Saturday, 30 November 2013 11:04

ሰርቆ የሚያውቅ፣ በምልክት ያስራል የወላይትኛ ተረት (ከይሰት ቤእደይ መላት ጐዜስ)

Written by 
Rate this item
(11 votes)

ከዕለታት አንድ ቀን ሶስት ትላልቅ ገበሬዎች በጣም አባያ ሆነው በየጫካው እየደነበሩ እፅዋቱን እየረመረሙ አገር-ምድሩን እያመሱ አስቸገሩ፡፡ የዱር አራዊቱ ሁሉ በግዙፍነታቸውና በጉልበተኝነታቸው ፈሯቸው፡፡ የደኑ አራዊት አንድ ቀን ተሰበሰቡና
“እነዚህን በሬዎች ምን ብናደርግ ነው በቀላሉ ልንበላቸው የምንችለው?” ይባባሉ ጀመር፡፡ ሆኖም ሁሉም ፈሩ፡፡ የበሬዎቹ ትላልቅ መሆን ከወኔያቸው በላይ ሆነ፡፡ ስለዚህም ምንም ሳያረጉዋቸው ቆዩ፡፡
አንድ ቀን አንድ ብልጥ ጅብ መጣና “ቆይ ግዴላችሁም፤ እኔ እነዚህን በሬዎች እነጣጥልላችኋለሁ” አለ፡፡ ከዚያም ወደ በሬዎቹ ሄደና እንዲህ አላቸው፡-
“እባካችሁ ተራ በተራ ላናግራችሁ እፈልግ ነበር፡፡ ትፈቅዱልኛላችሁ?”
በሬዎቹም፤
“እንደፈለክ ልታናግረን ትችላለህ” አሉት፡፡
አያ ጅቦም በመጀመሪያ ጥቁሩን በሬ ጠርቶ፤
“ከእናንተ መካከል የነጩ በሬ ነገር ያሳስበኛል”
“ለምን ያሳስብሃል?” አለና ጠየቀ ጥቁሩ በሬ፡፡
“ጠላቶች ከሩቁ በነጩ ቆዳው ምክንያት ይለዩታል፡፡ ስለዚህም በቀላሉ ስለሚለዩዋችሁ ያጠቋችኋል፡፡ የሚሻለው ገለል ብታደርጉት ነው-ተመካከሩበት” አለው፡፡
በሬዎቹ ተመካከሩና ነጩ በሬ ለብቻው ራቅ ብሎ እንዲኖር አደረጉ፡፡ የደኑ አውሬዎች፤ ብቻውን ያገኙትን በሬ አድነው፣ አሳድደው በሉት፡፡ አያ ጅቦ ቀጠለና ጥቁሩን በሬ እንደገና ጠራው፡፡
“የዚህ የጓደኛህ የቀዩ በሬ ነገር በጣም አሳሳቢ ሆኖብኛል” አለው፡፡
“ለምን አሳሳቢ ሆነብህ?” አለው፡፡
“ምክንያቱም፤ ደም የመሰለ ቀይ በመሆኑ፤ ሰዎች ከሩቅ ይለዩታል፡፡ ስለሆነም ባንድ አፍታ የት እንዳላችሁ ይለዩና ይከታተሉዋችኋል! ራቅ አርገህ ብትልከው አንተ እንደዛፍ ወይም እንደዛፍ ጥላ የጠቆርክ በመሆንህ አይለዩህም” አለው፡፡
ጥቁሩ በሬም ሄዶ ለቀዩ በሬ ስለተባለው አደጋ አዋየው፡፡ ቀዩ በሬ ተስማማና ራቅ ወዳለ ቦታ ሄደ፡፡
ቀዩ በሬ ብቻውን ሲሆንላቸው የዱር አውሬዎቹ አሳደው ሰፈሩበት፡፡
በመጨረሻም ወንድም የሌለው ጥቁሩ በሬ በግላጭ ተገኘና የዱር አውሬዎች ሁሉ ተቀራመቱት፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ አያ ጅቦ “የአፍ-አጣፋጭ” የሚል ስም ወጣለት፡፡  
*   *   *
የባለተራ ደወል የሚለውን አለማሰብ የዋህነት ነው፡፡ አዳዲስ አካሄዳችንን አለማስተዋልም ጅልነት ነው! “እኔ እዚህ መሆኔ በቂ ነው” ከማለት ባሻገር፤ “እገሌ የት ደረሰ?” ማለት ያባት ነው፡፡ የኃይል ሚዛንን አውቆ ማን ምን እያደረገ ነው? ምን ዘዴ እየተጠቀመ ነው? ማለት ደግ ነው፡፡ “የከፋፍለህ ግዛውን መርህ የምንንቀውና የምንሳለቅበትን ያህል፤ ዕውነት ቢሆንስ? ማለት ከማኪያቬሊ ጀምሮ የኖረ ያለ፤ “ደባ” መሆኑን ማስተዋል ታላቅነት ነው፡፡
የሀገር፣ የህዝብ እና የተቋም ሚሥጥር ግራ ሊያጋባን አይገባም፡፡ የሚሥጥር ትርጉም ብዙዎችን ቢያወዛግብም፤ የግል - ሚሥጥርና የአገር ሚሥጥር ግን መለየት ይኖርበታል፡፡
