Saturday, 28 December 2013 12:00

“አንጥረኛ” ቤተሰብና ታላላቅ ሥራዎቻቸው

Written by  ብርሃኑ ሰሙ
Rate this item
(7 votes)

አያታችን የአፄ ምኒልክን፣ አባታችን የአፄ ኃይለስላሴን ዘውድ ሰርተዋል
ወንድሜን ሙያውን ጀርመን አገር ያስተማሩት ንጉሱ ናቸው
የአክሱምና ላሊበላ መስቀሎችን ዲዛይን አሻሽሎ የሰራው አባቴ ነው
ወላጆቻቸው የአንኮበር ተወላጆች ናቸው። አባታቸው ከአንኮበር ጀምሮ በአዲስ አበባ ቤተመንግሥትም የወርቅና ብር

ጌጣጌጦች ባለሙያ ነበሩ፡፡ ከታላቅ ወንድማቸው ጋር በመሆን የአባታቸውን ሙያ ከልጅነት ዕድሜያቸው ጀምሮ

የቀሰሙት አቶ ይሔይስ ደጀኔ፤ በጀርመን አገርም ተጨማሪ ዕውቀት ገብይተዋል፡፡ ደምበል ሕንፃ ላይ “ይሔይስ ደጀኔ

የወርቅና ብር ሠሪ” የሚል መደብር ያላቸው አቶ ይሔይስ፤ “አባታችን በሙያው የነበረውን ዕውቀት ዛሬ በ76ተኛ

ዓመቴም አልደረስኩበትም” ይላሉ፡፡ በወርቅና በብር ከሚሰሩ ጌጣ ጌጦች ጋር በተያያዘ የቤተሰባቸውን ታሪክና ተያያዥ

ጉዳዮችን አውግተውናል።
ከትውልድዎና አስተዳደግዎ ይጀምሩልኝ…
በአዲስ አበባ ከተማ ጐላ ሠፈር በ1930 ዓ.ም ነው የተወለድኩት፡፡ በልጅነቴ ያመኝ ስለነበር፤ ከጐንደር የመጡ መምሬ

ቅሩብ የሚባሉ ቄስ ተቀጥረውልኝ ቤት ውስጥ ነበር ትምህርቴን የተከታተልኩት፡፡ ሌሎችም የጐላ ሠፈር ልጆች እየመጡ

እንማርበት የነበረው ቤት የእናቴ ወንድም ነበር፡፡ የቤተመንግሥት ካባ ሰፊና ሙካሽ ጠላፊ ባለሙያ የነበሩት አጐቴ፤

አቶ አድማሱ ኃይለማርያም ይባላሉ፡፡ የቄስ ትምህርቴን ፊደል ከመቁጠር ጀምሬ፣ ዳዊት በመድገም፣ በወንጌል ንባብ

ካዳበርኩ በኋላ፤ በመርካቶው ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን እንድቀድስ ተጠይቄ ነበረ፡፡ እኔ ግን ዘመናዊ ትምህርት

የመማር ፍላጐት ስለነበረኝ፣ በ1944 ዓ.ም ኮከበ ጽባሕ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ትምህርት ቤት ገባሁ፡፡
የትምህርት ቤታችን ርዕሰ መምህር ካርል ማይክል የሚባሉ አሜሪካዊ ነበሩ፡፡ 12ተኛ ክፍልን ካጠናቀቅኩ በኋላ

ለተጨማሪ ትምህርት ወደ ጀርመን አገር እንድሄድ ነገሮችን ያመቻቸልኝ ታላቅ ወንድሜ አቶ ክበርዬ ደጀኔ ነበር፡፡
ይህንን ያደረገበት ምክንያት ደግሞ፤ ቤተሰባችን ለተሰማራበት የአንጥረኝነት ሙያ እኔ ከፍተኛ ፍላጐት እንዳለኝ

በማስተዋሉ ነው፡፡ ታላቅ ወንድሜም ጀርመን አገር ድረስ ሄዶ ሙያውን ተምሮ ስለነበር፣ እኔም ወደዚያ እንድሄድ

ያመቻቸልኝ፤ በጀርመን አገር የሚያውቃቸውን ሰዎች በማነጋገር ነበር፡፡
እስቲ ወደኋላ መለስ ብለው የእናንተ ቤተሰብ ከአንጥረኝነት ሙያ ጋር በተያያዘ ያለው ታሪክ ምን እንደሚመስል

