ፌደሬሽኑ በኢቴቪ የፕሪሚየር ሊግ ጨዋታዎችን ለማስተላለፍ ያለውን እቅድ በውድድር ዘመኑ መጀመርያ ሲያስታውቅ ፍላጐቱ ላላቸው ስፖንሰሮች የ2 ሚሊዮን ብር የጨረታ መነሻ ዋጋ አቅርቦ ነበር፡፡ በሊጉ የመጀመርያው ሳምንት የቡናና ሐረርን ጨዋታ በኢቲቪ3 ላይ ለማስተላለፍ ተሞክሮ ያልተሳካ ሲሆን ምክንያቱም ከስፖንሰሮች ጋር የውል ስምምነቱ ባለመጨረሱ እንደነበር ተገልጿል፡፡
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታዎችን ከ14 ዓመት በፊት በቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭት ለማስተላለፍ ተሞክሮ እንደነበር ይታወሳል፡፡ የኢቴቪ የስፖርት ጋዜጠኞች በአዲስ አበባ ስታድዬም የሚደረጉ የብሄራዊ ቡድንና የክለቦች ኢንተርናሽናል ግጥሚያዎች በጥሩ ኮሜንታተርነት እና በሰፊ ትንተና ለማቅረብ ብቁ ልምድ አላቸው፡፡ ይህ የተሟላ ብቃት ደግሞ የስቱድዮና የመስክ ካሜራ ባለሙያችንም ይጨምራል፡፡ በቲቪ የሚቀርቡ ጨዋታዎች በተጠና የስፖንሰሮች የማስታወቂያ ደቂቃዎች፤ የስርጭት ምስልን በማያጣብቡ የፅሁፍ መልክቶች በማጀብ ከፍተኛ ገቢ መሰብሰብ ይቻላል፡፡ የጨዋታዎች ቀረፃ ሪፕሌይ ሊኖራቸው ግን ይገባል፡፡
በቴሌቭዥን ስርጭት የሚገኝ ገቢን ለሊግ ውድድሮች ለማከፈል በዓለም እግር ኳስ ሁለት አይነት አሰራሮች አሉ፡፡ አንደኛው ክለቦች በመብቱ የሚገኘውን ገቢ እኩል የሚካፈሉበት ሲሆን የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በዚያ መልክ መስራቱ ምሳሌ ሆኖ ይጠቀሳል፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ትልልቅ ክለቦች በተናጠል የቴሌቭዥን ስርጭት መብታቸውን በመደራደር ከሌሎች የሊጉ ክለቦች የላቀ ድርሻ የሚወስዱበት ሲሆን የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ በዚህ ሁኔታ መንቀሳቀሱ ናሙና ይሆናል፡፡