Print this page
Monday, 27 January 2014 08:46

ሳያሽ የጐረሰ ዝንጀሮ በሳል ይሞታል

Written by 
Rate this item
(6 votes)

አንዳንድ ዕውነተኛ ታሪክ ሲቆይ ተረት ይመስላል፡፡ የሚከተለው ትርክት እንዲያ ያለ ጠባይ አለው:-
ሰውየው እሥረኛ ነበሩ አሉ፡፡ በጥንት ዘመን፡፡ ዚቀኛ ናቸው - ነገር አዋቂ፡፡
እሥረኞች “የሻማ” የሚሉት ፈሊጥ አላቸው፡፡ የኢኮኖሚ እርዳታ ነው አንዱ፡፡ የመዝናኛ ጥያቄ ነው ሁለተኛው፡፡
ጠያቂው እሥረኛ - በምን ታሠሩ? አላቸው፡፡
አዲሱ እሥረኛ - አለቃዬ ጠፍቶ
ጠያቂው እሥረኛ - ለምን ጠፋ?
አዲሱ እሥረኛ - ለሠራዊት የመጣ የዩኒፎርም ጨርቅ ወደ መርካቶ አሻግሮ
ጠያቂው እሥረኛ - ታዲያ እርሶ ምን አገባዎት?
አዲሱ እሥረኛ - እሱ እስኪመጣ እዚህ ተቀመጥ ተብዬ ነው
ጠያቂው እሥረኛ - እሺ አሁን እርሶ ምንድነዎት ታዲያ ?
አዲሱ እሥረኛ - ቀብድ ነኛ!
ሁሉንም አሳቋቸው፡፡
እሥረኛው ዋሉ አደሩና ለምርመራ ተጠሩ፡፡
ሄደው ሲመለሱ ፊታቸው ቀልቷል፡፡ ንዴትና እልህ እየተናነቃቸው ነው! የሚቀርባቸው እሥረኛ ጠጋ ብሎ አነጋገራቸው፡፡
“ምነው ከፍቶዎታል?” አላቸው
“መርማሪው አበሳጨኝ!”
“ለምን?”
“ቀበሌህን ተናገር አለኝ - አላውቅም አልኩት”
“ምን ነካዎት አድራሻ መደበቅማ አይቻልም፡፡ መናገር ነበረብዎት!”
“እኔ እምቢ አልኩት - ስለማላምንበትም ነው፡፡ ጣጣው ብዙ ነው”
“እንዴት ነው የማያምኑበት”
“ቆይ ላጫውትህ… አንድ ልጅ ቄስ ት/ቤት ይማራል አሉ፡፡ አንድ ቀን ተገርፎ ወደቤቱ እያለቀሰ ይመጣል፡፡
እናቱ - “ምን ሆንክ ልጄ” ስትል ትጠይቀዋለች፡፡
ልጁም እየተነፋረቀ፤ “እኚህ የኔታ መቱኝ” ይላታል፡፡
“ምን አድርገሃቸው መቱህ?”
“ሀ በል ሲሉኝ ጊዜ እምቢ አልኳቸው”
“አንተ የሞትክ! ሀ ማለት አቅቶህ ትገረፋለህ?”
“አይ እማዬ የኔታን አታውቂያቸውም፡፡የየኔታ ጉዳቸው መች ያልቃል? - ሀ ስትይ ሁ በይ ይሉሻል። ሁ ስትይ ሂ በይ ይሉሻል…እንዲህ እያሉ እስከ “ፐ” ያለፉሻል!...”
*    *    *
ጣጣው የማያልቅ ችግር ለትውልድ ይተርፋል፡፡ በትምህርት ከሀ እስከ ፐ መጓዝ የማይናቅ መሆኑ ባይካድም፤ ውጣ - ውረዱ፣ መከራው ሰቆቃው አይጣል ነው፡፡ ችግርን ከምንጩ መንቀል ብልህነት ነው። ከፊደልም ከህይወትም መማር ሙሉ ያደርገናል፡፡ ለለውጥ ዝግጁ የምንሆነው አንድም ዕውቀታችን ወደ ጥበብ ሲበስል፤ አንድም ለአዲስ ነገር አዕምሮአችን ክፍት ሲሆን፤እንዲሁም ከስህተታችን ለመማር እንችል ዘንድ ግትርነትን ስናስወግድ ነው፡፡
በሀገራችን የታሪክ ሂደት፤ ትግል፣ ድርድር፣ ዕርቅና ስምምነት፣ ጠቅልሎ ገብቶ ከመንግሥት ጋር መሥራት፣ መጣላትና መክዳት አዘውትረው የታዩ ክስተቶች ናቸው፡፡
በተለይ መከዳዳት እጅግ ተደጋግሞ የታየ ነው፡፡
“ወዳጅን አንዴ መክዳት ይቻላል ሁለት ጊዜ ግን አይቻልም” ceasy to rat but not to re – rat) ይላሉ ዊንስተን ቸርችል፡፡ ትግል ሲከር፣ ዘመን ሲከዳ፣ አቋም ሲሟሽሽ፣ ተስፋ ሲጠፋ፣ በተለይም ወኔ ሲከዳ፤ አሊያም አቋም ሲለወጥ፤ እናት - ክፍልን ትቶ ወደሌላ ሠፈር ይገባል፡፡
