Saturday, 14 December 2013 12:43

ነዋሪዎች በሽታ የሚሸምቱባቸው የመዲናዋ ምግብ ቤቶች

Written by  መታሰቢያ ካሳዬ
Rate this item
(2 votes)

እርስዎ፤ በአዲስ አበባ የሚኖሩ የጥሬ ሥጋ ወዳጅና አድናቂ ከሆኑ አካባቢዎቹን በሚገባ ያውቋቸዋል፡፡ ህዝበ አዳም ተሰልፎ ጥሬውን ከጥብሱ የሚያማርጥባቸው ሥፍራዎች ናቸው። ከአዲሱ ገበያ  እስከ ገዳም ሰፈር፣ ከዶሮ ማነቂያ እስከ ልደታ ድረስ አካባቢዎቹ በጥሬ ሥጋ አቅርቦታቸው ይታወቃሉ፡፡ በተለይ፤ በደመወዝ ሰሞንና በሳምንቱ እረፍት ቀናት ቤቶቹ በቁርጥ ሥጋ ተመጋቢዎች በእጅጉ ይጨናነቃሉ፡፡ በእነዚህ ቤቶች እንኳንስ መቀመጫ መቆሚያ ሥፍራ ማግኘት ይቸግራል። ወንበርና ጠረጴዛ በወጉ አግኝቶ ከሚስተናገደው ተመጋቢ ቁጥር ይልቅ በትንንሽ ዱካዎችና የለስላሣ ሣጥኖች ላይ ተቀምጦ፤ ጥሬ ሥጋ የተቆለለበትን ትሪ ጉልበቱ ላይ አስቀምጦ የሚበላው ተመጋቢ ይበልጣል። ቤቶቹ “እስቲ ምሣ እየበላን እንጫወት” ለሚሉ አይነት ሰዎች (ቀጠሮዎች) በፍፁም አይመቹም። እየተጣደፉ ገብተው፣ ባገኙት ነገር ላይ ተቀምጠውና በጥድፊያ ተመግበው፣ በጥድፊያ ከፍለው ለሚወጡት ብቻ ነው የሚሆኑት፡፡
ታዲያ እነዚህን ቤቶች የሚያመሳስላቸው አንድ የጋራ ጉዳይ አላቸው፡፡ ከአዲሱ ገበያ እስከ ጊዮርጊስ፣ ከዶሮ ማነቂያ እስከ ልደታ ቤቶቹ የሚመሳሰሉባቸው ዋነኛው ጉዳይ የመፀዳጃ ቤቶቻቸውና የምግብ ማብሰያ ክፍሎቻቸው የተያያዙ መሆናቸው ነው። እዛው መፀዳጃ ቤቱ በራፍ ላይ ምግብ አብሣይ ሠራተኞች፣ ደንበኛ ያዘዘውን ምግብ ለማድረስ ተፍ ተፍ ሲሉ ይታያሉ። እጅግ የሚሰነፍጥ ሽታ ባለው መፀዳጃ ቤት ለደቂቃዎች የመቆየት ብርታት ካለዎት፣ የስንት ደንበኛ ምግብ ተሰርቶ እንደሚወጣ መቁጠር ይችላሉ፡፡
የዚህኑ መፀዳጃ ቤት ግድግዳ ተደግፈው ያዘዙት ምግብ መድረስ አለመድረሱን በጉጉት የሚጠባበቁ በርካታ የሆቴሉ ደንበኞች አሉ። በእነዚሁ ቤቶች የእጅ መታጠቢያውም የሚገኘው በመፀዳጃውና ማብሰያ ክፍሉ አካባቢ ነው፡፡ ከመፀዳጃ ቤቱ የሚሰማውን ነጐድጓዳዊ ድምፅ በጆሮ፣ የሚተነፍገውን ሽታ በአንፍጫ እየተቀበሉ መፀዳጃ ቤቱ ደጃፍ ላይ ተቀምጦ መመገብ ለበርካታ አዲስ አበቤዎች አዲስ ነገር አይደለም። በእዚህም ሳቢያ በቀላሉ ሊያልፍ ከሚችል ቀላል ህመም እስከሞት ለሚያደርሱ በሽታዎች መጋለጥ ለከተሜው ነዋሪ የተለመደ ነው፡፡
