Saturday, 28 December 2013 11:39

‘የንጉሥ ቃል…’

Written by  ኤፍሬም እንዳለ
Rate this item
(7 votes)

እንዴት ሰነበታቸሁሳ!
መቼም ነገር ሥራችን ሁሉ ጠያቂ የጠፋበት አገር መስሏል፡፡ “በምን ምክንያት?” “እንዴት እንዲሀ ይሆናል?”  ምናምን

መባባል … አለ አይደል….የሀጢአት ሁሉ መጨረሻ ሆኖ ሁሉንም ነገር “እሺ!” ብቻ ሆኗል፡፡
‘በዛኛው’ ባለፈው ዘመን አንደኛው ባለስልጣን አሉ አድራጊ ፈጣሪው ሲበዛባቸው… “አንድ ንጉሥ አውርደን ሁለት መቶ

ሰማንያ አምስት አነገሥን….” ምናምን ነገር ብለዋል ይባል ነበር፡፡ ‘ያልተቀቡ ነገሥታት’ በዙባቸዋ!
ታዲያላችሁ…ዘንድሮ በአንድ በኩል ‘ተቀብተንም’… “አልወርድምም አልፈርድምም!” ብለን ቅዝምዝም ‘ዝቅ ብሎ

በማሳለፍ’ የተካንን ባለወንበሮች አለን፡፡ “ውሳኔ አልወስንም፣ ፊርማ አልፈርምም ብለህ ህዝብ አጉላልተሀል…” በሚል

‘ሀጢአተኛ’ የመባል ዕድሉ ጠባብ ነዋ—ያውም የሚባል ከተገኘ!
ደግሞላችሁ…በሌላ በኩል ደግሞ ማን ‘ቀብቶ’ እንዳስቀመጠን የማንታወቅ ንጉሦች እየበዛን ነው፡፡ የታክሲ ረዳቱ

‘ንጉሥ’፤ “ከመገናኛ ፒያሳ ስድስት ብር ነው…” ሲል “በአንተ መጀን” ብሎ መቀበል እንጂ…  “መንግሥት ያወጣው ታሪፍ

እያለ አንተን ማን ወሳኝ አደረገህ?” ብሎ ነገር የለም፡፡ ‘የንጉሥ ቃል’ ነዋ! የሚያስከትለው ጣጣ መአት ነዋ!
ሌላው ታክሲ ረዳት ‘ንጉሥ’… “ሃያ ሁለት ብቻ ነው የምጭነው…” ሲል “በአንተ መጀን” ብሎ መቀበል እንጂ…አለ

አይደል… “ታፔላህ ላይ አራት ኪሎ፣ ካዛንቺስ ይል የለም ወይ…” ብሎ ሙግት አያዋጣም፡፡ ‘የንጉሥ ቃል’ ነዋ!

የሚያስከትለው ጣጣ መአት ነዋ!
እናላችሁ…‘ተቀብተው’… አለ አይደል… “ባልፈርም፣ ባልፈራርም አትገለብጠኝ!” ከሚሉት ይልቅ ‘ሳይቀቡ’ “ምንስ ባደርግ

ምን ታመጣለህ?” የሚሉ እየበዙ ነው፡፡ (ልጄ…ለነገሩ ‘ለመቀባትም’ ስንትና ስንት መስፈርት አለ!)
የመሥሪያ ቤቱ የምንና የምናምን የሥራ ሂደት ባለቤት ‘ንጉሥ’……“መሥሪያ ቤታችን በዘንድሮ የበጀት ዓመት የዕቅዱን

ዘጠና በመቶ አሳክቷል…”  ሲል “በእርሶ መጀን” ብሎ መቀበል እንጂ…አለ አይደል… “ከዘጠናው ውስጥ ሰባ አምስቱን

ከየት አምጥተህ ነው የዶልከው…” ምናምን ብሎ ሙግት የለም፡፡ ‘የንጉሥ ቃል’ ነዋ! የሚያስከትለው ጣጣ መአት ነዋ!
እናላችሁ…ዙፋን ችሎት ሳይሰየም፣ ‘ሬፈረንደም’ ሳይጠራ…የሚተላለፉ ‘ንጉሣዊ’ ትእዛዛትና ያልተጻፉ ህግጋት እያስቸገሩ

