Saturday, 25 October 2014 09:59

ቁምነገርና ፌዝ አለመለየት “አደጋ አለው!”

Written by  ኤልያስ
Rate this item
(20 votes)

          ኢህአዴግ ብዙ ይዘገያል እንጂ አንዳንድ ነገሮችን እኮ ይቀበላል፡፡ (ምንጩን አጣርቶ ነው ታዲያ!) ምን ሰምተህ ነው አትሉኝም! ሰሞኑን በEBC እንደሰማሁት፣ የመንግስት ተቋማት የኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች (የህዝብ ግንኙነት ለማለት ነው) በፌስ ቡክ አጠቃቀም ላይ ስልጠና የተሰጣቸው ሲሆን ዓላማውም በማህበራዊ ድረ-ገፆች ላይ የሚሰራጩ “በሬ ወለደ” ዓይነት ውሸቶችን ለመመከትና እውነታውን ለማሳወቅ ነው ተብሏል፡፡ ደስ አይልም - ውሸትን በእውነት መመከት!! (እውነት አንፃራዊ ናት እንዳትሉኝ!) ለማንኛውም ግን ፌስ ቡክን እዘጋዋለሁ ከሚል ‹ቴረር› ወይም ‹ሆረር› ሺ ጊዜ ይሻላል (ይሻላል ብቻ ሳይሆን ትክክለኛ ውሳኔ ነው!) በነገራችሁ ላይ በግል ፕሬሶችም ላይ ተመሳሳይ ውሳኔ ይሻል ነበር፡፡ በአንድ ጊዜ እኒያን ሁሉ የፕሬስ ውጤቶች ዝም ጭጭ ከማሰኘት ማለቴ ነው፡፡ (ያኔ አልተገለጠለት ይሆናላ!)
ወደ ሌላ አጀንዳ ከማለፋችን በፊት አንድ ሁለት ቀልዶችን ብነግራችሁስ፡፡ ሰውየው የአውራው ፓርቲ ወይም የ“ልማታዊ መንግስታችን” ካድሬ ነው - የቀልድ ምንጮቼ እንደነገሩኝ፡፡ እናላችሁ…የመንግስት ሃላፊዎች የሃብት ምዝገባ ሲካሄድ ይሄም ካድሬ ሃብቱን ሊያስመዘግብ ተገኝቶ ነበር (ካድሬም ለካ ሃብት አለው!) በምዝገባው ሂደት ላይ ታዲያ “የሥራ ዓይነት” ሲል ይጠይቃል፤ የሃብት መዝጋቢው - ካድሬውን፡፡ (“ካድሬነት” የሚል ከመሰላችሁ ተሳስታችኋል!) ካድሬ ሆዬ፤ የሥራ ዓይነት ሲባል “መንግስትነት” ብሎ አረፈው፡፡ እዚህ አገር ለመጀመርያ ጊዜ ነው እንዲህ ያለ ሥራ መኖሩን የሰማሁት፡፡ እኔ እሱን ብሆን ግን “መንግስትነት” ሳይሆን “ኢህአዴግነት” ነበር የምለው፡፡ እውነት ግን ለካድሬ የሚቀርበው የትኛው ነው? መንግስት ወይስ ኢህአዴግ? ቀልዱ ያን ያህል ፍርፍር አድርጐ ባያስቅም በኢህአዴግ ካድሬዎች ላይ ጥናት ለሚያካሂዱ የፖለቲካ ምሁራን ጥሩ ግብዓት እንደሚሆን ቅንጣት አልጠራጠርም፡፡
ሌላ ቀልድ ልጨምርላችሁ፡፡ ይሄኛው መራራ ቀልድ (bitter humour) የሚባለው ዓይነት ነው፡፡ (“መራራ ኑሮ ላይ መራራ ቀልድ” እንዳትሉኝ!) ቀልዱን አንድ ጉምቱ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ፤ የኢህአዴግ ከፍተኛ ሹማምንት በተገኙበት መድረክ ላይ የተናገሩት እንደሆነ ስለሰማሁ ዘና ብላችሁ አንብቡት (ቀልድ እኮ የህዝብ ሀብት ነው!) ከህአዴግ ጋር ከምር የምጣላው መቼ መሰላችሁ? ቀልድ እንደ መሬት ሁሉ የህዝብና የመንግስት ሃብት ነው ያለ ጊዜ! (ቀልድ በሊዝ በጄ አንልማ!)
