Monday, 23 December 2013 09:36

የባህር ዳር ጉዞ - የአውራ አምባ ጉዞ ማኮብኮቢያ!

Written by  ነቢይ መኰንን
Rate this item
(0 votes)

“ብዙ በሠራህ ቁጥር ጥቂት ትናገራለህ፡፡ ምክንያቱም ጥርት አርገህ ታውቀዋለህ፡፡”
ተፈራ አባተ የፋና የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ማህበር ሥራ አስኪያጅ፡፡

ኅዳር 30/2006 ዓ.ም፤ የቀጠለው ጉዞዬ ወደ ፋና የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ማህበር ነበር፡፡ ይህኛው ማህበርም የቀጠለው ጉዞዬ ወደ ፋና የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ማህበር ነበር፡፡ በዚህኛው የፋና ጽሕፈት ቤት ተረጋግተን ተቀምጠን ነው ውይይቴን የቀጠልኩት፡፡
 “ፋና እንዴት ተመሠረተ?” አልኩት፤ ሥራ አስኪያጁን፡፡
“ፋና የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ማህበር የተመሠረተው… የኢየሩሣሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት (የእህማልድ) እዚህ ቀበሌ 12 ውስጥ ይሠራ ነበር - በ4 ፕሮግራም ላይ ይሠራ ነበር፡፡
ማለት 1) እናት አባት ያጡ ህፃናት 2) ጤና 3) ትምህርት 4) ኑሮ ማሻሻያ
እየሩሣሌም አንድ 4 ዓመት ቆይቶ ሲወጣ፣ የጀመረውን እኛ መልካም ሥራውን ተረከብን፡፡ ባጭሩ፤ ሥራውን የሚቀጥል ሰው መኖር ስላለበት ይሄ ማህበር እንዲመሠረት ሆነ፡፡ በማን? ብትለኝ፤ በቀበሌ 12 ማህበረሰብ ልማት መማክርት ከህብረተሰቡ የተመረጡ 72 የኮሚቴ አባላት ተገኙ፡፡ ሥ/አስኪያጅ ኮሚቴ ተመረጠ፡፡ ከዛ ከሥ/አ/ኮሚቴ ውስጥ ህዝቡ በሊቀመንበርነት መረጠኝ፡፡ ሁለተኛ ዙርም አሁን ተመርጬ ቀጠልኩ፡፡ መተዳደሪያ ደንቡ ተሻሻለና በቦርድ እንዲመራ ሆነ፡፡ በቦርድ ሲመራም እኔ በሥራ አስኪያጅነት ተመረጥኩ፤ ተሾምኩ፡፡
ቀበሌያችን የችግርተኞች ቀበሌ ነው፡፡ ጄክዶም መጀመሪያ የገባው ይሄ ችግር በጣም የጠነከረ መሆኑን አስቀድሞ ተገንዝቦ ነው፡፡ አብዛኛው ቤተሰብ በእማ - ወራዎች ነው የሚመራው!” አለኝ፡፡
“ለመሆኑ ጄክዶ ወደ ህብረተሰቡ መጣ፣ ወይስ ህብረተሰቡ ወደ ጄክዶ መጣ?” ብዬ ጠየኩት፡፡
“ቆሻሻን የማስወገድ፣ የፅዳት ጉዳይ፤ ነበረ ዋና ሥራው፡፡ ወላጆች ያጡ ህፃናት በርካታ ናቸው፡፡ ዝቅተኛው ማህበረሰብ ይበዛል፡፡ ጄክዶ መጀመሪያ የህብረተሰቡን ችግር አይቶ እየተንቀሳቀሰ ነበር፡፡ እኛ ችግሩ አስጨንቆን በኋላ ነው ተሰብስበን ምን እናድርግ የተባባልነው፡፡
“ችግሩስ አሳሳቢ ነበር ያኔ?”
ዳኛቸው ተቀበለ ለምላሹ፡፡
“ይሄውልህ ትንሽ ዘርዘር አርገን እንየው!
በ1977 ዓ.ም ጄክዶ ህፃናትን በካምፕ ይዞ ያሳድግ ነበር፡፡ ከኮሙኒቲ ጋር መሥራት የጀመረው እኛጋ ነው፡፡ ትልቁ ሥራው፤ ማህበረሰቡ ችግሩን እንዲያወጣ አደረገ፡፡ ደረጃ አወጣ፡፡ 14 ፕሮግራሞች ነደፈ፡፡ 4 ፕሮግራም በአቶ ተፈራ አስተባባሪነት ለኛ ተሰጠ፡፡ ማህበረሰቡ ተረከበ፡፡ የቤት ኪራይ ነው ዋና ገቢያችን፡፡ አመራሩ በህብረተሰቡ ተመርጦ ነው፡፡ ሀብቱን የሚያንቀሳቀስው ራሱ ህብረተሰቡ ነው፡፡ ቤት ኪራይ አለ፡፡ ባለሀብቶች አሉን፡፡ ዘላቂነት ላልከው ይሄ ነው ጉዳዩ፡፡ የግሼ አባይ ቀበሌ ህዝብ 20ሺ ይሆናል፡፡”