ነው፡፡
ለነገሩማ ምን መሰላችሁ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ዘንድሮ ቦሶችን የሚያስቀይም ነገር እስካልተናገሩ ወይም

እስካላደረጉ ድረስ ‘ያልተቀባ ንጉሥ’ መሆን ይቻላል፡፡ ቀይ መስመር አልታለፈማ! ቀጪ፣ ተቆጪ የለማ!
እናላችሁ…የምግብ ቤት ባለቤት ‘ንጉሥ’ … ትናንትና በብር ከስሙኒ ይሸጠው የነበረውን ከቡና የጠቆረ ሻይ… “ከዛሬ

ጀምሮ የሻይ ዋጋ ሦስት ብር ከሽልንግ ነው…” ምናምን ሲል…አለ አይደል…“በአንተው መጀን” ብሎ መቀበል

እንጂ…“የስኳሩ ዋጋ ያው፣ የሻይ ቅጠሉ ዋጋ ያው…” ምናምን ብሎ ‘ጭቅጭቅ’ የለም፡፡ ‘የንጉሥ ቃል’ ነዋ!

የሚያስከትለው ጣጣ መአት ነዋ!
እናማ…ያልተቀባ ንጉሥ ሲበዛብን፣ የተቀባ ንጉሥ ሲዘባነንብን…አለ አይደል… ከዚህ በፊት እንዳወራነው “ይቺ አገር

ወዴት እየሄደች ነው…” ማለት ከጀርባው ‘ያለፈው ስርአት ናፋቂነት’ ምናምን ነገር ጉዳይ ሳይሆን… ግራ የመጋባት ጉዳይ

እንደሆነ ልብ ይባልልንማ፡፡
ስሙኝማ…ዘንድሮ እንደ ግል ትምህርት ቤት ባለቤቶች የተመቸው አለ! ልክ ነዋ ‘ተቀቡም አልተቀቡ’ እንደፈለጉ ዋጋ

መጫን ይችላሉዋ! በወር ክፍያ ላይ በአንድ ጊዜ አንድ ሺህና ሁለት ሺህ ብር ቢጨምሩ “በህግ አምላክ!” የሚላቸው ያለ

አይመስልም፡፡ እናላችሁ… የግል ትምህርት ቤት ባለቤት ‘ንጉሥ’… “ከዛሬ ጀምሮ በአንድ ተማሪ የወር ክፍያ ላይ አንድ

ሺህ ብር ጨምረናል…” ቢል…“በእርሶ መጀን” ብሎ መቀበል ነው እንጂ…“ምን ተጨማሪ ነገር አመጣችሁና ነው!” ምናምን

ብሎ ‘ጭቅጭቅ’ አያዋጣም፡፡ ‘የንጉሥ ቃል’ ነዋ! የሚያስከትለው ጣጣ መአት ነዋ!
ስሙኝማ…የግል ትምህርት ቤት ባለቤት አንድዬ ዘንድ ሲደርስ ምን የሚባል ይመስለኛል መሰላችሁ…
“ሥራህ ምን ነበር?”
“አንድዬ፣ የግል ትምህርት ቤት ባለቤት ነበርኩ።”
“እህ…አንተው ነህ? ስላንተ የሚነገረው አቤቱታ ከምድር አልፎ እኔንም እኮ ሲረብሸኝ ነው የከረመው። እንደው ለመሆኑ

እንዲህ ሰው ጤፉ የሆንከው ምን ተማምንህ ነው?”
“ጌታዬ ምን አደረግሁ…የህዝቡን ልጆች ባስተማርኩ፣ ድንጋይ እንዳይወረውሩና አማርኛ እንዳይናገሩ በህግ

ስለከለከልኩ…ደግሞ…”
“በቃህ፣ በቃህ!…ህጻናቱ በየጥጉ አደንዛዥ ዕፅ ሲያጨሱ የነበረው በአንተ ትምህርት ቤት አይደለም? እኔ ለአቅመ ዓዳምና

ሔዋን ስትበቁ ትደርሱበታላችሁ ያልኩትን ነገር ገና ጡጦ እንደጣሉ የሚለማመዱት በአንተ ትምህርት ቤት አይደለም!

