Print this page
Monday, 19 May 2014 08:08

የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች አሳሳቢ ደረጃ ላይ ናቸው ተባለ

Written by  መታሰቢያ ካሳዬ
Rate this item
(6 votes)

በከተማችን ካሉ የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች በትክክለኛ ባለሙያ የታገዘ ህክምና የሚሰጡት ከግማሽ በታች ናቸው

ለጥርስ ህክምና እስከ 25 ሺህ ብር ድረስ የሚያስከፍሉ ክሊኒኮች አሉ

               በፒያሣው አትክልት ተራ አካባቢ መደዳውን ከተደረደሩት የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች በአንደኛው ነበር ቀንና ሌሊት እየጠዘጠዘ እንቅልፍ የነሳትን ጥርሷን ከ2 ዓመት በፊት ያስነቀለችው። በክሊኒኩ ያገኘችው ህክምና ለጊዜው ከሥቃይዋ ገላግሏታል። ትዕግስት (ለዚህ ዘገባ ስሟ የተቀየረ) ወደ ክሊኒኩ ገብታ፣ የጥርስ ህክምናዋን ለማድረግ ስትወስን፣ ምንም ዓይነት የጤና ችግር ያጋጥመኛል ብላ አላሰበችም። በዚያ ላይ በክሊኒኩ መግቢያ ደጃፍ ላይ በጉልህ ተፅፎ የተሰቀለው ማስታወቂያ፣ ህክምናው በሥራው ብቁ በሆኑ ባለሙያዎችና ንፅህናቸው በአግባቡ በተጠበቀ መሳሪያዎች እንደሚሰጥ ይገልፃል። ህክምናውን ያደረገላት “ሃኪም”፣ ህመምተኛ ጥርሷን ከነቀለ በኋላ፣ የህመም ማስታገሻ መድኃኒቶችንና አሞክሳሲሊን የተባለውን ክኒን ሰጥቶ አሰናበታት። ትዕግስት ሌትና ቀን ያሰቃያት ከነበረው የጥርስ ህመሟ መገላገሏ ደስታን የፈጠረላት በወራት ለሚቆጠር ዕድሜ ብቻ ነበር። ከጥቂት ወራት በኋላ የተነቀለው ጥርሷ አካባቢ ሃይለኛ የህመም ስሜት ይሰማት ጀመር። ቀስ በቀስ ህመሙ እየጨመረ ሥቃዩ እየበረታባት ሄደ።

እዛው ጥርሷን የተነቀለችበት የጥርስ ክሊኒክ ሄደች። በክሊኒኩ ያገኘቻቸው “ሃኪሞች” ምንም አይነት ችግር እንደሌለባት ገልጸው፤ የህመም ማስታገሻ ክኒን ብቻ እንድትወስድ አዘው አሰናበቷት። ሥቃይዋ ግን ከምትችለው በላይ ሆነባት። በመንጋጋዋ አካባቢ ብቻ ተወስኖ የነበረው የህመም ስሜቷ፤ ጭንቅላቷን ክፉኛ ወደሚበጠብጥ ከባድ የራስ ምታት ህመም ተለወጠ። ዓይኗን መግለጥ እስከሚያቅታት ድረስ በራስ ምታት ህመሙ ተሰቃየች። አፏን እንደልቧ መክፈት መዝጋቱ የማይታሰብ ሆነባት። በስቃይ ለመናገርም ሆነ ምግብ ለመዋጥ አፏን በከፈተች ቁጥር የሚሰነፍጥና እጅግ የሚያስጠላ መጥፎ ጠረን ከአፏ መውጣት ጀመረ። ይህም ህይወቷን የበለጠ መራራና ከባድ አደረገባት። ቀናት እየጨመሩ በሄዱ ቁጥር፣ ሥቃይዋ ከአቅሟ በላይ እየሆነ ሔደ። ቢቸግራት እዛው ፒያሳ ወደሚገኝ ሌላ የጥርስ ክሊኒክ ለህመሟ ማስታገሻ ፍለጋ ሄደች። “የክሊኒኩ ሃኪም የረባ ምርመራ እንኳን ሳያደርግልኝ ሁለቱ መንጋጋዎቼ መነቀል እንዳለባቸው ነገረኝ” ትላለች። በቂ ገንዘብ አልያዝኩም በሚል ሰበብ ከክሊኒኩ ለ ቃ እንደወጣችም ት ናግራለች።

