ በግል ተግባሩ እንዳኘው። በርካታ ስደተኞች በራሳቸው የግል ጥረት ሃብት በማፍራትና ሃብት በመፍጠር ለአገሪቱ ኢኮኖሚ ጠቃሚ አስተዋፅኦ ያበረክታሉ” በማለት መከራከሪያ ለማቅረብና ለማሳመን ተጣጥረዋል። በተጨባጭ መረጃ የተደገፈ ጥናታዊ ፊልም፣ ዘገባ እና መግለጫ በማሰራጨት የጥላቻ ስሜቶችንና የጅምላ ፍረጃን ለማርገብ ደፋ ቀና ብለዋል። ምን ያደርጋል? ብዙዎቹ ሰሚ አላገኙም። ሰሚ ያገኙትም፣ የሚያምናቸው አላገኙም። ጥረታቸውና ሙከራቸው፣ ከመነሻው ከንቱ እንደሆነ አላወቁም። ድንገት ተነስተው፤ “ስለ ተጨባጭ መረጃ፣ ስለ ሃብት ፈጠራ፣ ስለ ግል ማንነት” የሚያወሩት ነገር ውጤት አላስገኘም። ለምን ቢባል፤ አብዛኞቹ የረድኤት ድርጅቶችን ተመልከቷቸው።
ከፊሎቹ የእርዳታ ድርጅቶች፣ የምዕራባዊያንን የሳይንስና የስልጣኔ እመርታን የሚያወግዙ የሃይማኖት ሰባኪዎች ናቸው። በአንድ በኩል ጭፍን እምነትን እየሰበኩ፣ በሌላ በኩል ደግሞ “እባካችሁ ለተጨባጭ መረጃ ክብር በመስጠት ከጭፍን ስሜታዊነት መታቀብ ያስፈልጋል” ቢናገሩ ማን ይሰማቸዋል? ከንቱ ንግግር ነው።
ከፊሎቹ የእርዳታ ድርጅቶች ደግሞ፣ በ“ሃብት ፈጠራ” ላይ ሳይሆን በ“ሃብት ክፍፍል” ላይ የተመሰረተ ሶሻሊስታዊ የኢኮኖሚ አስተሳሰብ በማንገብ የምዕራባዊያንን የካፒታሊዝም ዝንባሌ የሚያጥላሉ ናቸው።
“የሆነ የአገር ሃብት አለ። ዋናው ቁምነገር፣ ያንን ሃብት የማከፋፈል ጥያቄ ነው” ብለው ያምናሉ። ሃብት ማፍራትንና ሃብት መፍጠርን እንደቁምነገር ስለማይቆጥሩትም ነው፤ ብዙዎቹ የረድኤት ድርጅቶች ባለሃብቶችንና የቢዝነስ ድርጅቶችን ሲያወግዙ የምንሰማው። “የሆኑ ሰዎች የሚበለፅጉት፣ ሃብት ስለሚያፈሩ ሳይሆን፣ ከአገር ሃብት ውስጥ ከድርሻቸው የበለጠ ሸምጥጠው ስለሚወስዱ ነው” ብለው ያምናሉ። እንደዚህ አይነት እምነት የያዘ ሰው ስደተኞችን መጥላቱ የግድ ነው። ስደተኞችን ባየ ቁጥር፤ “የአገርን ሃብት የሚሸመጥጡ ተጨማሪ እጆች መጡብኝ፤ ድርሻዬን ይቀራመቱብኛል” ብሎ መስጋቱ አይቀርማ። እና፣ እለት በእለት “ስለ ሃብት ክፍፍል” የሚደሰኩሩ የእርዳታ ድርጅቶች፣ ድንገት ተነስተው፣ “ስደተኞች ሃብት ያፈራሉ” የሚል አንድ ጥናታዊ ፊልም ቢሰሩ ቅንጣት ለውጥ አያመጣም።
የባህል ጥበቃን የሚሰብኩ ሌሎቹ የእርዳታ ድርጅቶችም እንዲሁ፣ የምዕራባዊያንን ዝንባሌ ያወግዛሉ - በባህል ወራሪነት ወይም በባህል የለሽነት እየወነጀሉ። “የሰው ማንነት የሚወሰነው በአገሩ ወይም በብሄረሰቡ ባህል ነው” እያሉ ዘወትር የጅምላ ማንነትን የሚሰብኩት እነዚሁ የረድኤት ድርጅቶች፤ ድንገት አንድ ቀን ተነስተው “ከሌላ አገር የመጡ ስደተኞችን አትጥሉ፤ በጅምላ አትፈርጁ” የሚል ቁራጭ መግለጫ ቢያሰራጩ፣ ኢምንት ለውጥ አያመጡም።
ታዲያ፣ ቀውሱ፣ ግጭቱ፣ አደጋው በየአመቱ እየተደጋገመና እየተባባሰ መምጣቱ፣ ከዚያም አልፎ መፍትሄ አልባ መምሰሉ ይገርማል?

Read 1866 times