Print this page
Monday, 20 April 2015 14:48

እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው

Written by 
Rate this item
(8 votes)

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ኢጣሊያዊ የማፊያ መሪ (የዘራፊ፣ የመንታፊና ገዳይ ቡድን መሪ) መሞቻው ጊዜ ደርሶ ኖሮ የልጅ ልጁን ጠራው፡፡ ከዚያም፤
“የልጅ ልጄ ያስጠራሁህ ለዋዛ አይደለም፡፡ በደንብ አዳምጠኝ”
“እሺ አያቴ፡፡ ምን ልትለኝ ፈልገሃል?”
“እንግዲህ መሞቻዬ ተቃርቧል”
“አያቴ፣ ለምን እንዲህ ትላለህ?”
 “በጣም ደህና እኮ ነህ?” ምንም የህመም ምልክት እንኳ አይታይብህም
“አይመስለኝም፡፡ ድምፄ ከመክሰሙ በፊት ብታዳምጠኝ መልካም ነው፡፡”
“እሺ አያቴ አዳምጥሃለሁ”
“አየህ እኔ ምን ጊዜም እንድታስታውሰኝ ስለምፈልግ አንድ ስጦታ ልሰጥህ እፈልጋለሁ”
“አያቴ ምንም ስጦታ ባትሰጠኝም አልረሳህም”
“በጭራሽ፡፡ የሰንሰል ቅጠልም ቢሆን ሰው ለሰው ስጦታ የሚሰጠው እንዲያስታውሰው ይጠቅመዋል፡፡ ስለዚህ ኮልት 45 ሽጉጤን እሰጥሃለሁ፡፡ ዘራፊ፣ መንታፊና የገዳይ ቡድን አባል የሆንኩትን አያትህን ምን ጊዜም የምታስታውሰኝ በዚህ ሽጉጥ ይሆናል” አለ፡፡
ይሄኔ የልጅ ልጁ፤
“ግን አያቴ፣ እኔ ሽጉጥ፣ ጠመንጃ፣ ጦር ጋሻ አልወድም፡፡ ምን ያደርግልኛል? እኔ የማፊያ ቡድን አባል አልሆንም፡፡  ይልቅስ ዕውነት የምትወደኝ ከሆን ሮሌክስ ሰዓትህን ትተህልኝ ሂድ፡፡ ውድ ሰዓትህ ሁልጊዜ አንተን የስታውሰኛል፡፡”
አያትዬው ድምፁ እየተንተባተበና እየተጎተተ መጣ፣
“የልጅ .. ል…ጄ…. በደ…ምብ አድምጠኝ የ… ቤታ…ችንን… ን.ግ.ድ.የምትመራው አንድ…ቀን አን…ተ  ነ.ህ… ከዚያ ቆንጆ ..ሚ..ስ..ት…ታገባ…ለህ፡፡ ብዙ … ገንዘብ ..  ይኖ.. ርሃል፡፡ ትልቅ ቪላ.. ቤ..ት ይኖር…ሃል፡፡ ምናል…ባ…ት..ም.. አንድ ሁለት ባምቢኖ (ልጆች) ይኖሩሃል፡፡
… እና ከዕለ… ታት አንድ ቀን … ሥ…ራ ውለህ ወደ ቤት … ስትመጣ ሚስትህ … ከሌላ ወንድ ጋር ተኝታ ልታገኛት ትችላለህ…  ያን ጊዜ ምን ታደርጋለህ? … የእኔን ሮሌክስ ሰዓት እያሳየህ “በቃችሁ ሰዓቱ ደርሷል!” ትላቸዋለህ?
ይልቅ መሳሪያዬን ተረከብ!” አለውና ድምፁ መሰማት አቆመ፡፡
*            *           *
ሁሉም ጉዳይ የየራሱ ማስፈፀሚያ አለው፡፡ የሀገራችን አንዳች የሚያህል ችግር አባትና ልጅ፣ ትውልድና ትውልዱ አለመጣጣሙ ነው፡፡ የአንዱ ፍላጎት ከሌላው ፍላጎት ጋር አለመመጋገቡ ነው፡፡ ለማንኛውም እያንዳንዱ ትውልድ የየራሱን ጣዕም ማበጀቱ እጅግ ወሳኝ ነገር ነው፡፡ የየራሱ ጣዕም የሌለው ትውልድ ለአገር አይበጅም፡፡ ስፖርት የሚያዘወትር፤ ትግል የሚወድ፣ አለ፡፡ ባንፃሩ ማጭበርበርን እንደኑሮ ዘዴ የለመደ፣ በመፈክር አገር እገዛለሁ ብሎ የሚያስብ፤ እርስ በርስ መጠላለፍን እንደፖለቲካ ካባ የደረበ ወዘተ ብዙ ዓይነት ትውልድ አይተናል፡፡