ይንገሩኝ…
የአባቴ አባት አቶ በላይነህ ዓለምነህ እና የእናቴ አባት አቶ ደገፉ ጋሼ፤ በአንኮበር ቤተመንግሥት በአንጥረኝነት ሙያ

ይሰሩ ነበር፡፡ በዚያ ወቅት መስቀልና የቤተክህነት ዕቃዎችን ሠርተዋል፡፡ አፄ ምኒልክ ሲነግሱ የተጠቀሙበትን ዘውድ

አርመናዊው ዲክራን አቢያን ሲሰራ፣ አያቴና ወንድሙ በሥራው ላይ ተሳትፈዋል፡፡ አፄ ኃይለሥላሴ ሲነግሱ

የተገለገሉበትን ዘውድ በመስራትም አባቴ ሙያዊ ዕውቀቱን አዋጥቷል፡፡ ከዚያም በኋላ ብዙ ነገር ሠርቷል፡፡
ጥንታዊውን የአክሱምና የላሊበላ መስቀሎችን ዲዛይን አሻሽሎ የሰራው አባቴ ነው፡፡ አሁን በአራት ኪሎ ቤተመንግሥት

አጥር ላይ የሚታየውና የቀዳማዊ ኃይለሥላሴን ሥም ምህፃረ ቃል በድርብ ዲዛይን የቀረፀውም እሱ ነው፡፡ የጃንሆይ

የክብር አልባሳት ቁልፎችንም ሠርቷል፡፡ የአፄ ኃይለሥላሴ የልብስ ቁልፍ በመጀመሪያ ተሰርቶ የመጣው ከእንግሊዝ

ነበር፡፡ ንጉሡ ከለንደን የመጣውን ዲዛይን ስላልወደዱት አባቴ አሻሽሎ እንዲሰራላቸው ጠይቀውት፣ የልብስ

ቁልፎቻቸውን በ21 ካራት ወርቅ ሠርቶላቸዋል፡፡
የንጉሡ የልብስ ቁልፎች ላይ ምን ዲዛይን ነበረ?
የአፄ ኃይለሥላሴ ልብስ የወርቅ ቁልፎች በተለያየ ዲዛይን ነበር የተሰራው፡፡ መሐሉ ላይ የቅዱስ ጊዮርጊስ አርማ ያለበት

አለ፡፡ ግራና ቀኝ የተጠላለፉ ሻምላዎችን አርማ የያዙም ቁልፎች ነበሩ፡፡ በክብ ቅርጽ የተሰሩት የልብስ ቁልፎች

በዙሪያቸው የዘንባባ ዲዛይን የተሰራላቸው ሲሆን ጫፋቸው ላይ ደግሞ የዘውድ አርማ አላቸው፡፡
አባትዎ በየትኛው ቤተመንግሥት ውስጥ ነበር እነዚህን ሥራዎች የሚሠሩት?
ከቤተመንግሥት ቅጥር ሠራተኞች አንዱ ሆኖ በአንጥረኝነት ሙያ ያገለገለው፤ በጃንሆይ ልዩ ግምጃ ቤት ውስጥ ነበር፡፡

ግምጃ ቤቱ በገንዘብ ሚኒስቴር ስር የሚተዳደር ሲሆን፤ ቦታውም አሁን 6 ኪሎ ዩኒቨርስቲ በሆነው ገነተ ልዑል

ቤተመንግሥት ውስጥ፤ ከማርቆስ ቤተክርስቲያን በስተጀርባ ነበር። ከአባቴ ጋር የሚሰሩ በጅሮንድ ማንደፍሮ የሚባሉ

ሌላ ኢትዮጵያዊም ነበሩ፡፡
በሙያው ላይ የተሰማሩ የውጭ አገር ሰዎችስ አልነበሩም?
የአንጥረኝነት ሙያ በአገራችን በሁለት መንገድ ተስፋፍቶ ነው ለዛሬ የደረሰው፡፡ አንደኛው፤ ከጥንት አክሱማዊያን አንስቶ

