Saturday, 17 December 2011 11:41

ቡናና የጊዮርጊስ ተመልካቹን ወደ ስታድዬም ይመልሳሉ?

Written by  ግሩም ሠይፉ
Rate this item
(2 votes)

የ2004 የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ከተጀመረ 3 ሳምንት ቢያልፈውም በአዲስ አበባ ስታድዬም እና በሌሎች የክልል ከተሞች የሚደረጉ ጨዋታዎች በተመልካች ድርቅ መመታታቸው አሳሰበ፡፡ የአምናው ሻምፒዮን ኢትዮጵያ ቡና እና የጥሎ ማለፍ አሸናፊው ቅዱስ ጊዮርጊስ  በአዲስ አበባ ስታድዬም የሚገናኙ ሲሆን ይሄው ጨዋታ በተመልካች ድርቅ ለተመታው አዲስ አበባ ስታድዬም መነቃቃት ሊፈጥር እንደሚችል ተገምቷል፡፡  በ14 ክለቦች መካከል  በአዲስ መዋቅር የሚካሄደው ፕሪሚዬር ሊጉ  በአጀማመሩም በሁሉም የሚዲያ ዘርፎች በቂ ሽፋን እያገኘ ቢሆንም በተለይ በአዲስ አበባ ስታድዬም ጨዋታዎችን የሚከታተል ስፖርት አፍቃሪ እየተመናመነ በመምጣቱ የፉክክር ደረጃውን ሊቀንሰውና ክለቦች በገቢ ተጠቃሚ የሚሆኑበትን እድል እንደሚነፍግ ታውቋል፡፡

የውድድር ዘመኑ ሲጀመር በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን የተመረጡ  ጨዋታዎች ለማስተላለፍ መታቀዱ በይፋ ቢነገርም ባልታወቀ ምክንያት ይህን ተግባራዊ ማድረግ ባለመቻሉም ግጥሚያዎች በአገር አቀፍ ደረጃ ሊኖራቸው የሚችለውን ትኩረት አደብዝዞታል፡፡ በፕሪሚዬር ሊጉ የ3 ሳምንት ጨዋታዎች 17 ግጥሚያዎች ተደርገው 30 ጎሎች ከመረብ ያረፉ ሲሆን ሊጉ ባንድ ጨዋታ በአማካይ 1.76 ጎል የሚመዘገብበት ሆኗል፡፡ የአምናው ሻምፒዮን ኢትዮጵያ ቡና 3 ጨዋታዎች አድርጎ በሁለቱ አቻ ወጥቶ እና በአንዱ ተሸንፎ በ2 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ነው፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሁለት ተስተካካይ ጨዋታዎች  እየቀሩት ከሳምንት በፊት በውድድር ዘመኑ የመጀመርያ ግጥሚያው ከሜዳው ውጭ በድሬዳዋ ከነማ አድርጎ 1ለ0 ከተሸነፈ በኋላ ያለምንም ነጥብ  13ኛ ላይ ነው፡፡

በሌላ በኩል በነገው በትልቁ የኢትዮጵያ ክለቦች ደርቢ የሚጋጠሙት ኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ በአፍሪካ የክለቦች ውድድር የቅድመ ማጣርያ ግጥሚያዎቻቸውን በኮሞሮስ ደሴት እና በጋቦን ከሜዳቸው ውጪ  በጥር ወር መጨረሻ ላይ ይጀምራሉ፡፡ በ16ኛው የአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮናነቱ የሚሳተፈው ኢትዮጵያ ቡና በቅድመ ማጣርያ የመጀመርያ ግጥሚያውን ከሜዳው ውጭ ከኮሞሮሱ ክለብ ኮየን ኖርድ ጋር ይጀምራል፡፡  በ9ኛው የአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕ ላይ ተሳታፊ የሚሆነው የኢትዮፕያ ጥሎ ማለፍ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ  ደግሞ በቅድመ ማጣርያው የመጀመርያ ግጥሚያው የሚገናኘው ከጋቦኑ ክለብ ኤኤስ ማንጋስፖርት ጋር ነው፡፡  ሁለቱ ክለቦች  የመልስ ጨዋታዎቻቸውን በአዲስ አበባ ስታድዬም በየካቲት ወር አጋማሽ ላይ ያደርጋሉ፡፡

በቅድመ ማጣርያው የደርሶ መልስ ጨዋታዎች በአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ የሚወዳደረው ኢትዮጵያ ቡና የኮሞሮሱን ክለብ ኮይን ኖርድ ጥሎ ካለፈ  በቀጣይ ምእራፍ ከግብፁ ክለብ አልሃሊ ጋር ይገናኛል፡፡ በኮንፌደሬሽን ካፑ የሚወዳደረው ቅዱስ ጊዮርጊስ  ደግሞ  የጋቦኑን ክለብ ማንጋስፖርትን ጥሎ ማለፍ ከቻለ በቀጣይ ምእራፍ ከቱኒዚያው ክለብ አፍሪካ ጋር ይፋጠጣል፡፡በአፍሪካ የክለብ ውድድሮች ላይ የተሳትፎ ታሪክ ካላቸው የኢትዮጵያ ክለቦች ቅ/ጊዮርጊስ፣ መብራት ሀይልና ሀዋሳ ከነማ  ፤ ደደቢት እና ኢትዮፕያ  ቡና  ተጠቃሽ ሲሆኑ ከምድብ ማጣርያ በፊት ያሉትን የ2 ዙር የማጣርያ ምእራፎችን ማለፍ  ሳይችሉ ቀርተዋል፡፡ ዘንድሮ ኢትዮጵያን በአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ የሚወክለው ኢትዮጵያ ቡና  በታሪኩ በአራት አህጉራዊ የክለብ ውድድሮች የመሳተፍ እድል አግኝቷል፡፡ ክለቡ በአፍሪካ ሻምፒየንስ ሊግ ከ11 ዓመት በፊት እስከ ሁለተኛ ዙር  መድረሱ የመጀመርያው ስኬት ከመሆኑም በላይ ለአገሪቱ ክለቦች ትልቁ የውጤት ደረጃ ነው፡፡ ቅ/ጊዮርጊስ በኢትዮጵያ  እግር ኳስ ታሪክ ለበርካታ ጊዜያት በኢንተርናሽናል ውድድር በመሳተፍ ግንባር ቀደም ሲሆን  ለመጀመሪያ ጊዜ የተካፈለው ከ37 አመታት በፊት  ነበር፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን በአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳታፊ የነበረው ጊዮርጊስ በቅድመ ማጣርያው የተደለደለው ከሱዳኑ ኤልሜሪክ ጋር እንደነበር ሲታወስ ጥሎ ማለፍ  እንዳዳገተው ይታወሳል፡፡፡

 

Read 2677 times Last modified on Saturday, 17 December 2011 11:46