Saturday, 28 December 2013 12:03

ዶ/ር ጌታቸው ተድላ እና ሜቄዶንያ

Written by 
Rate this item
(8 votes)

“ሰው ለማገልገል መፈጠር መታደል ነው”


ራስዎን ያስተዋውቁ …
ስሜ ጌታቸው ተድላ ይባላል፡፡ አሁን የምኖረው አዲስ አበባ ውስጥ ነው፡፡ ትምህርቴ በእርሻ ኢኮኖሚክስና በገጠር ልማት

ሲሆን የመጨረሻው ማዕረጌ PHD ነው፡፡ በዓለም ዙሪያ ብዙ አገሮች ላይ ሰርቻለሁ፡፡ ጡረታ ስወጣ አገሬ ላይ መጥቼ

መፃፍ የጀመርኩ ሲሆን እስካሁን  ወደ ስድስት ያህል መፃህፍትን ጽፌያለሁ፡፡
የመጽሐፍቱን ስም ቢዘረዝሩልኝ?
የመጀመሪያው መጽሀፌ የአባቴ የእርሻ ሥራ ላይ ያጠነጥናል፡፡ ሁለተኛው መጽሐፍ እኔ ሳልጽፈው ክቡር ፀሐፊ ትዕዛዝ

አክሊሉ ሃብተወልድ (በኃይለስላሴ ጊዜ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩ ናቸው) እስር ቤት ሆነው የፃፉትን ህዝብ ማወቅ

አለበት በሚል በአማርኛም በእንግሊዝኛም ተረጐምኩት። በመጨረሻም አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፕሬስ “የአክሊሉ

ማስታወሻ” በሚል አውጥቶት በርካታ ቅጂዎች ተሸጠዋል፡፡ ከዚያ በኋላ በራሴ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን “የህይወት

ጉዞዬና ትዝታዎቼ” የሚል መጽሐፍ ፃፍኩኝ። ይህን ከጨረስኩ በኋላ “ተስፋ የተወጠረች ህይወት” የሚል መጽሐፍ

ፃፍኩኝ። በደርግ ጊዜ ስድስት ልጆች ከዘመቻ ጠፍተው ወደ ጅቡቲ ሰባት ቀንና ሰባት ሌሊት የተጓዙበትን ታሪክ

ያሳያል፡፡ በመጨረሻም “ከትዝታ ጓዳ” እና “እንደወጡ የቀሩት ኢትዮጵያዊ” የሚል መጽሐፍ ለመፃፍ በቅቻለሁ፡፡
በተባበሩት መንግስታት ውስጥ ለረጅም ጊዜ መስራትዎ ይታወቃል፡፡ እስኪ የት የት እንደሰሩ ይንገሩኝ…
ከ20 አመት በላይ በተባበሩት መንግስታት የምግብና እርሻ ድርጅት (FAO) ነው የሰራሁት፡፡ በልዩ ልዩ አገሮች ለምሳሌ

በሌሴቶ፣ በታንዛኒያ እና በበርካታ አገሮች ሰርቻለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ በአለም የስራ ድርጅት (ILO) ውስጥ ገባሁና

በናይጀሪያ ለአምስት አመት ሰራሁ፡፡ መጨረሻ ላይ በሰላም ማስከበር ሥራ በኢራቅ የሰሜኑ ክፍል (ኩርዶች በሚኖሩበት)

ሁለት አመት፣ ባግዳድ ደግሞ ሁለት አመት በአጠቃላይ ለአራት አመት አገልግያለሁ፡፡ ሳዳም ሁሴን በነበሩበት ዘመን

ማለት ነው።  
ጡረታ ከወጡ በኋላ ከመጽሐፍ ውጭ ምን እየሰሩ ነው?
ከመጽሐፍ ውጭ በአሁኑ ሰዓት በበጐ አድራጊ ድርጅቶች ውስጥ በበጐ ፈቃደኝነት ነው የምሰራው። በዋናነት ሜቄዶንያ

የአረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን ማዕከል ውስጥ ብዙም ባይሆን የአቅሜን ለማድረግ እየጣርኩኝ እገኛለሁ፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ በወላጅ አልባ ህፃናት፣ በሴቶች ጥቃት፣ በትምህርትና የሴቶችን አቅም በመገንባት ዙሪያ የሚንቀሳቀሱ