ትውልዶች እየተቀባበሉ እዚህ ያደረሱት ሲሆን፤ ሁለተኛው ከአፄ ምኒልክ ጊዜ አንስቶ ልዩ ልዩ ዕውቀት ያላቸው የተለያዩ

አገራት ባለሙያዎች ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡ ሲደረግ ከገቡት መሐል አርመኖችም ስለነበሩበት፣ እነሱ በአገራችን

የአንጥረኝነት ሙያ እንዲያድግና እንዲስፋፋ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡
አባታችን በንጉሠ ነገሥቱ ግምጃ ቤት በሚሰሩበት ዘመን፣ ፒያሳ ላይ የወርቅና ብር መስሪያና መሸጫ ያለው ሳቫጂያን

የሚባል አርመናዊ ነበር፡፡ በነገራችን ላይ የንጉሡ ግምጃ ቤት “ብር መኪና ቤት”ም ተብሎ ይጠራ ነበር። አባታችን

እንደነገረን፣ በ”ብር መኪና ቤት” ገንዘብ የማተም ሥራ፣ የወርቅና ብር ሥራ ብቻ ሳይሆን ከረሜላ ሁሉ ይመረትበት

ነበር፡፡
አባትዎ የሰሯቸው ሌሎች ሥራዎች ካሉ ቢነግሩኝ…
ለአፄ ኃይለሥላሴና ለቤተመንግሥት ብዙ ነገር ሠርቷል፡፡ የጃንሆይን የልብስ ቁልፎች ከአባቴ ውጭ ማንም

አልሰማራም፡፡ የሲጃራ መያዣ ሣጥን፣ የሴት ቦርሳ ጌጦች፣ የተለያዩ አገራት እንግዶች ሲመጡ፤ ጃንሆይ በሽልማትነት

የሚሰጧቸው ኒሻንና ሜዳሊያዎች፣ የወታደራዊ የማዕረግ ምልክቶች፣ የሸሚዝ እጅጌ ማስያዣ ቁልፎች (ከፊሊንግ)፣ የአበባ

ማስቀመጫዎችና የተለያዩ የሳሎን ጌጣጌጦች፤ በወርቅ፣ በብር፣ በዝሆን ጥርስና በአልማዝ ጭምር ሠርቷል፡፡
አርመናዊው ሳቫጂያንም ለቤተ መንግሥት ብዙ ነገሮችን ሠርቷል፡፡ ማህተም ይቀርጽ ነበር። ለወታደራዊ አገልግሎት

የሚውሉ ጌጣ ጌጦች፣ የማዕረግ ምልክቶችና የልብስ ቁልፎችን ይሰራ ነበር፡፡ የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ጥይት ፋብሪካም

በተመሳሳይ መልኩ በብዙ ሥራዎች ላይ ተሳትፏል፡፡
ከአፄ ኃይለሥላሴ ውጭ የልብስ ቁልፎችን በወርቅ ያሰራ ሌላ ማን አለ?
አንደኛ ሥራው በሚስጢር ነው የሚሰራው፡፡ ሁለተኛ የዲዛይን ሥራው የዳበረ ዕውቀትና ልምድ ስለሚጠይቅ፤ አሰራሩም

ጊዜ ስለሚወስድ ብዙ ሰው የልብስ ቁልፎችን ከወርቅ ሊያሰራ አይችልም። የማሰሪያ ዋጋውም ቢሆን ውድ ነው፡፡ ልዑል

ራስ አስራተ ካሳ ግን ከወርቅ የተሰራ የልብስ ቁልፎች ነበሯቸው፡፡
ታላቅ ወንድምዎ የወርቅና ብር ሥራን ለመማር ወደ ጀርመን መሄዳቸውን ገልፀውልኛል፡፡ እስቲ ስለ ወንድምዎ