ወደ ቀልዱ እንሂድ፡፡ ኢህአዴግና ሰይጣን፤ ቤት ለመከራየት አንዲት በእድሜ የገፉ ባልቴት መኖሪያ ቤት ይሄዳሉ፡፡ ሁለቱም እኩል ስለደረሱ የኪራዩ ዋጋ ጨረታ ዓይነት ነገር ሆነ፡፡ ኢህአዴግ ጨረታውን በአሸናፊነት ለመወጣት ቆርጦ ስለተነሳ፣ ከተጠየቀው የኪራይ ዋጋ ከፍ አድርጐ ተናገረ፡፡ (ሰይጣንን ወደመጣበት ለመመለስ!) አሮጊቷ የሁለቱንም እጩ ተከራዮች ሃሳብና አቅም ለአፍታ ያህል ከገመገሙ በኋላ ቤታቸውን ለሰይጣን እንደሚያከራዩት ይፋ አደረጉ፡፡ (በሙስና መሆን አለበት!) ኢህአዴግ ክው አለ (ከ97 ምርጫ በኋላ “ከፍተኛው ድንጋጤ” በሉት!) ለመረጋጋት እየሞከረ፤ “ምነው እናት፤ እኛ ከፍ ያለ ገንዘብ አቅርበናል፤ በዚያ ላይ ከ20 ዓመት በላይ ህዝባዊነታችንን በተግባር አረጋግጠናል፡፡ እንዴት እኛን ትተው ለዚህ ለከሃዲ ሰይጣን ያከራያሉ?” ሲል ጠየቀ፤ ኢህአዴግ፤ በቁጣና በመማፀን መሃል እየዋለለ፡፡ እሳቸውም “ሰይጣን እኮ ቢያንስ በፀበል ይለቃል…” አሉ፡፡ (“ኪራይ ሰብሳቢ” ብዬ ልፈርጃቸው አልኩና የዕድሜ ባለፀግነታቸው አሳሳኝ!)
ዘመኑ በከፊልም ቢሆን ነፃ ገበያ ነውና ኢህአዴግ አሮጊቷን “የኒዮሊበራል ቅጥረኛ” ብሎ ከመፈረጅ ውጪ ሌላ ምንም ማድረግ አልቻለም (ይሄ የእኔ ግምት ነው!) እኔ የምለው የሸማቾች ማህበር የሚባለው ተቋም፤ የግል ቤቶችን የኪራይ ተመን ሊያወጣ ነው የሚባለው ከምር ነው እንዴ? (“ነፃ ገበያ” መንምና መንምና “ገበያ” ብቻዋን ልትቀር ነው!) በነገራችሁ ላይ ይህቺን ቀልድ የፈጠሯት ሥልጣን ይገባናል ባይ ወገኖች ሳይሆኑ አይቀርም (ጥርጣሬ ነው!)፡፡ ግን እኮ ሥልጣን በምርጫ እንጂ በፀበል አይገኝም፡፡  
በቅርቡ ኢትዮጵያና ማሊ እዚህ አዲስ አበባ ስታዲየም ተጋጥመው በተሸነፍንበት ወቅት ኢህአዴግ “የሻዕቢያ ቅጥረኞች” እንደሚላቸው ዓይነቶቹ የሚሊን ቡድን “ኢቦላ! ኢቦላ!” በማለት ለማብሸቅ ሞክረው ነበር አሉ፡፡ (እብደት እኮ ነው!) የሆኖ ሆኖ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በተራው ማሊ ሄደና ድል ቀናው፡፡
አሸነፈ፡፡ ድል ብቻ ግን አይደለም፡፡ ፈተናም ገጥሞት ነበር አሉ፡፡ (ከዚህ ይጀምራል ቀልዱ!) እናም ቂም በሆዳቸው የቋጠሩት ማሊዎች ሰብሰብ ብለው “አገራችሁ የመጣን ጊዜ ለምንድነው ‹ኢቦላ! ኢቦላ!› እያላችሁ የሰደባችሁን? ሲሉ አፋጠጧቸው፡፡ የቡድናችን ተወካዮችም “መሳደባችን እኮ አይደለም…እኛ አገር ‹ኤቦ…ኤቦ ላላ›” የሚል ዘፈን ስላለ ነው” በማለት በብልሃት ተወጡት፡፡  
አንዳንዴ የሚቀለድበትና የማይቀለድበትን ነገር መለየት ሳይኖርብን አይቀርም፡፡ እውነቱን ልንገራችሁ አይደል … “ኢቦላ” ብሎ መሳደብ ኋላቀርነትም ኢ-ሰብዓዊነትም ነው፡፡ (እልም ያለ ፋርነት በሉት!)