በአሥራ ሦስት ዓመታቸው የሲጋራ ፓኮ በቦርሳቸው ይይዙ የነበሩት በአንተው ትምህርት ቤት አይደለም!”
“አንድዬ እኔ ምን ላድርግ፣ ወላጆቻቸው…”
“በቃህ፣ በቃሀ…የአንተ ጉዳይ አስቀድሞ የተወሰነ ስለሆነ ደብዳቤህን ሂድና ከመዝገብ ቤት ውሰድ…ደግሞ ስማኝ…”
“አቤት፣ አንድዬ…”
“ዲያብሎስን፣ ይኸው መልካም ወዳጅ ልኬልሀለሁ ብሎሀል በለው፡፡”
እናላችሁ…ያልተቀባን ነገሥታት በዝተናል። በሁሉም ነገር የእውቀት መጨረሻዎች እኛ እየሆንን ስትተነፍሱ

እያስፈቀዳችሁኝ ልንል ምንም የማይቀረን የቁጥራችን መብዛት ለጊነሱ መጽሐፍ ሊያደርስን ምንም አልቀረው፡፡ አይደለም

መልስ የሚሰጠን የትኛው እናቱ የወለደችው ነው ቀና ብሎ የሚያየን!
በዛ ሰሞን ኳሳችን ላይ “እህ…” ብሎ በጥልቀት ከመነጋጋር…አሼሼ ገዳሜው በቻ በዛና፣ “እንደው እዚች ቦታ አካባቢ

ቢታሰብበት…” ብሎ ነገር አስቸጋሪ ነበር፡፡ እናላችሁ…‘ያልተቀባ የኳስ ንጉሥ’…“የቡድናችንን ጨዋታ ድፍን ዓለም በጉጉት

እየጠበቀው ነው…” ሲል “በእርሶ መጀን” ብሎ መቀበል እንጂ…“ኧረ’ባካችሁ እንኳን የኳስ ቡድናችንን እኛ መኖራችንን

የማያውቅ ዓለም ብዙ ነው…” ብሎ ነገር የለም፡፡ ‘የንጉሥ ቃል’ ነዋ! የሚያስከትለው ጣጣ መአት ነዋ!
ስሙኝማ…‘ያልተቀባ ንጉሥ’ ሆኖ የከረመ የኳስ ሰው አንድዬ ዘንድ ሲደርስ ምን የሚባል ይመስለኛል መሰላችሁ…
“አንተ ደግሞ ሥራህ ምን ነበር?”
“አንድዬ ኳስ ተጫዋች ነበርኩ፡፡”
“ምን አልከኝ!”
“ቆይ..ቆይ እስቲ… ይሄን ያህል ችላ ብያችሁ ነበር እንዴ! ኳስ መጫወት ሥራ ሆኗል ነው የምትለኝ?”
“አዎ አንድዬ..”
“ማለት ኳስ ተጫውታችሁ የዕለት ጉርስ የዓመት ልብስ ታገኛላችሁ?”
“አዎ አንድዬ፣ ያውም በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ብር፡፡ ምን ይገርማል?”
“ይገርማል እንጂ…እኔ ጥረህ ግረህ በግንባርህ ወዝ ብላ አልኩ እንጂ ኳስ ስታሳድድ ውለህ ብላ አልኩ…ተወው ብቻ

ይቅር፡፡ እና ለህዝቡ ምን አደረጋችሁ?”
“እንዴ አንድዬ አልሰማሁም እንዳትል…”
“ምኑን?”
“ከሠላሳ አንድ ዓመት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ አልፈን ህዝቡን ፌሽታ በፌሽታ አድርገነው እንዴት አልሰማህም?”
“ተሞኝተሀል በለኛ፣ አምልጦሀል በለኛ…እኔ እኮ ከሠላሳ ምናምን ዓመት በኋላ የሚለውን ስትደጋገሙ ጎተራችን ሞላ፣

