Sunday, 19 January 2014 00:00

“አንድነት” የኢትዮ-ሱዳን ድንበር ጉዳይ ለህዝብ ግልጽ እንዲሆን ጠየቀ

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(11 votes)

በግል መጽሄቶች ላይ የቀረበውን ጥናት ተቃውሟል

መንግስት የኢትዮ- ሱዳን ድንበር ጉዳይን ለህዝብ ግልፅ እንዲያደርግ አንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት አና ለአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር በጻፈው ደብደቤ መጠየቁን አስታውቆ፣ በጉዳዩ ላይ ከአዲስ አበባ ህዝብ ጋር ለመወያየት ቀጠሮ መያዙን ገለጸ፡፡ ፓርቲው በሰጠው መግለጫ፣ ሰሞኑን በሚዲያዎች አጀንዳ ሆኖ የሰነበተውን የኢትዮ-ሱዳን ድንበር ማሻሻል ጉዳይ በጥልቅ እየከታተለው መሆኑን አመልክቶ፣ ህዝቡ የድንበር ማካለል ሂደቱን ጉዳይ የማወቅ መብት እንዳለው መንግስት ተገንዝቦ ጉዳዩን ይፋ እንዲያደርግ አሳስቧል፡፡

መንግስት በሉአላዊነት ጉዳይ ላይ ብቻውን የመወሰን መብት የለውም ያሉት የፖርቲው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ በደፈናው በድንበር ጉዳይ ስምምነት ላይ ተደርሷል የሚል መግለጫ መሠጠቱ አግባብ አይደለም ብለዋል፡፡ በጉዳዩ ላይ ፓርቲያቸው ከአዲስ አበባ ህዝብ ጋር ለመወያየት ለጥር 18 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጠሮ መያዙን ኃላፊው ገልጸዋል፡፡ በውይይቱ ላይ የድንበር ማካለል ላይ ኤክስፐርቶች ሃሣብ እንደሚሠጡም ኃላፊው አስታውቀዋል፡፡ በሌላ በኩል፤ አንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ በቅርቡ የግል መጽሄቶችንና ኘሬሶችን በተመለከተ የቀረበውን የጥናት ውጤት አጥብቆ እንደሚቃወምና ሪፖርቱ የህብረተሰቡን ሃሣብን በነጻነት የመግለጽ መብት የሚገድብ በመሆኑ ሊጤን ይገባዋል ብሏል፡፡ ፓርቲው ኢህአዴግ ከዚህ ጥናት ሪፖርት በመነሣት የተወሰኑ ሚዲያዎችን ለማፈን እንደተዘጋጀ በግምገማው መረዳቱን አቶ ሀብታሙ ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡

Read 3416 times