በ2002 ዓ.ም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የህክምና ፋኩሊቲ የተደረገ አንድ ጥናት እንደሚጠቁመው፤ በከተማዋ ውስጥ ከሚገኙና የመፀዳጃ ቤት አላቸው ተብለው ከተመዘገቡ አነስተኛ ምግብ ቤቶች ውስጥ 85 በመቶ የሚሆኑት የመፀዳጃ ቤቶቻቸውና  የማብሰያ ክፍሎቹ ተጐራባች ናቸው። መፀዳጃ ቤቶቹ በአብዛኛው ንፅህና የጐደላቸውና እጅግ የሚተነፍግ ሽታ ያላቸው ሲሆኑ፤ አንዳንዳቹም ወለላቸው የተበላሸና ለአይን በእጅጉ የሚያስፀይፉ ናቸው። በከተማዋ ከመመገቢያ ሥፍራ የራቁ ንፁህ የመፀዳጃ ቤቶች ያላቸው ምግብ ቤቶችን ማግኘት ይናፍቃል፡፡
ትቀልዳላችሁ? ምግብ ለመመገብ ከተቀመጣችሁበት የመፀዳጃ ቤቱ በራፍ ላይ ወደ መፀዳጃ ቤት የሚገባውን ሰው ለማሳለፍ አስር ጊዜ ብድግ ቁጭ ማለት ሁሉ ግድ ነው፡፡ ግን አማራጭ የለም፤ አብዛኛው የከተማው ነዋሪ ለመመገብ አቅም የሚኖረው በእነዚህ ቤቶች ነው፡፡ ምግቡንና ታይፎይዱን በአንድ ላይ በልቶ ከፍሎ ይወጣል። ታይፎይዱ ደግሞ ቆይቶ ያስከፍለዋል፡፡ ይህን አስተያየት የሰጠኝ በእነዚህ ምግብ ቤቶች ደንበኛ የሆነ ወጣት ነው፡፡  
እስከ 1995 ዓ.ም ድረስ የሆቴሎችና ምግብ አቅራቢ ድርጅቶችን የጥራትና ንፅህና ደረጃ በመቆጣጠር እርምጃ የመውሰድ ሃላፊነት የተሰጠው በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሥር ለሚገኘው “የጤናው ዘርፍ” የተባለ ክፍል ነበር፡፡ ከ1995 ዓ.ም በኋላ ግን ኃላፊነቱ ለከተማው ጤና ቢሮ ተሰጥቶ “ደንብ ማስከበር” በሚባሉ ኃይሎች ቁጥጥርና እርምጃ የመውሰዱ ተግባር እንዲቀጥል ተደረገ፡፡
ሆኖም ግን፤ ምግብ ቤቶቹን በየጊዜው የማየቱና የንፅህና ሁኔታቸውን የመቆጣጠሩ ጉዳይ ትኩረት ተሰጥቶት፣ በአግባቡና በሥርዓቱ ሊከናወን አልቻለም፡፡ በአጥፊዎቹ ላይም በቂ እርምጃ እየተወሰደ አይመስልም፡፡ በዚህም ሣቢያ ዛሬ አዲስ አበባችን በአብዛኛው መመገቢያና ማብሰያ ክፍሎቻቸው ከመፀዳጃ ቤቶቻቸው ጋር የተጐራበቱ ምግብ ቤቶች መናኸሪያ ለመሆን በቅታለች፡፡