ወገናችን መራቡ ቆመ…ምናምን የምትሉ መስሎኝ ነበር፡፡ ኳስ ነበር እንዴ!”
“አንድዬ ድካማችንን ፉርሽ አታድርግብን እንጂ…”
“ይሁና… የአንተ ጉዳይ ሌላ ጊዜ ይታያል፡፡ እስከዛው እዛ ላሉና ገና ወደ እኔ ላልመጡ ዘመዶችህ ሠላሳ ምናምን ዓመት

እያላችሁ የምትደጋግሙት ነገር ሠላሳ የሚለውን ቁጥር ሊያስጠላኝ ስለሆነ ተዉኝ ብሏችኋል በልልኝ…”
እናላችሁ…የተቀቡም ያልተቀቡም ነገሥታት ኑሮን ከድጡ ወደማጡ እያደረጉብን ነው፡፡ ይኸው… በ‘ቦተሊካው’ እንኳን

እኛ ፍሬ ነገራችን ያልነውን የልብ፣ የልባችንን እንዳንተነፍስ ‘ነገሥታቱ’ ከወዲህና ከወዲያ  ቆቅ አየኝ በል እያሉን

ነው፡፡
ስሙኝማ…‘የተቀቡና፣ ያልተቀቡ ነገሥታት’ የሆኑት ‘ቦተሊከኞች’ አንድዬ ዘንድ ሲደርሱ ምን የሚባሉ ይመስለኛል

መሰላችሁ…
“አንተ ደግሞ ምን ነበርክ?”
“ፖለቲከኛ ነኛ!”
“ልታስቀኝ እየሞከርክ ነው፣ አይደል!”
“ኧረ በጭራሽ አንድዬ…በየመድረኩ ያንን ሁሉ ስለፈልፍ፣ በየጋዜጣው ላይ ፎቶዬን በትልቁ ገጭ አድርጌ ስወጣ፣

በየቴሌቪዥኑና በየሬድዮኑ የኢትዮጵያን የፖለቲካ ሁኔታ ስተነትን…ይሄን ጊዜ ሁሉ አይቼህ አላውቅም ነው የምትለኝ?”
“እኔን የገረመኝ ደግሞ ምን እንደሆነ ልንገርህ…በዛች አገር ፖለቲከኛ አለ ስትለኝ…”
“ሞልተናላ አንድዬ! በእርግጥ አንዳንዶቹ…”
“ቆይ ዝርዝሩን ተወውና ለህዝቤ ምን አደረጋችሁለት?”
“አንድዬ በእውነትም ረስተኸናል ማለት ነው፡፡ የፖለቲካ እውቀቱ እንዲዳብር፣ ጠላቶቹን እንዲለይ፣ ከጎረቤቱ ጋር

በዓይነ ቁራኛ እንዲጠባበቅ…ምን ያላደረግነው አለ! ደግሞ ሰዉ የሚበጀውን ስለማያውቅ የሚበጀውን እንዲያውቅ…”
“በቃህ፣ በቃህ…አንተ ወደ ዳር ሁን…”
“ጌታዬ አሁን ወስንና ወደ መንግሥተ ሰማያት…”
“መንግሥተ ሰማያት መግባትም አምሮሀል? ስማኝ እናንተን ዲያበሎስ ዘንድ ብልካችሁም ከተገባራችሁ ጋር

ስለማይመጣጠን…ሌላ ከገሀነም ጓዳ የጨለመ ቦታ እስካገኝላችሁ ወደመጣችሁበት ትመለሳላችሁ፡፡”
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል….ጠፍተው ከርመው ብቅ የሚሉ ሰዎችን ሳይ ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…አንድዬ

“ለእናንተ ቦታ እስኪያመቻች…” ብሎ የመለሳቸው! ቂ…ቂ…ቂ…
እናላችሁ…‘የተቀቡም፣ ያልተቀቡም ነገሥታት’ ቁጥር በዝቶብናል ይቀነስልንማ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Read 4244 times