የ ህመም ስሜት ያላት ቀደም ሲል በተነቀለችው ጥርስ ቦታ የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች አሳሳቢ ደረጃ ላይ ናቸው ተባለ በከተማችን ካሉ የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች በትክክለኛ ባለሙያ የታገዘ ህክምና የሚሰጡት ከግማሽ በታች ናቸው ለጥርስ ህክምና እስከ 25 ሺህ ብር ድረስ የሚያስከፍሉ ክሊኒኮች አሉ ላይ መሆኑን እያወቀች፣ ሌላ ጥርስ መነቀል አለበት የሚለውን ውሳኔ አላመነችበትም። የትዕግስት ስቃይ እረፍት አልባ መሆኑ ካሳሰባቸው ጓደኞቿ አንዷ፣ ትዕግስትን ይዛ ወደ ራስ ደስታ ሆስፒታል ሄደች። በሆስፒታሉ በተደረገላት ምርመራ፣ የጥርሷ ዋንኛው አቃፊ ውስጠኛው ክፍል (Root Canal) ቀደም ሲል በተፈፀመና አግባብ ባልሆነ የጥርስ መንቀል ሂደት ሳቢያ በከፍተኛ ሁኔታ መጎዳቱንና መመረዙን፣ ህክምናውንም በአገር ውስጥ ለማከናወን አስቸጋሪ እንደሆነ ተነገሯት። አስቸኳይ ህክምና ካላደረገችም ችግሩ እየጨመረ ሄዶ፣ ወደ ሌሎች የሰውነትዋ ክፍሎች በተለይም ወደ ጭንቅላት ነርቮቿ የሚሰራጭ መሆኑን ዶክተሮች አረዷት። ለህክምናው ያስፈልጋል የተባለችውን ገንዘብ ስትሰማ ሰማይ ምድሩ ዞረባት። “ውጪ አገር ሄደሽ ከ290 ሺህ ብር በላይ የሚፈጅ ህክምና ማድረግ አለብሽ” ተባለች። ይህንን ወጪ ሸፍና ህክምናውን ለማግኘት አቅም የላትም። ለዓመታት በስምንት መቶ ብር ወርሃዊ ደመወዝ የመርካቶው ይርጋ ሃይሌ ህንፃ ውስጥ በልብስ መሸጫ መደብር ውስጥ ነው የሰራችው።

እሱንም ቢሆን በዚሁ የጥርስ ህመሟ ሳቢያ ከለቀቀች ወራት አልፈዋል እናም ለህክምናዋ የሚሆን ገንዘብ የምታገኝበት አማራጭ በማጣትዋ ቀደም ሲል በሥራ አጋጣሚ የተዋወቀቻቸውን ሰዎችና ሌሎች በጎ አድራጊ ግለሰቦችን እርዳታ ለመጠየቅ ተገዳለች። በአሁኑ ወቅት በሆስፒታሉ የሚደረግላትን የህክምና እርዳታ በመከታተል፣ ከህመሟ ጊዜያዊ እፎይታን ለማግኘት እንደቻለችም ትናግራለች በራስ ደስታ ሆስፒታል በተደረገላት ህክምና የድዷ ቁስለት እየዳነ መሄዱን፣ ከሰዎች ጋር እንዳትነጋገር አድርጓት የነበረው የአፍ ጠረኗ፣ በእጅጉ እየተሻሻለ እንደሆነ ገልፃለች። ትዕግስት በጥርስ ህክምና ሰበብ የደረሰባትን ይህንን የጤና ችግር ልትነግረኝ አብረን የቆየንባቸው ጥቂት ደቂቃዎችን ለእኔ እጅግ የፈተና ነበሩ። “አሁን እጅግ ተሻሽሏል” የተባለው የአፍ ጠረኗ ቀደም ሲል ምን አይነት ቢሆን ነው አስብሎኛል። ትዕግስት በጥርስ ህክምና ሰበብ በየመንደሩና በየጉራንጉሩ ውስጥ እየተከፈቱ በታካሚው ህይወትና ጤና ላይ “ቁማር የሚጫወቱ” የምትላቸውን የጥርስ ክሊኒኮች የሚቆጣጠርና አሰራራቸውን የሚከታተል አካል ባለመኖሩ ምክንያት እንደእሷ ሁሉ እጅግ በርካቶች አደገኛ ለሆኑ የጤና ችግሮች መጋለጣቸውን ትናገራለች።