የበጐ አድራጐት ድርጅቶች አሉ። እርስዎ ለምን ሜቄዶንያን መረጡ?
ሜቄዶንያን የመረጥኩበት ዋናው ምክንያት የአረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን ማዕከል በመሆኑ ነው። ብዙ በጐ አድራጐት

ድርጅቶች የሚሰሩት በህፃናት፣ በጉዲፈቻ እና በመሳሰሉት ላይ ነው። ሜቄዶንያ የሚሰራው ስራ በጣም ቅዱስና የተለየ

ነው፡፡ ይህን ስልሽ የሌላው መጥፎ ነው፤ ጥቅም የለውም ለማለት አይደለም። ሜቄዶንያ በትንሽ ብር ብዙ ስራ

የሚሰራበት፣ በጐ ፈቃደኞች ያለ ክፍያና ያለ ደሞዝ፣ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ፣ ሽንትና ሰገራ የማይቆጣጠሩትን ሳይጠየፉ

እያጠቡ እያገላበጡ የሚውሉ የሚያድሩበት ድርጅት ነው፡፡ ይህ በእውነት ልብ የሚነካ በመሆኑ የመረጥኩበት ዋነኛ

ምክንያቴ ነው፡፡ መስራቹ አቶ ቢኒያም በለጠን ውሰጅ… በጣም ወጣት ነው፤ ትልቅ ሰው ነው፤ የሚሰራውም ቅዱስ ስራ

ነው፡፡ ይህን የማይሞከር ስራ ሞክሮ ለዚህ የበቃ ፅኑ ልጅ ነው፤ ይህንን ልጅ ደግሞ ማገዝ አለብኝ በሚል ነው

የመረጥኩት፡፡
እንግዲህ በጐ ፈቃደኛ ሲኮን የግድ ገንዘብ ያለው መሆን አያስፈልግም፡፡ የሜቄዶንያ መስራች  የአቶ ቢኒያም መርህ

“ሰውን ለመርዳት ሰው መሆን በቂ ነው” የሚል ነው፡፡ እርስዎ በየትኛው ዘርፍ ነው እርዳታ የሚያደርጉት?   
እኔ እንግዲህ በተለያዩ ዘርፎች ነው የማገለግለው። በቻልኩት ሁሉ፡፡ ለምሳሌ በአስተዳደሩ በኩል እሰራለሁ። ከእኔ

መሰሎች ጋር ስድስት ሆነን “የአማካሪ ግሩፕ” በሚል ቡድን አቋቁመን የማማከር ስራ እንሰራለን። በገንዘብም በኩል

ቢሆን እውነት ለመናገር ያቅማችንን እያደረግን ነው፡፡ ለምሳሌ ታህሳስ 13 ቀን 2006 ዓ.ም በተደረገው የግሎባል ሆቴል

የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ላይ ለማሳተም 64ሺህ ብር ያወጣሁበትን “ከትዝታ ጓዳ” እና “እንደወጡ የቀሩት

ኢትዮጵያውያን” የተሰኙ ሁለት መፃህፍቶቼን 900 ያህል ቅጂዎች ለሽያጭ አቅርቤ ገቢ እንዲያገኙበት አድርጌያለሁ፡፡
እኔ ሁለቱን መፃህፍት በመቶ ብር እንዲሸጡ ነበር የተመንኩት፡፡ ነገር ግን እነሱ ሁለቱን በ150 ብር እንሸጣለን ብለው

በዚህ ዋጋ ሲሸጡ ነበር፡፡ ዘጠኝ መቶውም ካለቀ ወደ 135ሺህ ብር ገደማ ያገኙበታል ማለት ነው፡፡ ይህቺ የእኔ ትንሿ

አስተዋፅኦ ናት፡፡
በሜቄዶንያ ከሚገኙ 300 ያህል አረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን መካከል አይቼው በጣም ስሜቴን ነክቶታል የሚሏቸው

