Saturday, 06 September 2014 10:45

አንድነት በአዲሱ ዓመት ሃገራዊ ኃላፊነትን ለመሸከም ተዘጋጅቼአለሁ አለ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

            አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ በአዲሱ ዓመት ሃገራዊ ኃላፊነትን ለመሸከም መዘጋጀቱን ገለፀ፡፡ ፓርቲው ከትናንት በስቲያ ረፋድ ላይ በጽ/ቤቱ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ “የገዢውን ፓርቲ ምርጫ መጣ ነፃ ፕሬስ ውጣ” አይነት አካሄድ አጥብቆ እንደሚቃወም አስታውቋል፡፡
እንደነ አንዷለም አራጌ፣ ናትናኤል መኮንን፣ አንዱዓለም አያሌው፣ ሻምበል የሺዋስ፣ ሃብታሙ አያሌው እና ዳንኤል ሺበሺ ያሉ ወጣት የፓርቲው አመራሮች በፖለቲካ አመለካከታቸው ብቻ ወህኒ ተወርውረው የግፍ ፅዋ እየተጋቱ ነው” ያለው ፓርቲው፤  “አፈናና ስደት በአምባገነን መሪዎች አገር የተለመደና የሚታወቅ ቢሆንም አምባገነንነት በኢህአዴግ እንዲያበቃ ቆርጠን እንታገላለን” ብሏል፡፡
ፓርቲው ከ2003 ዓ.ም እስከ 2007 ዓ.ም ያለውን ጊዜ “የኢትዮጵያ ፖለቲካ ትግል እድሳትና ማንሰራራት ዘመን” ብሎ በመሰየም ባለፉት አመታት በከፍተኛ ህዝባዊ ንቅናቄ የኢትዮጵያን ህዝብ ችግሮች አደባባይ እንዳወጣ አስታውቋል፡፡
“የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” እና “የእሪታ ቀን” በሚል ያካሄዳቸውን እንቅስቃሴዎች በመጥቀስ፡፡
የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው በመግለጫው ላይ እንደተናገሩት፤ “አፈናና እስራት ቢበዛብንም ትግሉ ከዚህም የባሰና የከፋ ችግር እንደሚያስከትል እያወቅን ስለገባንበት በሰላማዊ ትግላችን እንቀጥላን“ ብለዋል፡፡
ፓርቲው በ2007 “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነትና ፍትሃዊ ምርጫ “በሚል አመቱን ሙሉ የሚቆይ ንቅናቄ እንደሚያካሂድ ገልፆ፣ በዚሁ ዓመት በሚደረገው ሃገራዊ ምርጫ ላይ የምርጫ ቦርድ፣ የመገናኛ ብዙሃን፣ የፍትህ ስርዓቱና ሌሎች የዴሞክራሲ ተቋማት በህገ-መንግስቱ የተደነገገውን መሰረት በማድረግ ገለልተኝነታቸውን በአንፃራዊ ደረጃ በማረጋገጥ፣ በምርጫው እንደሚሳተፍና የህዝብን የስልጣን ባለቤትት ለህዝብ እንደሚያበስር አመራሮቹ ተናግረዋል፡፡
 የፓርቲውን ስትራቴጂና የአምስት ዓመት እቅድ መሰረት በማድረግ፣ በአብዛኛው የአገሪቱ ክልል ምርጫ ተኮር አደረጃጀት ለመዘርጋት እንቅስቃሴ መጀመሩንም ፓርቲው አስታውቋል፡፡ “መንግስት ለ2007 ዓ.ም ምርጫ ፍጆታ ሲል ለሰራተኛው ደሞዝ ጨመርኩ ቢልም ህዝቡ ጀኑሮ ውድነት የተሰቃየበትና አሁንም እየተሰቃየ ያለበት ዓመት ሆኗል፡፡” ያሉት አመራሮቹ፣ መንግስት ገበያውን በአስቸኳይ በማረጋጋት የህዝቡን ጫና እንዲቀንስ ጠይቀዋል፡፡
 መንግስት የአዲስ አበባን ይዞታ ለማስፋፋት ሲል የሚመለከታቸውን የህብረተሰብ ክፍሎች ሳያወያይ ባደረገው አከላለል በተነሳ የህዝብ ቁጣ በርካታ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ለሞት፣ ለአካል ጉዳት፣ ለእስራትና ለተያያዥ ጉዳዮች ያጋለጠ በመሆኑ ከምንግዜውም በላይ ዓመቱን መራራ አድርጎት ማለፉን የተናገሩት የአንድነት አመራሮች በ2007 ዓ.ም ይህ ሁሉ ግፍ ተወግዶ ህዝቡ እፎይታ የሚያገኝበት ዓመት እንዲሆን ፓርቲው ከምንጊዜውም በላይ የሃገርን ኃላፊነት ለመሸከም መዘጋጀቱን ገልፀዋል፡፡ፓርቲው ለኢትዮጵያ ህዝብ ባስተላፈው መልእክት፤ በመጪው አገራዊ ምርጫ ከህዝቡ ጋር በመሆን ሰላማዊ ትግሉን በምርጫ ለማሳካት በአራቱም ማዕዘናት የፖለቲካ ፕሮግራሙን እንደሚተገብርና መጪው ዘመን የኢትዮጵያ ህዝብ ነፃነት በእጁ የሚገባበት በመሆኑ ህዝቡ ከትግሉ ከጎኑ እንዲቆም ጥሪውን አቅርቧል፡፡

Read 1873 times