Saturday, 31 May 2014 12:21

የ‘ሰዎች ለሰዎች’ መስራች ካርልሀይንስ በም በ86 አመታቸው አረፉ

Written by 
Rate this item
(2 votes)

ለበርካታ አመታት በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ሰፋፊ የምግባረ ሰናይ ስራዎችን በመስራት የሚታወቀው ‘ሰዎች ለሰዎች’ (Menschen für Menschen) የበጎ አድራጎት ድርጅት መስራች ኦስትሪያዊው በጎ አድራጊና ታዋቂ የፊልም ተዋናይ ካርልሀይንስ በም፣ ከትናንት በስቲያ በ86 አመታቸው አረፉ።
ባለፈው አመት የአልዛይመር በሽታ ተጠቂ መሆናቸው በይፋ የተነገረ ሲሆን ህክምናቸውን ሲከታተሉ ቆይተው፣ ከትናንት በስቲያ ምሽት በኦስትሪያ ከሳልዝቡር አቅራቢያ በምትገኘው ግሮዲግ ከተማ፣ በመኖሪያ ቤታቸው ህይወታቸው ማለፉን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
እ.ኤ.አ በ1928 ጀርመን ዳርምስታድ ውስጥ የተወለዱት ካርልሀይንስ በም፣ በስነጥበብ ታሪክና በትወና ትምህርታቸውን የተከታተሉ ሲሆን ለረጅም አመታት በፊልም ትወና ሙያ ተሰማርተው በርካታ ስራዎችን አከናውነዋል፡፡
እ.ኤ.አ በ1981 ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት ‘ሰዎች ለሰዎች’ (Menschen für Menschen) የተባለውን የበጎ አድራጎት ድርጅት በመመስረትና በመምራት፣ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ብዙዎችን ተጠቃሚ ያደረጉ ከትምህርት፣ ከጤናና ከሌሎች ዘርፈ ብዙ ጉዳዮች ጋር የተያያዙ ስራዎችን በማከናወን ይታወቃሉ፡፡
‘ሰዎች ለሰዎች’ን ለረጅም ጊዜያት ሲመሩ የቆዩት ባለቤታቸው ወ/ሮ አልማዝ፣ ካለፈው ታህሳስ ወር ጀምሮ ድርጅቱን የማስተዳደሩን ሃላፊነት ለሌሎች አስረክበው ወደ ኦስትሪያ በመሄድ ባለቤታቸውን ሲያስታምሙ እንደነበር  እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡  
በበጎ አድራጎት ስራቸው ላከናወኑት የላቀ አስተዋጽኦ የኢትዮጵያ መንግስት በ1995 ዓ.ም የክብር ዜግነት የሰጣቸውና ሳር ቤት ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በስማቸው አደባባይ  ተሰይሞ ሃውልት የቆመላቸው ካርልሀይንስ፣ ታዋቂዎቹን የ‘ባላንዛ የሰብዓዊነት፣ የሰላምና የወንድማማችነት ሽልማት’ እና ‘ኢሴል የማህበራዊ አስተዋጽኦ ሽልማት’ ጨምሮ፤ ከተለያዩ አገራት በርካታ የስኬትና የአገልግሎት ሽልማቶችን አግኝተዋል፡፡
ካርልሀይንስ ‘ሲሲ’፣ ‘ፎክስ ኤንድ ሂዝ ፍሬንድስ’፣ ‘ላ ፓሎማ’፣ ‘ዘ ስቶው አዌይ’ እና ‘ካም ፍላይ ዊዝ ሚ’ን ጨምሮ፤ በአሜሪካ፣ በጀርመን፣ በኦስትሪያና በሌሎች አገሮች በተሰሩ 45 ያህል ፊልሞች ላይ በመተወን ችሎታቸውን ያስመሰከሩ ተዋናይ መሆናቸውን ዘ ሆሊውድ ሪፖርተር ዘግቧል፡፡
በ1983 ዓ.ም ከኢትዮጵያዊቷ ባለቤታቸው አልማዝ ተሾመ ጋር በመሰረቱት ትዳር ሁለት ልጆችን ያፈሩት ካርልሀይንስ በም፤ ከቀድሞ ትዳሮቻቸው ያፈሯቸው አምስት ልጆች አሏቸው፡፡

Read 2747 times