ሁሉም እኔ ልክ ነኝ ስለሚል ተው አይሆንም ማለት አዳጋች ነው፡፡ አቋሙ ታሪክ እስኪሆን በትዕግስት እንድንጠብቅ እንገደዳለን፡፡
ሌላው ችግራችን ስም-ልጠፋ ነው - በክፋት፡፡ (Branding) በዚህ ጉዳይ ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ያለንን መስማት ጥሩ ነው፡-
“አንድ ተረት ልንገርህ፡፡ አንዲት እናት ልጇ አይናፋር ኖሮባት ከጓዳ አልወጣ አለ፡፡ “ወጣ በል!”  ተብሎ ከጓደኞቹ ጋር መቀላቀል ቢፈልግም አልቻለም፡፡ ግን የልጆቹን ሁሉ ስም አጥንቷል፡፡ እዚያ አካባቢ የሚነገረውን ስለሚሰማ ሁሉን ያውቃል፡፡ እቤት ይገባና ለእናቱ “በደሻ እንዲህ ሲል አፍንጮ እንዲህ ብሎ መለሰለት … ቀዮ ግን …” እያለ ይነግራታል፡፡ እናቱ ስትመልስለት “ያንተስ ስም ማነው?” ስትለው “እኔማ … እኔማ ስም የለኝም” አላት፡፡ “እንግዲያው ሂድ… ሂድ መንገዱን አቋርጥ፡፡ ልክ ስታቋርጥ ስም ያወጡልሃል፡፡ ያኔ ትነግረኛለህ፡፡” አለችው፤ ይባላል፡፡
መንገዱን ማቋረጥ የሀሳብ ትግል ይሆናል፡፡ የአቋም መለወጥ ሊሆን ይችላል። የሀሳብ ልዩነትን ግልፅ ሆኖ ማሳየት ሊሆን ይችላል፡፡ በማንኛውም የትኛውንም አዲስ መንገድ አቋርጠን እንሂድ ብንል አዲስ ስም እንደሚወጣልን ጥርጥር የለውም፡፡ ያየናቸው መንግስታት ሁሉ ለጠላቶቻቸው ስም ሳያወጡ አልኖሩም፡፡ ንፁሃን ዜጎችን ጭምር ስም ያወጡላቸዋል፡፡ ይሄ ደግ ዜጋ መንግስትን እንዳያምንና እንዲጠራጠር ያደርገዋል፡፡ ጥርጣሬ ካለ ዕድገት የለም፡፡ ልማት የለም፡፡ ወደፊት መራመድ የለም! ስለዚህ ለትንሽ ለትልቁ መንገድ አቋራጭ፤ ስም ማውጣቱን ትተን ለምን ከቤቱ ወጥቶ መንገድ አቋረጠ? ብለን መጠየቅ ያባት ነው!
ለውጥ ባየን ቁጥር ግትር ብለን አልቀበልም ማለት ጅልነት ነው፡፡ ለውጥ ባየን ቁጥር አብረን ዘራፍ ማለትም ጅልነት ነው፡፡ እኔ ምን አገባኝ ብሎ በምንግዴ መጓዝና መንግሥት ተለወጠ  አልተለወጠ፣ አይሞቀኝ አይበርደኝ ማለት የባሰ ጅልነት ነው! እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው ማለት እንደማያዋጣን ከልብ አውቀን ከተጓዝን አያሌ ነገሮችን ወደቀናው ነገ እንዲያመሩ ለማድረግ እንችላለን፡፡ ለዳግማይ ትንሣዔም እንበቃለን! መልካም በዓል!




Read 5632 times
Administrator

Latest from Administrator