ክሊኒኮቹ የህክምና መሳሪያዎቻቸውን በንፅህና የማይጠብቁ በመሆናቸው፣ ኤችአይቪን ጨምሮ ሌሎች ተላላፊ በሽታዎችን ከአንዱ ወደ አንዱ በቀላሉ የሚያስተላልፍ የበሽታ መፈልፈያ ቦታዎች ሆነዋል ስትል በምሬት ገልፀለች። ለካርድ ተብላ በከፈለችው 50 ብር እና ለጥርስ መንቀያ ባስከፈልዋት 120 ብር ጤናዋን ሳይሆን የእድሜ ልክ በሽታዋን ሸምታ መውጣቷ እጅግ እንደሚያሳዝናት የምትናገረው ትዕግስት፤ መንግስትና ጉዳዩ የሚመለከታቸው ወገኖች የጥርስ ህክምና ክሊኒክ እየተባሉ በየጉራንጉሩ የሚከፈቱትንና በከተማዋ ውስጥ እንደ አሸን የፈሉትን ክሊኒኮች ቁጥጥር ሊያደርጉባቸውና አሰራራቸውን ሊከታተሏቸው ይገባል ትላለች። ለወገኖቻቸው ህይወት ቅንጣት ደንታ በሌላቸው አንዳንድ ራስ ወዳድ ሰዎች፣ የብዙ ሰዎች ህይወት ሊበላሽ አይገባውም ስትልም በቁጭት ትቆዝማለች። “ህብረተሰቡም ለጥርስ ህክምና በሚሄድበት ጊዜ ህክምናው በምን ዓይነት ሁኔታና በማን እንደሚሰጠው ማወቅ ይኖርበታል። ከእኔ ሊማርም ይገባል ባይ ናት።

የጥርስ ህክምና ሊሰጥ የሚገባው በሙያው በአግባቡ በሰለጠኑና ስፔሻላይዝድ ባደረጉ የህክምና ባለሙያዎች ሲሆን ሃኪሞቹ ማንነታቸውንና ደረጃቸውን የሚገልፅ ባጅ፣ በግልጽ በሚታይ ሁኔታ በደረታቸው ላይ ማንጠልጠል እንደሚኖርባቸው የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ያወጣው የህክምና መመሪያ (Guideline) ይጠቁማል። የህክምና መገልገያ መሳሪያዎቹ ጥራትና ንፅህናቸው በአግባቡ የተጠበቀ፣ የህክምና መስጫ ስፍራው የታካሚውን ደህንነት በአስተማማኝ ሁኔታ የሚጠብቅና ለድንገተኛ የጤና ችግሮች አስተማማኝ ዝግጅት ያለው መሆን እንደሚገባውም ይገልፃል። ይሁን እንጂ ይህንን ዘገባ ለማዘጋጀት ተዘዋውሬ ካየኋቸው፣ በጎጃም በረንዳና በአትክልት ተራ አካባቢ ከሚገኙ የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች በአንደኛውም ከላይ የተገለፁትን መስፈርቶች የሚያሟሉ ክሊኒኮችን አላየሁም። አብዛኛዎቹ ክሊኒኮች ለህክምና ሥራ አመቺ ባልሆነ ሥፍራ የተሰሩና የንፅህናቸው ሁኔታ እጅግ አሳሳቢ ደረጃ ላ ይ ነ ው። ከ ዚህ በ ተጨማሪም በ ክሊኒኮቹ ደጃፍ ላይ እንደተሰቀለው ማስታወቂያ ሁሉ ህክምናው በስቴራላይዘር ከበሽታ ንፁህ ሆነው በፀዱ መሳሪያዎች የሚሰጥ መሆኑን የሚያረጋግጡ ነገሮችን ለማየት አልቻልኩም።