“20ሺ ከሆነ ብዙኮ ነው፤ እንዴት approach ታረጉታላችሁ (እንዴት ትቀርቡታላችሁ)?” አልኩ ቀጥዬ፡፡
“ይሄ 3 ቀበሌ ነው፡፡ የ3 ቀበሌ ውሁድ ነው… ግሼ አባይ ነው እሚባለው፡፡ ሥራችን ህፃናቱን፣ ሴቱን፣ አረጋዊውን፣ መንከባከብ ነው እኛ አጋርም አለን፡፡ “ጐህ ለሁሉ” ነው የሚባለው፡፡ ያ ማህበር ይመለምላል፡፡ እኛ እዚህ ቀጠና ሶስት ሆነን በህፃናት ላይ እንሰራለን፡፡ 01፣ 02፣ 03 ቀበሌዎች፡፡ የህፃናት መምረጫ መስፈርታችን:-
1ኛ/እናትም አባትም 2ቱንም ያጡ
2ኛ/ ከእናት ወይ ከአባት አንዱን ብቻ ያጡ
3ኛ/ሌላ ሰው/ቤተሰብ የሚያሳድጋቸው
4ኛ/ ቤተሰብ ኖሯቸውም የተጐሣቆለ ህይወት ውስጥ ያሉ፤  
ፍፁም ችግርተኞችና ለችግር የተጋለጡ ናቸው፡፡
“ዘላቂነታችሁስ?” አልኳቸው፡፡
“የፋና ማህበር፤ ለጋሽ ባይኖርም ይኖራል! እዚህ ደረጃ ደርሷልና ሥጋት የለብንም አየህ፤ አንድ ፕሪንሲፕል አለው መርህ አውጥተናል፡፡ “አንድ ሰው አንድ አረጋዊ ይያዝ!” የሚል፡፡ ስኬታማ ነን! 38 ደጋፊዎች 38 አረጋዊ በሚገባ ተንከባክበዋል፡፡ እኛ facilitate (የማመቻቸት ሥራ)  ነው የምናረገው በዓል ሲኖር አርደን ቅርጫ እናከፋፍላለን! ሁልጊዜ! ነገሩ ምንድን ነው፤ መቼም እነዚህ ሰዎች ከጥሩ ኑሮ የወረዱ ናቸው፡፡ እነዚህን የመርዳት፣ የማቋቋም ጥሩ ኑሮ የማኖር፤ ሥራ ነው የሠራነው! የፌዴራል ሠራተኛ እና ማህበራዊ ጉዳይ ሠርተፊኬት የሸለመን ለዚህ ነው፡፡ ብቸኛ ተሸላሚ ነን!
ጄክዶ ዳሞ በልምድ ልውውጥ አኳያ ክህሎታችንን በጣም ቀይሮታል!
“ለሥልጠና ከዚህ ካላችሁበት ወጥታችሁ ታውቃላችሁ? ሌሎች ማህበራትን አይታችኋል?” አልኩ፡፡
“በመላው ኢትዮጵያ ለማለት ትችላለህ፡፡ ድሬዳዋ፣ ጅማ፣ አዋሳ፣ ደብረዘይት… ምኑ ቅጡ! ብዙ ቦታ ዞረን የሚጐድለንን ቀስመን መጥተናል!! የምናውቀውን አሳውቀናል!!
ከጄክዶም ውጪ Oxfam Canada ጋር ጅማ ሄደናል፡፡ ፋና ሠለጠነ ማለት ልምዱን ሥራ ላይ አዋለ ማለት ነው፡፡ ሥልጠና በፀጉር ሥራ፣ በምግብ ዝግጅት፣ በሹፍርና፣ ሞባይልና ጥገና
4000 ብር ለአንድ ሰው አውጥተን፤ ከዚያ በ6000 ብር ለአንድ ሰው አሳደግነው፡፡ 14 የሚሆኑ ሹፌሮች አሠልጥነን አውጥተናል፡፡
“ቮለንታሪዝም (የበጐ-ፈቃድ ሥራ) ከባድ ይመስለኛል፤ ለምን ቀጠለ?”
በሥራው ስለምንረካ ነዋ!” …  
አሁን ምንም የምትቀምሰው የሌላት፤ እንዲህ ቁጭ ብላ ሲያያት ሰው ያዘነ እንደሆን የቡና ቁርስ ይሰጣት የነበረች ምስኪን ሴት፤ አሁን ግን ብዙም ባይሆን 100-150 ብር ስታገኝ፣ የራሷን ህይወት እንደልቧ ስትኖር ማየት ያረካል፡፡  ሠፈር ወጣቱ፤ ጨርሶ ውሃ ልክ ላይ እንዳይቀመጥ ውሃ ልኩ ላይ የተቃጠለ የመኪና ዘይት፤ እየቀቡ እንዲሸሽ ይደረግ የነበረ ወጣት፣ ሙሉ በሙሉ ሰው ጠልቷቸው የነብሩ ልጆችን፤ አሰልጥነህ … ዛሬ መኪናውን ሲያሽከረክር ስታየው…ይሄን ባልደረባችንን ዳኛቸውን፤ ጋሼ ሠርቪስ ልስጥህ?” ሲለው ስታይ፤ ቤቱ ቅርብ ቢሆንም ሲወስደው ስታይ፣ በበጐ ፈቃደኝነት መሥራትህ እርክት ያረግሃል!