ይንገሩኝ…
አቶ ክብርዬ ደጀኔ ታላቅ ወንድሜ ነው፡፡ አያታችን በአፄ ምኒልክ ዘውድ፣ አባታችን በአፄ ኃይለሥላሴ ዘውድ ሥራ ላይ

እንደመሳተፋቸው ሁሉ፤ አቶ ክብርዬም የሥላሴ ካቴድራልና የአክሱም ጽዮን ቤተክርስቲያናትን መንበር በብርና በወርቅ

በመሥራት ባለታሪክ ነው፡፡ ከልጅነቱ ጀምሮ አባታችን ወደሚሰራበት ቤተመንግሥት እየሄደ በመለማመድ ነበር ሙያውን

ያዳበረው፡፡ በየዓመቱ ለገና በዓል የአበባ ማስቀመጫ ከብር እየሰራ ለንጉሠ ነገሥቱ ያበረክትላቸው ነበር፡፡ ይህንን

ፍላጎቱን ያዩት አፄ ኃይለሥላሴ፤ ሙሉ ወጪውን ችለው ጀርመን አገር ሄዶ ሙያውን እንዲማር ረዱት፡፡ ከጀርመን

ሲመለስ ፒያሳ ከማህሙድ ሙዚቃ ቤት በታች፣ ሱቅ ከፍቶ በወርቅና ብር ሥራ ላይ ተሰማራ፡፡
እርስዎስ ለትምህርት ጀርመን የሄዱት እንዴት ነበር?
ታላቅ ወንድሜ ጀርመን በሄደበት ወቅት፣ ትምህርት በማይኖረኝ ጊዜ፤ ቤተመንግሥት እየሄድኩ አባታችንን በሥራ እረዳ

ነበር፡፡ ወንድሜ የፒያሳውን ሱቅ በ1954 ዓ.ም. ከከፈተም በኋላ በተመሳሳይ መልኩ በሥራው ላይ እሳተፍ ስለነበር፣

ለሙያው ያለኝን ፍቅርና ችሎታ ያየው ወንድሜ፤ ጀርመን ሄጄ እንድማር ሁኔታዎችን አመቻችቶ ሲልከኝ፣ የትራንስፖርት

ወጪዬን የሸፈኑልኝ ንጉሥ ኃይለሥላሴ ነበሩ፡፡
አባታችሁ በሙያቸው እያገለገሉ በቤተመንግሥት ሠራተኛነት የቆዩት ለምን ያህል ጊዜ ነው?
ጃንሆይ የጡረታ ዕድሜውን እያራዘሙለት ብዙ ቆይቷል፡፡ ንጉሡ ወርደው ደርግ የመንግሥት ስልጣን ሲይዝ፤ ኮሎኔል

መንግሥቱ ኃይለማርያም “እናውቃለን፤ ብዙ አገልግለዋል፤ ምንም የተሻለ ነገር ስላላገኙ ባለዎት ደሞዝ ጡረታ

እንዲወጡ ፈቅጃለሁ” ብሎት የቤተ መንግሥት ሠራተኛነት ሲያበቃ፤ ፒያሳ ወንድሜ በከፈተው ሱቅ ለብዙ ጊዜ

ሠርቷል፡፡ አሁን አባቴም ወንድሜም በሕይወት የሉም፡፡ እኔ ሙያውን ያስተማርኩት ታናሽ ወንድሜ ተመስገን ደጀኔ፤

በፒያሳ ወርቅ ቤት እየሰራ ነው፡፡ በውጭ አገር የሚኖሩ ወንድምና እህትም አሉን፡፡
እስቲ ስለ ጀርመን ትምህርትዎ ያጫውቱኝ…
የገባሁበት ትምህርት ቤት 26 ሠራተኞችና 150 ተማሪዎች ነበሩበት፡፡ 149ኙ ተማሪዎች ጀርመናዊያን ነበሩ፡፡ መጀመሪያ