ለቅኝት በተዘዋወርኩባቸውና በፒያሣው አትክልት ተራ አካባቢ በብዛት ከሚገኙት የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች በአንዱ ውስጥ ያገኘሁት አንድ “የህክምና ባለሙያ” በክሊኒካቸው የስቴራላይዘር መሳሪያ አለመኖሩን ገልፆ “ህክምናውን የምንሰጠው ለአንድ ሰው አንድ በሆነ ወይንም ከአንድ ጊዜ በላይ አገልግሎት ላይ በማይውሉ መሳሪያዎች ነው ብሎኛል። ይህ አባባሉ ግን እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ደሃ አገራት ቀርቶ በለፀጉ በሚባሉት አገራት ውስጥ እንኳን ሊሆን እንደማይችል ግልፅ ነው። እጅግ ውድ ዋጋ የሚያወጡ መሳሪያዎችን ከአንድ ጊዜ በላይ አንጠቀምባቸውም ማለቱ የማይመስል ነገር ነው። ላለፉት 10 ዓመታት በጥርስ ህክምና ሙያ ውስጥ የቆዩት ዶክተር የኋላሸት ስመኘው ይህንኑ ጉዳይ አስመልክተው ሲናገሩ፤ በአሁኑ ወቅት በከተማዋ ከሚገኙት የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች አብዛኛዎቹ እጅግ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሳቸውን ጠቁመው የመሣሪያዎቹ ንፅህና አጠባበቅና የባለሙያዎቹ ብቃት ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች ናቸው ብለዋል። የጥርስ ህክምና መሳሪያዎች ለአንድ ሰው አገልግሎት ከሰጡ በኋላ ለሌላ ሰው ጥቅም ላይ ከመዋላቸው በፊት እስከ 30 ደቂቃ ለሚሆን ጊዜ በበረኪና በሚገባ መዘፍዘፍና በሚገባ መታጠብ ይኖርባቸዋል፤ በአግባቡ ተዘፍዝፈውና ታጥበው የፀዱት ዕቃዎች አውቶክሌቭ ወደተባለውና ዕቃዎቹን በአግባቡ ለመቀቀል ወደሚያስችለው መሳሪያ መግባት ይኖርባቸዋል።

ከዚህ በኋላ ነው ዕቃዎቹ ከበሽታ ነፃ ሆኑ የሚባለው። በዚህ ሁኔታ የፀዱ መሳሪያዎች፣ የታካሚውን ጤንነት በአስተማማኝ ሁኔታ የሚጠብቁ ናቸው ብለዋል። ግን በተጠቀሱት ስፍራዎች ይህንን የዶክተር የኋላሸት ስመኘውን አባባል የሚያረጋግጡ አንዳችም ክሊኒኮች ለማየት አልቻልንም። ለቅኝት ከተዘዋወርንባቸው የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች ውስጥ በተሟላ መሳሪያና በሙያው በሚገባ በሰለጠኑ ብቁ ባለሙያዎች ተደራጀተው ለታካሚው አገልግሎት በመስጠት ላይ ያሉ ጥቂት ክሊኒኮችንም ታዝበናል። ፒያሳ እሪ በከንቱ አካባቢ፣ ሃያ ሁለትና መገናኛ አካባቢ ያየናቸው የጥርስ ህክምና ክሊኒኮች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው። በእነዚህ ክሊኒኮች ለደንበኞቻቸው አግባብ ያለው ህክምና ሲሰጡ ከተመለከትናቸው ጥቂት ክሊኒኮች የሚሰጠው የጥርስ ህክምና በሙያው በሚገባ በሰለጠኑ ብቁ ባለሙያዎች እና ንፅህናቸው በአግባቡ በተጠበቀላቸው መሳሪያዎች መሆኑን በስፍራው ተገኝተን ለመታዘብ ችለናል። ክሊኒኮቹ ለአገልግታቸው የሚስከፍሉት ዋጋ ከሌሎች ክሊኒኮች ጋር ሲነፃፀር ዳጎስ ያለ ነው ሊባል ይችላል። በእነዚህ ክሊኒኮች ውስጥ አንድ ጥርስ ከመነቀሉ በፊት ሊታከም መቻል አለመቻሉ በራጅ ምርመራና ሌሎች መሰል የምርመራ አይነቶች እንዲረጋገጥ ይደረጋል። ታካሚው ለህክምናው የሚያወጣው ወጪም እነዚህን ጉዳዮች ከግምት ውስጥ ያስገባ ነው።