በእነዚህ ምግብ ቤቶች የሚመገቡ ሰዎች እንደ ሺጌላ፣ ሳልሞኔላ፣ ካምፒሎባክተር፣ ኢ-ኮላይ-ሊስቴሪያና ቦቱሊኒየም ለመሳሰሉ በሽታ አምጪ ባክቴሪያዎች በቀላሉ ሊጋለጡ እንደሚችሉና በእነዚህ ባክቴሪያዎች ሣቢያ የሚመጡ በሽታዎችም እስከ ሞት ሊያደርሱ እንደሚችሉ የጤና ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡ በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል በላብራቶሪ ቴክኒሺያንነት ከ10 ዓመት በላይ ያገለገለው ሰለሞን ተካ እንደሚናገረው፤ የአብዛኛዎቹ ምግብ ወለድ በሽታዎች ምንጭ የሆኑት ባክቴሪያዎች፣ ቫይረሶችና ጥገኛ ትላትሎች በንፅህና ጉድለት የሚከሰቱና በተለይም በመፀዳጃ ቤት ሣቢያ ሊመጡ የሚችሉ ናቸው፡፡
የምግብ ማብሰያና የመፀዳጃ ክፍሎቻቸው  በተጐራበቱ ምግብ ቤቶች በመመገብ ሳቢያ ከሚከሰቱ በሽታዎች መካከል የሆድ ጥገኛ ትላትሎች፣ የአንጀት ቁስለትና ሄፒታይተስ ጥቂቶቹ እንደሆኑ የሚናገሩት የጤና ባለሙያዎች፤ በሽታዎቹም ህመምተኛውን ለሞት ሊያደርሱት እንደሚችሉ ይገልፃሉ፡፡
በበሽታው ተይዘው ለህክምና ወደ ሆስፒታሉ ከሚመጡና የላብራቶሪ ምርመራ ከሚታዘዝላቸው ህሙማን መካከል አብዛኛዎቹ የተበከለ ምግብና ውሃ ወለድ የሆኑ የተለያዩ የአንጀትና የሆድ ጥገኛ ትላትሎች በምርመራ እንደሚገኝባቸው የላብራቶሪ ባለሙያው ይናገራል፡፡
የከተማዋን ነዋሪ ጤና እጅግ አሣሣቢ ደረጃ ላይ ያደረሱት እነዚህ ምግብ ቤቶች፤ ፈቃዳቸውን በሚያድሱባቸውና የጤና ቢሮ ተቆጣጣሪዎች ይመጣሉ በሚባሉባቸው ጊዜያት፣ ክፍሎቻቸውን አፅድተውና አስፈላጊ የሆኑ ዕቃዎችን ሁሉ አሟልተው፣ አንዳንዴ ደግሞ ተቆጣጣሪ እየተባሉ ከሚላኩ ሠራተኞች ጋር በሙስና ተደራድረው ቁጥጥሩን ያልፋሉ፡፡ ከዚህ በኋላ ነፃ ወጡ ማለት ነው። ቤቶቹን በድጋሚ ዞር ብሎ የሚያይና ንፅህናቸውን የሚከታተል ባለመኖሩ የቀጣዩ አመት ፈቃድ እደሣ ጊዜ እስከሚደርስ ማብሰያ፣ መመገቢያና መፀዳጃ ክፍሎቻቸውን አቀላቅለው ከጤናችን እያጣሉን ይቀጥላሉ፡፡
85 በመቶ ይሆናሉ ተብለው በጥናቱ በተጠቀሱት ሆቴሎችና ምግብ ቤቶች በየዕለቱ የሚመገበው የከተሜ ነዋሪ ቁጥር ቀላል አይደለም። ይሄ ደግሞ ሁኔታውን እጅግ አሣሣቢ ያደርገዋል። ይህንን ችግር ለማስወገድና የህብረተሰቡን አሳሳቢ የጤና ሁኔታ ለመታደግ የሚቻለው ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ የየድርሻቸውን መወጣት ሲችሉ ቢሆንም፤ ህብረተሰቡም ለራሱ ጤና ማሰብ ይገባዋልና ከእነዚህ አይነት መመገቢያ ሥፍራዎች ራሱን በመቆጠብ፣ የሚመገብበትን አካባቢ መምረጥ ይገባዋል፡፡ ታሞ ከመማቀቅ አስቀድሞ መጠንቀቅ እንዲሉ፡፡

Read 5072 times