Saturday, 07 June 2014 13:08

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በትርፋማነቱ ከዓለም 18ኛ ሆነ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

የአየር መንገዶች የአመቱ አጠቃላይ ትርፍ 18 ቢሊዮን ዶላር እንደሚደርስ ይጠበቃል

በትርፋማነታቸው ልቀው የተገኙ ሃምሳ የአለማችን አየር መንገዶችን በመምረጥ ይፋ ያደረገው አለማቀፍ የአየር መንገዶች ማህበር /IATA/ ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በ18ኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ገለፀ፡፡ በአመት ከ228 ሚሊዮን  ዶላር በላይ ትርፍ ያስመዘገበው የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ በምርጥ ትርፋማ አየር መንገዶች ዝርዝር ውስጥ ከመግባቱም በተጨማሪ፤ ከአፍሪካ ቀዳሚነቱን እንደያዘ አያታ አስታውቋል፡፡  በጥቂት አመታት ውስጥ በርካታ አውሮፕላኖችን በመግዛት አገልግሎቱን በፍጥነት እያስፋፋ የሚገኘው የኢትዮጵያ አየር መንገድ፤ በትርፋማነት ብቻ ሳይሆን ብዙ መንገደኞችንና ጭነቶችን በማጓጓዝ ታዋቂነቱን እያሳደገ መጥቷል፡፡ በዚህ አገልግሎቱ በአመት 2.3 ቢሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት ከአለማችን ሃምሳ ምርጥ አየር መንገዶች መካከል የ37ኛነት ደረጃን እንደያዘ አያታ ገልጿል፡፡
በትርፋማነት የአለማችን ቀዳሚ አየር መንገድ ተብሎ የተጠቀሰው የጀርመኑ ሉፍታንዛ ሲሆን፣ በአመት ወደ 42 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ገቢ አግኝቷል፡፡ ታዋቂዎቹ ዩናይትድ እና ዴልታ፣ የተሰኙ የአሜሪካ አየር መንገዶች  በ38 እና በ37.6 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ሁለተኛና ሶስተኛ ሆነዋል፡፡
የአየር መንገዶች ማህበር (አያታ) ዳይሬክተር ቶኒ ቴለር በሰጡት መግለጫ፣ የአለማችን አየር መንገዶች በዚህ አመት በድምሩ 18 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ትርፍ ያገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡
በየቀኑ በሚደረጉ 100 ሺህ ያህል በረራዎች 50 ሺህ መዳረሻዎችን ማስተሳሰር የቻለውና መቶኛ አመቱን ያከበረው የአለማችን የአቪየሽን ኢንዱስትሪ፤ በያዝነው የፈረንጆች አመት 3.3 ቢሊዮን መንገደኞችንና 520 ሚሊዮን ኩንታል ጭነት ያጓጉዛል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆሙት ቶኒ ቴለር፤ ኢንዱስትሪው በአለም አቀፍ ደረጃ ከ58 ሚሊዮን በላይ የስራ ዕድሎችን እንደፈጠረ ተናግረዋል፡፡

Read 2602 times Last modified on Saturday, 07 June 2014 13:15