ላይ ቋንቋቸው ቢያስቸግረኝም 6 ዓመት የሚፈጀውን ስልጠና በ3 ዓመት አጠናቅቄ ነው ዲፕሎማዬን ይዤ የመጣሁት፡፡

በብርና ወርቅ ሥራ ዲዛይን በማውጣትም ሆነ ያንን በትክክል ወደ ተግባር በመለወጥ ከልጅነቴ ጀምሮ የዳበረ ዕውቀት

ስለነበረኝ፤ ትምህርቱን በቶሎ ለማጠናቀቅ አስችሎኛል፡፡ ትምህርቱ የሙያ ብቻ ሳይሆን የዓለም ታሪክና ጠቅላላ

ዕውቀትንም ያካተተ ነበር፡፡ በዚህም በኩል ቢሆን አጥጋቢ ውጤት ነበር ያመጣሁት፡፡ በአገር ውስጥ ተማሪ እያለሁ

በሒሳብ ትምህርት ጎበዝ ነበርኩ፡፡ ስለ ኢትዮጵያ ታሪክ ብዙ ነገር ባናውቅም የዓለምን ታሪክ በስፋት ነበር የምንማረው፡፡

ይሄ የጀርመኑን ትምህርት ቀላል አድርጐልኛል፡፡
ከጀርመን ከመጡ በኋላ ሥራ የት ጀመሩ?  
ወንድሜ አቶ ክብርዬ፤ ከፒያሳውም በተጨማሪ በጊዮንና በሒልተን ሆቴሎች ተጨማሪ ሱቆችን ከፍቶ ስለነበር፣

ከጀርመን እንደመጣሁ ሥራ የጀመርኩት እሱ ጋር ነበር፡፡ በወቅቱ አባታችንም በቤተመንግሥት ይሰራ ስለነበር፣ ሦስታችን

በመተባበር ብዙ ሥራዎችን ሠርተናል፡፡ የአፄ ኃይለሥላሴ 80ኛ ዓመት የልደት በዓል ሲከበር ምድር ጦር፣ ፖሊስ

ሠራዊት፣ ፓርላማ፣ የሐረር ሕዝብ፣ የባሌ ሕዝብ … ትዕዛዝ እየሰጡን ልዩ ልዩ የስጦታ ዕቃዎችን፤ ከወርቅ ከብር፣

ከአልማዝ፣ ከከርከሮ ጥርስ … ሠርተናል። በዲዛይን ሥራዎቹ ላይ ሎሬት አፈወርቅ ተክሌም የተሳተፉባቸው ነበሩ።
እራስዎን ችለው መሥራት የጀመሩት መቼ ነው?
በ1968 ዓ.ም ጥቁር አንበሳ ትምህርት ቤት ፊት ለፊት “ይሔይስ ደጀኔ ወርቅና ብር ሠሪ” የሚል መደብር ከፈትኩ፡፡
ከዚያ በኋላ ለአገር ውስጥና ለውጭ ብዙ ታላላቅ ሰዎች በርካታ ጌጣጌጦችን ሠርቻለሁ፡፡ አልችልም ብዬ የምመልሰው

ሥራ የለም፡፡ እንዲህም ሆኖ በሙያው ላይ አባታችን የነበረውን ዕውቀት አሁን በ76ኛ ዓመቴም አልደረስኩበትም

እላለሁ፡፡
ለእኛ ዕውቀት መሠረት አባታችን እንደሆነው ሁሉ፣ እኔም ሙያውን ለሌሎች ኢትዮጵያዊያን በማስተማሬ ደስተኛ ነኝ፡፡

የወንድሜና የእኔም ልጆች የቤተሰባችንን ሙያ ማስቀጠል የሚያስችል ዕውቀት አላቸው፤ ሥራውንም በደንብ እየሰሩት

ነው፡፡
በመጨረሻ በአገራችን የወርቅና ብር ሥራ ያለበትን ደረጃ ቢነግሩኝ…
በወርቅና ብር ሥራ የላቀ ችሎታ ያላቸው ኢትዮጵያዊያን በየቦታው አሉ፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ አሉ የሚባሉት የከበሩ

ማዕድናትም ብዙዎቹ በአገራችን ይገኛሉ፡፡ እነዚህን ለመፈለግና ለመስራት ግን አንተጋም። የመስራት ስንፍና አለብን፡፡

ድሆች ተብለን የምንጠራው ለዚህ ነው፡፡ መንግሥትና ሕዝብ ከተባበሩ ይህ ችግር ይቀረፋል ብዬ አምናለሁ። ተባብረንና

ተከባብረን እንስራ የሚል መልዕክት ባስተላልፍ ደስ ይለኛል፡፡   

Read 3958 times