መደራደር፣ ዕርቅና መስማማት ከጦርነት እኩል ሜዳ ላይ ናቸው ይባላል፡፡ ጂኬ ቴስተርተን እንደሚለን “መደራደርና መስማማት ማለት ግማሽ ዳቦ ማግኘት ከምንም ይሻላል ነበር፡፡ አሁን ግን በዘመናዊ መንግሥታት ዘንድ ግማሽ ዳቦ ከሙሉ ዳቦ ይሻላል በሚል ተለውጧል”፡፡ ተደራድሮ አንድ ነገር ማግኘት ታላቅ ነገር ነው፡፡ ሆኖም መደራደርን እጅ ከመስጠትና ከክዳት ለይቶ ማየት ያሻል፡፡ ከማጐብደድ መለየት የስፈልጋል፡፡
ደራሲና ፀሐፌ - ተውኔት ፀጋዬ ገ/መድህን “በምኒልክ” ተውኔቱ ያለውን አለመርሳት ደግ ነው። “ሸዋም ያው ያባት ልምዱን፣ የባህል ግብሩን፣ በጐበና ሹመት ላይ አጉተመተመ፡፡ አጉረመረመ፡፡ ያኑ የሆድ ክፋት ቅርሱን፣ ምሱን፣ የምቀኛ ተውሳኩን፣ ውስጥ ውስጡን አቀረሸ፡፡ “ማናቸውን ንጉሥ እንበል?!” እያለ፤ ይሄ አዲሱ ጐበና፣ የልቼው ሳይሆን፣ ራሱን እንደንጉሥ ላስጠራ ባይ ተቆናኝ ሆኗል፤ መሾሙንስ ምኒልክ ሾመው፣ መሻሩንስ ማን ይሽርለት ይሆን? እያለ…”
ወገን ሳይኖር፣ አጋር ሳይኖር፣ በዙሪያ ደግ - አሳቢ ሳይኖር፤ ሹመት የዛፍ ላይ እንቅልፍ ነው! በእርግጥ አያሌ ከእናት ፓርቲያቸው የተለያዩ የጥንት የጧት ሰዎች እናውቃለን፡፡ ምናልባትም እነሱም የራሳቸው ምክንያት ይኖራቸው ይሆናል፡፡ ለአንድ የእንግሊዝ ፓርላማ ቀዳማዊት ኤልሣቤጥ አደረጉት የሚባል ንግግር ላይ “እንደኔ ከሆነ፤ ለምን መኖርን መውደድ እንዳለብኝ ወይም ለምን መሞትን መፍራት እንዳለብኝ አንዳችም ምክንያት የለኝም፡፡ የዚህችን ዐለም በቂ ልምድ አግኝቻለሁ፡፡ ዜጋ መሆንም፤ መሪ መሆንም ምን ማለት እንደሆነ አውቄያለሁ፡፡ መጥፎም ጥሩም ጐረቤት ኖሮኝ ያውቃል፡፡ ስለዚህ በራሴ ዕምነት መክዳት ጥሩ እንደሆን ተገንዝቤአለሁ፤ ብለዋል፡፡ ደግና ክፉ መለየት ያለበት ራሱ ባለቤቱ ነው።
የዱሮም ይሁን የአሁን ወዳጅ፣ ከጊዜ በኋላ፤ አቋም ለውጠው ሲገናኙ እንዴት እንደሚገናኙ፣  እንዴት እንደሚወያዩ፤ ግራ ሊገባቸው ይችላል፡፡ ሆድ ለሆድ ተግባብተው? ተቂያቂመው? ወይስ ይቅር ለእግዚሃር ተባብለው፤ ስለአገር ጉዳይ ተስማምተን እንሥራ ተባብለው?
በየትኛውም የሹመት ደረጃ ብንሆን፤ አገርን የሚጐዳ ከሆነ ሥልጣን በቃኝ ማለት መክዳት አይደለም የእንግሊዝ ተወላጁ የአውስትራሊያ ጠቅላይ ሚኒስትር አንዴ ሀይለኛ ግምገማ ተደርጐ አይምሬ የሆነ ግልጽ ሂስ ሲካሄድባቸው፤ “እኔምኮ ዶሮ እስኪጮህ ነበር የምጠብቀው ሥልጣኔን ለመልቀቅ” አሉ፤ አሉ፡፡ የፖለቲካ ሥልጣንን፤ ተዋግተንም እናምጣው፣ በሰላማዊ ድርድር፤ አሊያም ደጅ ጠንተን፤ ዳገት ቁልቁለት የሌለበት፣ በወርቅ አልጋ፣ በእርግብ ላባ ላይ መተኛት ነው ብሎ ማሰብ፤ ቢያንስ የዋኅነት ነው። “ሳያሽ የጐረሠ ዝንጀሮ በሳል ይመታል” ማለት ይሄው ነው፡፡

Read 5164 times
Administrator

Latest from Administrator