Saturday, 31 January 2015 13:09

የዱባይ አውሮፕላን ማረፊያ በአለማችን ቀዳሚው ሆነ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

የዱባይ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው አውሮፕላኖችንና መንገደኞችን በማስተናገድ በአለማችን ከሚገኙ አውሮፕላን ማረፊያዎች የመጀመሪያውን ደረጃ መያዙን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡
በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2014 ዓ.ም 70 ነጥብ 47 ሚሊዮን መንገደኞችን ያስተናገደው የዱባይ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ፣ ከዚህ በፊት በርካታ መንገደኞችን በማስተናገድ ቀዳሚነቱን ይዞ የቆየውን የለንደኑን ሄትሮው አውሮፕላን ማረፊያ በመብለጥ በአንደኝነት መቀመጡን ዘገባው አስታውቋል፡፡
የዱባይ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ስራ አስኪያጅ ሼህ አህመድ ቢን ሰኢድ አል መክቱም እንደገለጹት፣ በርካታ አለማቀፍ በረራዎችን በማስተናገድ የሚታወቀው አውሮፕላን ማረፊያው የሚያስተናግዳቸውን መንገደኞቹን ቁጥር ባለፉት አምስት አመታት በኣማካይ በሁለት ዲጂት እያሳደገ መጥቷል፡፡
አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው ዱባይን የአለማቀፍ የአየር በረራ ማዕከል የማድረግ ግቡን ወደ ማሳካት እየተቃረበ ነው ያሉት ስራ አስኪያጁ፣ በተያዘው የፈረንጆች አመትም የመንገደኞቹን ብዛት በከፍተኛ ሁኔታ ለማሳደግ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡
የአውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ፖል ግሪቭስ በበኩላቸው፣ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው አዲስ የበረራ ማስተናገጃ በመክፈት፣ አመታዊ የመንገደኞች ማሰተናገድ አቅሙን በያዝነው የፈረንጆች አመት 90 ሚሊዮን ለማድረስ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡
ከዚህ ቀደም በርካታ መንገደኞችን በማስተናገድ በቀዳሚነት ይጠቀስ የነበረው የለንደኑን ሄትሮው አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ በ2014 ያስተናገዳቸው መንገደኞች ቁጥር 68.1 ሚሊዮን እንደነበር ዘገባው ጨምሮ ገልጧል፡፡

Read 1885 times