አሉ?
በአጠቃላይ እዛ ያሉት ሁሉ ልብ ይነካሉ፡፡ ነገር ግን እኔም ሆንኩ ባለቤቴ በጣም ልባችንን የነካው አልጋ ላይ ተኝቶ

የሚገኘው ጌዲዮን የተባለው ወጣት ነው፡፡ 24 ሰዓት እዛው እየተገላበጠ ነው የሚውል የሚያድረው። ሰውነቱ ከወገቡ

በታች ፓራላይዝድ ነው፡፡ (በነገራችን ላይ ጌዲዮን በጣም ወጣት፣ ቀይ፣ እጅግ መልከ መልካም ሲሆን መናገር ባይችልም

መስማት ግን ይችላል፡፡ አጠገቡ ያለች በጣም ወጣት አስታማሚና ተንከባካቢው ብቻ የአፉን እንቅስቃሴ አይታ

ትተረጉማለች፡፡ ከዚህ በፊት የሀብታም ቤተሰብ ልጅ ነበር ተብሏል) ይህ ወጣት በጣም ቆንጆና የሚያሳዝን ነው፡፡
አዲስ አድማስ ላይ የወጡት ኮሎኔል ታሪክም ያሳዝናል፤ ነገር ግን አሁን እርሳቸው በጥሩ ሁኔታ ላይ ነው የሚገኙት፡፡

ከሁሉም ከሁሉም ግን ማን ልቤን እንደሚነካው ታውቂያለሽ? የአዕምሮ ህሙማኑ አረጋዊያን እላያቸው ላይ ሲፀዳዱ

ተሯሩጠው የሚያፀዱትና ንፁህ የሚያደርጓቸው አስታማሚዎች ልቤን ይነኩታል። እውነቱን ልንገርሽ እኔ አላደርገውም፡፡

በዚህ መጠን ሰውን ለማገልገል መፈጠር መታደል ነው፡፡ እና እነዚህ በጐ ፈቃደኞች ዝም ብዬ ሳስባቸው ፅናታቸው

ልቤን ይነካዋል፡፡ እግዚአብሔር ይባርካቸው፡፡
ከመፃህፍቱ በተጨማሪ አንድ ስዕል ለጨረታ አቅርበው ነበር አይደል…?
አዎ! “የቴዎድሮስ የመጨረሻው የመቅደላ ጉዞ” የተሰኘ ስዕል ነበረኝ፡፡ ያወጣላቸውን ያህል ያውጣላቸው ብዬ

ሰጠኋቸው፡፡ ከ10ሺህ ተነስቶ መቶ ሺህ ብር ተሸጠ፡፡ በጣም የምወደው እና ሳሎኔ ውስጥ ሰቅዬው የነበረ ስዕል ነው፡፡

ቴዎድሮስ በፈረስ ላይ ሆነው ሰው ከቧቸው ሲጓዙ የሚያሳይ በጣም ማራኪ ስዕል ነው፡፡
ባለፈው እሁድ በግሎባል ሆቴል የተካሄደው የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም አጠቃላይ ድባብ ምን እንደሚመስል

ቢገልፁልኝ…
እውነት ለመናገር … የእሁዱ ፕሮግራም ከጠበቅነው በላይ ነበር፡፡ አንደኛ ከ3500 በላይ ሰው ተገኝቷል። በሁለተኛ ደረጃ