ባለፈው ሳምንት ደግሞ የአሜሪካ ኤምባሲ ቦሌ ኤርፖርት አካባቢ አልሸባብ ጥቃት እንደሚሰነዝር መረጃ ደርሶኛልና ዜጐቼ ጥንቃቄ አድርጉ የሚል መልዕክት ማስተላለፉን ተከትሎ፣ በፌስ ቡክ ላይ “መንግስት 1፣ አልሻባብ 0” የሚል ፌዝ ወጥቶ ነበር፡፡ ሰው በራሱ ህይወት ያፌዛል እንዴ? ሽብር ማለት እኮ ሌላ ሳይሆን ቦንብ … ፈንጂ … እልቂት … ግድያ ጥፋት … ማለት ብቻ ነው፡፡ ሽብርተኞች ማለት ደሞ … እነ አልቃይዳ፣ እና አልሻባብ፣ እነ ቦካሃራም፣ እነ አይሲስ… አይነቶቹ ናቸው፡፡ (እነሱ እኮ ፌዝ አያውቁም!)
እኔ የምለው … ባለፈው ሳምንት የውጭ ጉዳይ ሚ/ር ኢቦላ ኢትዮጵያ ውስጥ አለመግባቱን ለህዝቡ ለማረጋገጥ ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ ላይ “ሻዕቢያ ያሰራጨው ወሬ ነው” ሲል የሰማሁ መስሎኛል፡፡ አይገርማችሁም… ሻዕቢያ ሌላው ሲያቅተው “የኢቦላ ሽብር” መንዛት ጀመረ ማለት ነው (እውነትም ተስፋ ቆርጧል!)
ወጋችንን እንግዲህ በቀልድ እንቋጨው፡፡ እንደአለመታደል ሆኖ ይሄኛውም ከመራራ ቀልዶች (bitter humor) የሚመደብ ነው፡፡ አይገርማችሁም … በዚህ ሳምንት ከሶስት ሰዎች የደረሱኝ ሶስቱም ቀልዶች ምርር ያሉ ናቸው፡፡ (መራራ ቀልድ የመራራ ኑሮ ውጤት ነው ልበል?) እናላችሁ አንድ ከፍተኛ የህንድ ባለስልጣን ኢትዮጵያን ለመጎብኘት ይመጣሉ፡፡ ጉብኝቱ የተጀመረው የቻይና የእጅ ሥራ ውጤት ከሆነው ከቀለበት መንገድ ነው አሉ፡፡ ከዚያም በጎተራ ማሰላጫ አድርገው… በቅዱስ ዮሴፍ ቤ/ክርስትያን በኩል ያልፋሉ፡፡ የህንዱ ባለስልጣን በርካታ ሃውልቶች ያዩና ጥያቄ ያቀርባሉ፤ “ይሄ ደሞ ምንድነው?”
የገዢው ፓርቲ የመንግሥት ተወካይ፤ “የሞቱ ዜጎቻችን የሚያርፉበት ሥፍራ ነው”
የህንድ ባለስልጣን፤ “እነዚህ ሁሉ … ለምን እንደኛ አታቃጥሏቸውም?” (በህንድ አስከሬን የማቃጠል ሃይማኖታዊ ሥርዓት እንዳለ ልብ ይሏል!)
የመንግስት ተወካይ፤ “አይ … እኛ በቁማቸው ነው የምናቃጥላቸው”
በነገራችሁ ላይ የዚህ ቀልድ ባለቤት ህዝብ ነው! (ኮፒራይቱም የህዝቡ ነው ማለት ነው!)

Read 5580 times