ታካሚው ጥርሱ ተጨማሪ ምርመራ እንዲደረግለት የማይፈልግና መነቀል ብቻ እንደሚፈልግ ከተናገረ ባለሙያዎቹ አገልግሎቱን እጅግ በተመቻቸና ብዙም የህመም ስሜት በሌለበት ሁኔታ ያከናውኑታል። ለዚህ ህክምናም እስከ 400 ብር የሚደርስ ክፍያ ደንበኛው ይጠየቃል። ከዚህ በተረፈ የተወላገዱ፣ ያለአግባብ የበቀሉ፣ ነርቮቻቸው የተበላሹና ህክምና የሚያስፈልጋቸው ጥርሶች ሁሉ በእነዚህ ሥፍራዎች ተገቢው ህክምና ይደረግላቸዋል። ክሊኒኮቹ ለአገልግሎታቸው እስከ ሰላሳ ሺህ ብር የሚደርስ ገንዘብ ያስከፍላሉ። በዓለማችን የተለያዩ አገራት ለጥርስ ህክምና የሚወጣው ወጪ (የሚከፈለው ክፍያ) እጅግ ከፍተኛ ነው። በካናዳ አንድን ጥርስ ለመነቀል አሊያም ለማስሞላት እስከ አንድ ሺህ ሁለት መቶ የካናዳ ዶላር የሚያስከፍል ሲሆን ይህም በእኛ ገንዘብ ሲመነዘር ከሃያ ሁለት ሺህ ብር በላይ የሚጠይቅ ነው። በስዊድን ተመሳሳይ ህክምና ለማግኘት ከአራት እስከ አምስት ሺህ ክሩነር (በእኛ ከ12 እስከ 15 ሺ ብር) የሚደርስ ገንዘብ ይጠይቃል።በዚህ ምክንያትም አብዛኛዎቹ ዲያስፖራዎች ቤተሰቦቻቸውን ለመጎብኘት ወደ ኢትዮጵያ ብቅ ባሉ ቁጥር፣ የጥርስ ህክምና ክሊኒኮችን ሳይጎበኙ አይሄዱም።

የፒያሣው ጎጀብ ክሊኒክ በበርካታ ዲያስፖራዎችና የውጭ አገር ዜጎች በመጎብኘት ቀዳሚውን ሥፍራ ይይዛል። ዲያስፖራዎቹና የውጭ አገር ዜጎቹ የተበላሸና የሚታከም ጥርስ ባይኖራቸው እንኳን ስምንት መቶ ብር እየተከፈለ የሚሰጠውን ሙሉ የጥርስ እጥበት አገልግሎት ፍለጋ የክሊኒኩን በር ያንኳኳሉ። በአገራችን የሚገኙትንና በጣት ሊቆጠሩ የሚችሉትን የጥርስ ህክምና ስፔሻሊስት ሐኪሞች በእነዚህ ሥፍራዎች እንደልብ ማግኘት ይቻላል። አቅምዎ ከፈቀደና መክፈል ከቻሉ በመረጡትና ቀልብዎ በወደደው ብቁ ባለሙያ መታከም ይችላሉ።

Read 7151 times