Print this page
Monday, 02 March 2015 09:09

ስትታጭ ያጣላች በሠርጓ ታጋድላለች

Written by 
Rate this item
(10 votes)

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ በጣም ጨካኝ ሹም ነበረ ይባላል፡፡ ይሄው ሹም በትንሽ በትልቁ ይቆጣል፡፡ ይገርፋል፡፡ ያስገርፋል፡፡ ሲያሻውም ይገድላል፡፡ አገር ይፈራዋል፡፡ ሰው ሲሽቆጠቆጥለት የማየትን ያህል የሚያስደስተው ነገር የለም፡፡
ወደ ቤቱ እንኳ በጊዜ ገብቶ ሚስቱ፤
“ዛሬ እንዴት ዋልክ?” ስትለው፤
“አንቺ ምን አለብሽ ሰው አትገርፊ፣
አታስገርፊ፣ አትገይ አታስገድይ
ቤትሽ ተኝተሽ ትበያለሽ፤ እኔ ላቤን አፍስሼ ያመጣሁትን ትቦጠቡጫለሽ!” ይላታል፡፡
“በነገራችን ላይ የአቶ እገሌ ልጅ ታሠረ ሲሉ ሰማሁ፡፡ አውቀሃል?”
“አዎን አውቄያለሁ፡፡ እኔ ሳላውቅ የሚሆን ነገር የለም አላልኩሽም?”
“ውይ ትንሽ ልጅ እኮ ነው፡፡ 15 ነው 16 ዓመቱ!”
“አዎ! እሥር ቤት እንዲቆይ ወሰንን”
“ምን ብላችሁ ወሰናችሁ?”
“ለአቅመ አዳም እስኪደርስ ይቀመጥና ሲያድግ እንገርፈዋለን ብለን ወስነናል”
“ውይ እንዴት ክፉ ናችሁ! አሁን ከእናንተና ከልጁ ማ ቀድሞ እንደሚሞት በምን ይታወቅና ነው እንዲህ የምትጨክኑት?”
“ስለ ነገ አርቀሽ ካላሰብሽ ምን ሠርተሽ ትኖሪያለሽ? ጠዋት የሆነውን ሳልነግርሽ? አንድ የህግ ት/ቤት ሄጄ ህግ መማር እፈልጋለሁ ብላቸው፤ ዲሬክተሩ አይቻልም!” አሉኝ
“ለምን አሉ?”
“አንተማ ፈርደህ ጨርሰሃል!” አሉኝ፡፡
“ይሄዋ እቅጩን ነገሩህ!”
“ዕውነትሽን ነው፡፡ ፈርጄ አለመጨረሴን ያሳየሁዋቸው አሁን እና እሥር ቤት ጐራ ብዬ ተሰናብቻቸው ስመጣ ነው!” ብሎ ሳቀ፡፡
                                         *    *    *
ሀገራችን ብዙ ለከት የለሽ ጭካኔ አይታለች፡፡ “ግፉ በዛብኝ እራሴን እገላለሁ” ያሉትን ተበዳይ፤ “እሱንም እኛ ከፈቀድንልህ ነው” ካሉት መሪ “ብዙ ቦታ አትፍጁ፤ አንድ ላይ ቅበሩ” እስካሉ መሪ ድረስ፤ ሰው ጤፉ ጭካኔ አይተናል/ታዝበናል፡፡ በእነዚህ ሁሉ ዘመናት የሚወራው ስለ ህዝብ ነው፡፡ ስለ ሀገር ሉዓላዊነት ነው፡፡ ስለ ሀገራዊነት ነው ስለ አንድነት ነው፡፡ ስለ ዕድገትና ብልፅግና ነው፡፡ የተሻለ ኢኮኖሚ ስለማምጣት ነው፡፡ ስለ ፍትሕ ርትዕ ነው፡፡ ህዝብ የፈለገውን መሪ እንዳገኘ ነው፡፡ ለውጥ በየቀኑ እየመጣ እንደሆነ ነው፡፡ ለውጥ ግን መሠረታዊ መሆን እንዳለበት በቅጡ የተናገረም፣ የተገበረም አልታየም፡፡
“ለውጥ አምፖል የመለወጥ ጉዳይ መሆኑ አብቅቷል፡፡ ይልቁንም ዓለምን ሙሉውን የመለወጥ፣ ሙሉን የማብራት ጉዳይ ነው” ትለናለች ናዎሚ ክላየን፡፡
አንድም አንድ አምፖል ቀይሮ መፎከር አሳሳች ስለሆነ፤ አንድም ደግሞ ቢያንስ የተሻለ አምፖል መሆን አለመሆኑ አለመታወቁም ነው፡፡ በመጨረሻም ዘላቂና አስተማማኝ ለውጥ ለማግኘት ለዋጩ ብቻ ሳይሆን ተለዋጩ ህዝብ ይሆነኛል ማለት ስላለበት ነው፡፡
ተጠቃሚውም አረጋጋጩ እሱ ነውና፡፡ ይህንን ህዝብ ተኮር መርህ ስንቶች ተመራጮች ከልባቸው አስበውበት፣ ምን ያህልስ ይታገሉለት ይሆን? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ በምርጫ ፉክክር ውስጥ አሯሯጭ የሚባል አለ እንዴ? የቅስቀሳ የአየር ጊዜ ምን ያህል የነገ ማንነትን ጠቋሚ ይሆን?
“ካልታዘልኩ አላምንም” ያለችው ሙሽሪት፣ ይፈረድባት ይሆን? እስከዛሬ ምን ያህል ያማሩ ፕሮግራሞችን አይተናል? እኒያን ፕሮግራሞች ስንቶች ከልብ ደከሙባቸው? ምን ያህል ህዝብ ልብ ውስጥ ገቡ/ኖሩ? የተቀሰቀስነውን ያህል ነቅተን ይሆን? ከጠዋቱ ጭቅጭቅ፣ ንትርክና፣ መፈነካከት ውስጥ መግባት በረከሰባት አገራችን ምን ያህል ተወዳዳሪ ይሳካለት ይሆን? ነው ወይስ ስትታጭ ያጣላች፤ በሠርጓ ታጋድላለች ይሆን አካሄዱ? እስቲ ለነገ ያብቃን ለፍሬ - ግብሩ!


Read 4943 times
Administrator

Latest from Administrator