እንደዛ የሚሉ ልጆችን ማግኘት በሆቴል በምግብም ደረጃ ቤተሰቦቻቸውን የለወጡ፤ የተዛባ ኑሮ የነበራቸውን ሰዎች ያቃኑ ማየት፣ እንዴት ልዩ ደስታ አይሰጥህም፤ በፓፒረስ ሆቴል ተቀጥረው ታያለህ፡፡ ቤተሰቦቻቸውን የለወጡ ወጣቶች፡፡ እንዲህ ያሉ ወጣቶችን ማግኘት ትልቅ ፀጋ ነው! በቃ ትረካለህ! ቀለብህ እሱ ነው! ሌላ ደሞዝ የለህም!
የበጐ ፈቃደኝነት ሚሥጥሩ ይሄው ነው!”
ዳኛቸው ገባበት፡-  
“አንድ ተቋም የራሱን ሪሶርስ ካየ Sustain ያደርጋል-ዘላቂነቱን ያውቃል፡፡ ከፈረንጅ የሚጠብቅ ነው Sustain ላያረግ የሚችል፡፡ የራስን ሀብት ማፈላለጊያ መንገድ ማግኘት ነው ዋናው! እኛ ጄክዶ መሠረት አሲዞናል፡፡ አሁን ደሞ ጤፍ አምጥተናል፡፡ በ4 ወር ውስጥ ቢያንስ አሥራ ምናምን ሺ ብር አትርፈናል፡፡ ህብረተሰቡ በአያያዛችን በጣም ከመተማመኑ የተነሳ፤
“እንዲህ ላሉ ህፃናት ማገልገል እፈልጋለሁ” የሚል ማህበረሰብ እያፈራን ነው፡፡ የራሱ ሥራ ባለቤት ማምጣት ደረጃ ላይ ነው!
ብዙ ዘመን አብረን ኖረናል፡፡ ለ2ኛ ጊዜ ተመርጠናል፡፡ ከጄክዶ ጋር መሥራት ችለናል፡፡ ደከመኝ ሰለቸኝ አለማለት መቻላችንም ቀላል አይመስለኝም፡፡”
አቶ  ተፈራ ቀጠሉና “ይሄን ለመረዳት ባለክሊኒኮች አሉ፡፡ የነሱን በጐ አድራጐት እይ፡፡ እናንተ ብዙ ልጆች ትረዳላችሁ እኔ ግን 10 ህፃናት በዓመት ባክም ምን አለበት?” ያለን ባለ ክሊኒክ አለ፡፡
“ኧረ ይበዛብሃል አትችለውም?” ብንል፤
“ህፃናቱ በዓመት አንዳንዴኮ ነው የሚታመሙት፤ ምንም ሊያሳስባችሁ አይገባም’ ነው ያለን- በሙሉ ልብ!”
አረጋውያንን ምን እንደምናደርግ ቸግሮን ባለበት ሰዓት ከደብረዘይት ተማርን - ሬክሰን ከሚባል ድርጅት ጋር፡፡ ውይይታችን አበቃ፡፡
የፋና ማህበር ልበ - ሙሉነት አርክቶኝ ነበር የተለያየነው፡፡
በልቤ . ከመሠረቱ የጠና ማኅበር እስከመጨረሻው ሊጓዝ መቻሉን፤
በማህበረሰባዊ ልማት ለረዥም ዓመታት መቆየት እንዴት ልምድ - ጠገብ እንደሚያደርግ
ሰው ከሰው ተገናኝቶ፣ ተወያይቶ፣ ልብ ለልብ ተገናኝቶ እንዴት የልቡን ማድረግ እንደሚችል፤
በማህበረሰቡ ላይ ዕምነት ማዳበር እንዴት ወሳኝ እንደሆነና
ሌሎች እድሮችን ማቀፍ እንዴት ዘርፈ-ብዙ ሥራ መሥራት እንደሚያስተምር፤ አሰብኩ፡፡ ከፋና የተማርኩት አመረቃኝ፡፡
ነገ ወደ አውራምባ ልሄድ ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ልሄድ አቅጄ ያልሄድኩበት ቦታ ነው፡፡ አሁን ሊሣካልኝ ነው መሰለኝ፡፡ በጣም ጓጉቻለሁ!!
የባህር ዳርን ባህል ቤቶች ልጐበኝ ዞር ዞር አልኩ፡፡ ብዙ አስደሳች ትውስታዎችን መዘገብኩ፡፡ ወደፊት በሰፊው እንደምጽፍባቸው አመንኩ፡፡
ሲመሻሽ ሆቴሌ ገብቼ፤ ፊቴን ወደ ዙምራ አዙሬ ተኛሁ!
(ጉዞዬ ወደ አውራምባ ይቀጥላል)

Read 2894 times