Saturday, 04 January 2014 10:35

ህገመንግስትን የሚቃረን አንቀጽ ከፀረሙስና አዋጅ እንዲሰረዝ ተወሰነ

Written by 
Rate this item
(6 votes)

የፌዴሬሽን ምክር ቤት በፓርላማ የወጣውን ህግ ሲያሻሽል አሁን የመጀመሪይው ነው፡፡ የቀድሞ መከላከያ ሚኒስትር አቶ ስዬ አብርሃ ተመሳሳይ ጥያቄ አቅርበው ውድቅ ተደርጐባቸው ነበር፡፡
“በሚኒስትር ማዕረግ የገቢዎችና ጉምሩክ ባስልጣን ዋና ዳሬክተር አቶ መላኩ ፈንታ ላይ የቀረበው የሙስና ክስ መታየት ያለበት በከፍተኛ ፍ/ቤት ነው ወይስ በጠቅላይ ፍ/ቤትን” በሚል ለተነሳው ጉዳይ ምላሽ ለመስጠት ለሰዓታት የተከራከሩ የፌደሬሽን ምክር ቤት አባላት፤ የሚኒስትሮች ክስ በጠቅላይ ፍ/ቤት እንዲታይ የሚደነግገው አንቀጽ ከፀረ ሙስና አዋጁ እንዲሰረዝ በ76 የድጋፍና በ8 የተቃውሞ ድምጽ ወሰኑ፡፡
የሙስና ክሶችን በቀዳሚነት የመዳኘት ስልጣን የከፍተኛ ፍ/ቤት እንደሆነ የሚገልፀው የፀረሙስና አዋጅ፣ ሚኒስትሮች ሊከሰሱ ግን በቀጥታ ወደ ጠቅላይ ፍ/ቤት እንደሚቀርብ ይገልፃል፡፡ በ1993 ዓ.ም ኢህአዴግ ውስጥ በተከሰተው ፀብ ከፓርቲው አመራርነት የተባረሩት የቀድሞ መከላከያ ሚኒስትር ስዬ አብርሃ፣ በወቅቱ በሙስና መከሰሳቸው የሚታወቅ ሊሆን፣  ጉዳያቸው በቀጥታ በጠቅላይ ፍ/ቤት እንዲታይ መደረጉን ተቃውመው እንደነበር ይታወሳል፡፡ እንደሌሎች ተከሳሾች የአቶ ስዬ ክስ በከፍተኛ ፍ/ቤት እንዲታይ መከራከሪያ ያቀረቡት ጠበቃ፤ አለበለዚያ ግን ይግባኝ የመጠየቅ የተከሳሽ ህገመንግስታዊ መብትን የሚጥስ ይሆናል ብለዋል፡፡  በፀረ ሙስና አዋጅ የተካተተው አንቀጽ ህገመንግስቱን ስለሚቃረን ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ቀርቦ ውሳኔ እንዲሰጥበት የአቶ ስዬ ጠበቃ ቢከራከሩም፤ ፍ/ቤቱ ጥያቄውን ውድቅ ማድረጉ ይታወሳል፡፡
ጥያቄው እንደገና ፍ/ቤት ውስጥ የተነሳው ከአስር አመታት በኋላ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ከፍተኛ ሃላፊዎች ላይ ከተመሰረተው ክስ ጋር ተያይዞ ነው፡፡ በአንድ በኩል ዋና ዳሬክተሩ አቶ መላኩ ፈንታ በሚኒስትርነት ማዕረግ የተሾሙ በመሆናቸው፣ በፀረ ሙስና አዋጁ መሰረት ጉዳያቸው በጠቅላይ ፍ/ቤት መታየት ይገባዋል የሚል አስተያየት ቀርቧል፡፡ የፀረ ሙስና ኮሚሽን አቃቤ ህጐች፣ በበኩላቸው ሁሉም ሰው በህግ ፊት እኩል እንደሆነ በህገመንግስት ውስጥ በግልጽ ስለሰፈረ፣ የሁሉም ተከሳሾች ጉዳይ በከፍተኛ ፍ/ቤት መታየት አለበት በማለት ተከራክረዋል፡፡ ፍ/ቤቱም፤ የአዋጁ አንቀፆች ከህገመንግስቱ ጋር እንደሚጋጩ ወይም እንደማይጋይጩ የመወሰንና ለዚህ ክርክር እልባት የመስጠት ስልጣን እንደሌለው በመግለጽ ነው፣ ጉዳዩን ለፌዴሬሽን ም/ቤት ያስተላለፈው፡፡  
በፌደሬሽን ምክር ቤት ስር የተቋቋመው የህገመንግስት ጉዳዮች የአጣሪ ጉባኤ፣ ጉዳዩን ከመረመረ በኋላ የውሣኔ ሃሳብ ያዘጋጀ ሲሆን፣ የምክር ቤቱ አባላት ለበርካታ ሰዓታት ተከራክረውበታል፡፡
“በፀረ ሙስና አዋጅ የተካተተው አንቀጽ ህገ መንግስቱን ስለማይፃረር ባለበት ይቀጥል፤ እንዲያውም ህገመንግስቱን የሚያስከብር ነው” በማለት አስተያየት የሰነዘሩ አባላት፤  “ባለስልጣናት በሙስና ሲባልጉ አምነው የተቀበሉትን ህገመንግስት ስለሚጥሱ ይግባኝ በሌለበት ሁኔታ ፍርዳቸው መታየቱ ተገቢ ነው” ብለዋል፡፡ አንዳንድ የምክር ቤቱ አባላት በበኩላቸው  ጉዳዩ ክብደትና እና ጥልቀት ያለው መሆኑን በመጠቆም ጉዳዩን ለማጤን የተሰጠው ጊዜ አጭር ነው የሚል ሃሳብ አቅርበዋል፡፡
በሌላ በኩል፤ “የይግባኝ መብት የሚጣሰው የአቶ መላኩ ብቻ ሳይሆን የአቃቤ ህግም ነው” በማለት የተከራከሩ አባላት፣ ጉዳዩ በከፍተኛው ፍ/ቤት መታየቱ ሁለቱንም ይጠቅማል ብለዋል፡፡ ይግባኝ በሌለበት ሁኔታ ፍርዳቸው መታየት አለበት በሚል የተሰነዘረውን ሃሳብ በመቃወም  ምላሽ የሰጡት የአጣሪ ጉባኤው አባል አቶ ሚሊዮን አሰፋ “የሚኒስትሮች ክስ ከሌላው ሰው ተነጥሎ ይታይ” የሚል ሃሳብ በዜጐች መካከል የመደብ ልዩነት መኖሩን ከሚያመላክት ፊውዳላዊ አስተሳሰብ የሚመነጭ በመሆኑ ተገቢ አይደለም ብለዋል፡፡
በመጨረሻም፤ አከራካሪው አንቀጽ ህገመንግስቱን ስለሚቃረን ከፀረ ሙስና አዋጅ እንዲሰረዝ በ76 የድጋፍና በ8 የተቃውሞ ድምፅ የተወሰነ ሆን፣ እንዲህ ዓይነቱ ውሳኔ ለምክር ቤቱ የመጀመሪያው መሆኑን በመጠቆም ታሪካዊ ውሳኔ ነው በማለት አፈጉባኤው አቶ ካሳ ተክለብርሃን ተናግረዋል፡፡

Read 3579 times