ሁሉም እጁን ዘርግቷል፤ በርካታ ብር ለግሷል፡፡ ለምሳሌ አንድ ስዕል ነበር፡፡ የአንዲት ሴት ስዕል ነው፡፡ ዝም ብሎ ስዕል

ነው፤ አንድ 20ሺህ ብር ቢያወጣልን ብለን ነበር የገመትነው፡፡ ነገር ግን 200ሺህ ብር ተሸጠ። ሌላ ስዕል ደግሞ 50ሺህ

ብር ቢያወጣልን ብለን አስበን 300ሺህ ተሸጠ፡፡ ብቻ ሰው የሜቄዶንያ ስራ ገብቶታል፤ መርዳት አለብን ብሎ አምኗል

ማለት ነው፡፡ ሌላው ስለሜቄዶንያ መታወቅ ያለበት በቀን አንድን ሰው ለመመገብ 20 ብር ያስፈልጋል፤ ለቁርስ፣ ምሳና

እራት ማለት ነው፡፡ አሁን ላሉት 300 ሰዎች በቀን 6ሺህ ብር እናወጣለን፡፡ በወር 180ሺህ ሲሆን በአመት 2 ሚሊዮን

አንድ መቶ ሰማኒያ ሺህ ብር ይወጣል፡፡ ይህ እንግዲህ ለምግብ ብቻ ነው። መድሀኒት፣ ልብስ፣ የንፅህና መጠበቂያ፣ እና

ሌሎችንም ሳይጨምር ነው፡፡ የዛሬ አመት ደግሞ ተረጂዎችን አንድ ሺህ የማድረግ እቅድ አለው፡፡ የሜቄዶንያ ተረጂዎቹ

አንድ ሺህ ሲደርሱ ለምግብ ብቻ ወጭው 20ሺህ ብር በቀን ይሆናል፡፡ በወር 600ሺህ ብር ይመጣል፣ በአመት ደግሞ

ወደ 5.5 ሚሊዮን ይሆናል፡፡ ይሄ ልጅ በእናትና አባቱ ቤት ነው 300ውን እየተንከባከበ ያለው፡፡
ታዲያ ተጨማሪ ቤት ሳይኖር እንዴት አንድ ሺህ ሰዎችን መርዳት ይቻላል?  
ያው መንግስት ሊሰጥ ያሰበውን 20ሺህ ሄክታር መሬት ቶሎ ቢሰጥና እዚያ ትልቅ ቤት ተሰርቶ አረጋዊያን ለብቻ፣

ሴቶችና ወንዶች ለብቻ፣ የአዕምሮ ህሙማን ለብቻ ሆነው፤ ክሊኒካቸዉ እዛው፣ ማረፊያቸውም እንዲሁ ሆኖ የተሻለ ስራ

መስራት ቢቻል ደስ ይለኛል፡፡ ቦታው ይገኝ እንጂ ግንባታው ጊዜ አይወስድም፤ ምክንያቱም ህዝብ ይገነባዋል የሚል

እምነት አለኝ፡፡
በእሁድ ዕለቱ ፕሮግራም በአጠቃላይ ምን ያህል ገቢ አገኛችሁ?
እኔ እስከማውቀው ከሶስት ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ተገኝቷል፡፡ ዲኤክስ መኪናም አግኝተናል፡፡ እግዚአብሔር ይመስገን፡፡
ከጨረታውና ከመሰል ነገሮች እንኳን ከ600ሺህ ብር በላይ ነው የተገኘው። ነገር ግን ወጪው ብዙ ነው፡፡ ያውም

ተጠንቅቀው ነው ገንዘቡን የሚያስተዳድሩት፡፡ ይገርምሻል… ሰው ማኮሮኒ ይዞ ይመጣል፣ ዱቄት ይዞ ይመጣል። በረከቱ

ነው መሰለኝ ተረጂዎቹ ጦማቸውን አድረው አያውቁም፡፡ ቢሆንም አሁንም እርዳታዎቹ ተጠናክረው መቀጠል

አለባቸው፡፡
በመጨረሻ ስለሜቄዶንያና ስለ መስራቹ አቶ ቢኒያም ምን የሚሉት ነገር አለ?
ኦ…ህ ስለ ቢኒያም ለመናገር እቸገራለሁ፡፡ እሁድ ዕለት እንኳን ንግግር ሳደርግ ስሜታዊ ሆኜ ነው ያለቀስኩት፡፡
ቢኒያም የእግዚአብሔር ሰው ነው፡፡ ለእነዚህ የአገር ባለውለታዎችና የአዕምሮ ህሙማን እግዚአብሔር የላከው ሰው ነው፡፡
በእንዲህ አይነት ጊዜ እንዲህ አይነት የተቀደሰ ስራ ለመስራት መመረጥና መታደል ያስፈልጋል። እኛ በእርሱ ዕድሜ

በነበርንበት ጊዜ ድግሪያችንን ይዘን፣ ፔኤች ዲ ይዘን፣ ንብረት አፍርተን፣ ቤት ትዳር ይዘን እያልን ነበር የምናስበው፡፡

እርሱ ግን  እንዴት ጉድጓድ ውስጥ የወደቁትን አንስቼ ያገግሙ እያለ ነው የሚጨነቀው፡፡ ይሄ በእውነት መታደል ነው።

ይህን ወጣት ማንኛውም ሰው ተሯሩጦ ማገዝ አለበት። አቶ ቢንያም እንዳለው “ሰውን ለመርዳት ሰው መሆን በቂ

ነው”፡፡
አመሰግናለሁ።  

Read 5263 times