Tuesday, 29 July 2014 14:41

የእስልምና ምክር ቤት አመራሮች ለ“መቄዶንያ” ከ100ሺ ብር በላይ የሚያወጡ ቁሳቁሶች ለገሱ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(1 Vote)

   የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች በጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዚዳንትን ጨምሮ የምክር ቤቱና የኡላማ ምክር ቤት አባላት “መቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ መርጃ ማዕከል”ን በመጎብኘት ከ100 ሺ ብር በላይ የሚያወጡ ቁሳቁሶችን ለገሱ፡፡
የምክር ቤቱ ፕሬዚዳንት ሼህ ኪያር ሼህ መሃመድ አማን፣ የኡላማ ምክር ቤት ፀሃፊ ሼክ ዚአዲን ሼህ አብዲላዚዝን  ጨምሮ ሌሎች የምክር ቤቱ አባላት ከትናንት በስቲያ ማዕከሉን በጎበኙበት ወቅት አልባሳት፣ የገላ ሳሙና፣ ዳይፐርና ሶፍት የመሳሰሉ መገልገያ ቁሳቁሶችን ለግሰዋል፡፡
በጉብኝቱ ወቅት ፕሬዚዳንቱ ባደረጉት ንግግር፤ የማዕከሉ እንቅስቃሴና ተግባር ከጠበቁትና ከገመቱት በላይ መሆኑን ገልፀው “መቄዶንያ በየጎዳናው የወደቁትን አንስቶ ለክብር በማብቃቱ ትልቅ ባለውለታ ነው፣ ይህን ስራውን ሁላችንም መደገፍ በጎ ተግባሩን ለሃገር ብቻ ሳይሆን ለዓለም ማስተላለፍ አለብን” ብለዋል፡፡
ተቋሙ ከአዲስ አበባ ውጪም ቅርንጫፍ ማዕከላት እንዲከፍት ምክር የለገሱት ፕሬዝዳንቱ፤ ሙስሊሙ ህብረተሰብ መቄዶንያን ማስታወስ አለበት ብለዋል፡፡ ማዕከሉንም ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል እንዲጎበኘው ፕሬዚዳንቱ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

Read 1880 times