ስልክ ወይም ኢሜይል ጠለፋ አዲስ ኃይላዊ ማረጋገጫ (Coerced confession) ነው ይባላል፡፡ አዲስ ሚሥጥር መያዣ ዘዴ ነው፡፡ ዱሮ፤ በጉልበት በማገት የምናደርገውን፤ ዛሬ በሽቦና በኤሌክትሪክ ኃይል ጠለፋ ላይ መፈፀም ማለት ነው፡፡ ይሄ እንግዲህ “ተመርማሪውን ከማስገደድ፣ ቢያስፈልግም በቶርቸት (በወፌ-ላላ)፤ ከማወጣጣት ዶክመንቶቹን ከመውረስ፣ የግል መረጃዎችን ከመውሰድ፣ ቤቱን ሰብሮ ከመግባት ይልቅ፤ ሌላ ዘዴ መተካት ማለት ነው፡፡ ይሄ በዘመናዊ መንገድ ሲታሰብ፣ የኢ-ሜይል መዛግብት መውረስ ማለት ነው፡፡
ይሄ ደሞ፤ የኤሌክትሮኒክ መገናኛ ዘዴዎችን የፈጠሩት ሰዎች ራሳቸው፤ የማያውቁት ዘዴ የለም ብለን እንመን እንደማለት ነው፡፡
“ፖስታህ ከተከፈተ አለቀልህ፡፡ ገበናህ ተቀደደ፡፡ ፈረሱ ከጋጣው ወጥቷል”
 “ዱሮ ሚሥጥር የቤተ ክህነት ነበር፡፡ ዛሬ ቴክኖሎጂ ወርሶታል፡፡ ነገር ከካህን ወደ ልዑል ካለፈ - ነገር ጠፋ” ይላል - ዘ ኒውዮርከር፡፡ ገዢ የማያቀው ሚሥጥር የለም ነው ቁም ነገሩ፡፡
ከግልጽነት ይልቅ ሚሥጥራዊነትን የሚፈልግ ወገን - ባሁኑ ዘመን ቀልጧል፤ የሚል እሳቤ ቢኖረን ይሻላል፡፡ “ሚሥጥር ከኮተኮታችሁ ሁሉ ነገር ተጀመረ፡፡ ጐበዝ! ሚሥጥራዊነት የሤራ መሣሪያ ናት (ጄሬሚ ቤንታም)” በድብቅነትና በሚሥጥራዊነት መኖር አይቻልም፡፡ ከህዝብ የምትደብቀው ሚሥጥር በተለይ፤ ውሎ አድሮ መሸማቀቂያህ ነው!
ድብቅነት ነገ ከነግ - ወዲያ ይገለጣል፡፡ ሚሥጥራዊነት ግን የጥብቅነቱን ያህል ይቆይ እንጂ የሚታወቅ አደጋ ይሆናል፡፡ ሚሥጥራዊነት ብዙ ሽፋን አለው:- የሉዓላዊነት ሽፋን፣ የመንግሥት ደህንነት ሽፋን፣ የተቋም ህልውና ሽፋን፣ ያለመከሰስ መብት ሽፋን…ምኑ ቅጡ! ዜጋ የግል - ሚሥጥሬ ነው ቢል ግን፤ በብዳቤ፣ በኢ-ሜይል፣ በሞባይል፣ በአካል ሊያስጠይቅህ ይችላል የሚባለው ሚሥጥር የመብቱን መገፈፍ አያመላክትም፡፡
“መንግሥት ዜጐቹን ላለመሰለል መጠንቀቅ ይገባዋል” ይላሉ ፀሐፍት፡፡ “እኛ ብቻ ነን መሪዎች” የሚሉ ህዝቡን እንዲህ ይላሉ:- “ለማመዛዘንና ለመፍረድ አትችሉም፡፡ ደንቆሮ ናችሁና፡፡ ያም ሆኖ፤ ደንቆሮ ሆናችሁ መቀጠል ይኖርባችኋል - ምነው ቢሉ ማመዛዘንና መፍረድ እንዳትችሉ ይፈለጋልና፡፡” ይላል /ቤንታም/፡፡
ፖስታ እየገለጡ ሚሥጥር ስለሚያዩ ፖስታ ቤቶች፣ ዲዝሬኤሊ እንዲህ ይላል፤ “ደብዳቤዬን ክፈቱ ግን መልስ መስጠት ቻሉ!”
ዋናው ጥያቄ ግን በግል - ሚሥጥር (Privacy)፣ በግልጽነት  (Publicity) መካከል ልዩነት እንዳለ ልብ - ማለት ያሻል የሚለው ነው፡፡
ሆኖም እንደ ኤድጋር አላን ፖ - አመለካከት፤ “ሁሉም ድብቅ ነገር (mystery) ነገ ተገላጭ ነው፡፡ ምንም ነገር ተሸሽጐ አይቀርም፡፡ ወንጀሎች መፈታት አለባቸው፡፡ ግርግዳዎች መፍረስ አለባቸው፡፡ መቃብሮች ይፈነቀላሉ፡፡ ፖስታዎችም ተቀደው ይታያሉ” ይላል፡፡
ሙሰኛን፣ ኢፍትሐዊን፣ ሃሳዊ - መሲህን፣ ደካማ - ፖለቲከኛን፣ አድርባይን፣ አሻጥረኛን፣ አስመሳይ ተራማጅን የሚያውቅና የሚከስ፤ በዚህም ሆነ በዚያ ዕውቀቱ ያለው ነው፡፡ “ሰርቆ የሚያውቅ፣ በምልክት ያሰራል” የሚለው የወላይትኛው ተረት ይሄው ነው፡፡   

Read 6528 times