Sunday, 24 November 2013 17:49

የኔትዎርክ መቆራረጥ እንጂ የደንበኞች መቆራረጥ አልገጠመኝም” - ኢትዮ ቴሌኮም

Written by  ኤልያስ
Rate this item
(10 votes)

ኢህአዴግም ያልተሰደደው ሥልጣን ላይ ስለሆነ ነው!
የደከመው ባለስልጣን ማረፍ እንጂ አምባሳደር መሆን የለበትም!

በአሁኑ ጊዜ የቱንም ያህል “ልማታዊ” ለመሆን ቢሞክሩ ፈፅሞ ያልተሳካላቸው የመንግስት ተቋማት ቢኖሩ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሱት የኢትዮጵያ መብራት ኃይል ኮርፖሬሽንና ኢትዮ ቴሌኮም ናቸው፡፡ (ልማታዊ ያልሆነ ሁሉ ኪራይ ሰብሳቢ ነው ማለት ግን አይደለም!) መብራት ሃይል መብራት እምቢ ሲለው፣ ቴሌኮምም ኔትዎርክ (በቴክኖሎጂ ግንኙነትን ማቀላጠፍ) አልሆንልህ ብሎታል (ምኑን ኖሩት ታዲያ?!)
የኢትዮ ቴሌኮም ሃላፊዎች ሰሞኑን ለፓርላማ ቋሚ ኮሚቴ በሰጡት ማብራሪያ፤ የኔትዎርክ መቆራረጥ የሚከሰተው በሃይል መቆራረጥና በኦፕቲክ ፋይበር መቆራረጥ እንደሆነ ገልፀዋል (በመቆራረጥ አለቁ እኮ!) ቴሌኮም እስካሁን የስራ አጋሩ በነበረው መብራት ኃይል ላይ የጣለው እምነት ተሸርሽሮ ማለቁን የሚጠቁም ፍንጭ እንደታየ ምንጮች ተናግረዋል፡፡ በሰሞኑ ማብራሪያው በኤሌክትሪክ ሃይል መቆራረጥ የሚፈጠረውን የኔትዎርክ መቆራረጥ ችግር ለመቅረፍ ጄነሬተር እጠቀማለሁ ብሏል - ቴሌኮም፡፡ (እቺን ለማሰብ ግን ይሄን ሁሉ ጊዜ!) ይሄ ሁሉ የኔትዎርክ መቆራረጥና የኢንተርኔት አገልግሎት መንቀራፈፍ ቢኖርም ግን “የደንበኞቼን ቁጥር 26 ሚሊዮን አድርሻለሁ” ብሎናል - ቴሌኮም፡፡ (“የኔትዎርክ መቆራረጥ የደንበኞች መቆራረጥን አላስከተለብኝም” እያለ ነው!) እኔ ግን … ቴሌኮምን ብሆን አፌን ሞልቼ “ደንበኞቼ” አልልም ነበር፡፡ (አገልግሎት ሳይኖር ደንበኛ?) እናም … ደንበኞቼ ሳይሆን “የክብር ደንበኞቼ” ነበር የምላቸው፡፡ ለምን መሰላችሁ … እኒህ ሁሉ “ደንበኞች” እኮ በኔትዎርክ መቆራረጥ ሳቢያ በሞባይል ስልክ  እየተጠቀሙ አይደለም። (ኮሙኒኬሽን ኖቼ!) ስለዚህ “የክብር ደንበኞች” የሚለው ነው በደንብ የሚገልፀን (እኔም ሞባይል ተጠቃሚ እኮ ነኝ!)” በሌላ አነጋገር … የደንበኝነት ክብር የተሰጣቸው ግን አገልግሎት የማያገኙ እንደ ማለት ነው፡፡ (የክብር አባልነት ወይም የክብር ዶክትሬት በሉት!) አያችሁ … ዝም ብሎ የክብር ነገር ስለሆነ ብዙ የሚያሸልል ነገር የለውም፡፡ (በክብር ደንበኝነት መኩራት የሚሻ መብቱ ነው!) ምናልባት ግን እያንዳንዱ ባለሞባይል ሲቪው ላይ ሊያካትተው ይችላል - “የኢትዮ ቴሌኮም የክብር ደንበኛ ወይም “Honorary Customer of Ethio-Telecom” በማለት፡፡ እናላችሁ … 26 ሚሊዮን ደንበኞች አሉኝ የሚለው 26ሚ. “የክብር ደንበኞች” በሚል መስተካከል አለበት፡፡ (የዶክትሬት ድግሪና የክብር ዶክትሬት ለየቅል ናቸው!)
እግረመንገዴን … የመብራት ሃይል ኮርፖሬሽን ደንበኞችም “የክብር ደንበኞች” መባል እንዳለባቸው ላስታውስ እሻለሁ፡፡ (በጨለማ እያሳደረን “ደንበኞቹ” ልንሆን አንችልም!)
ጉደኛው የመብራት ሃይል ኮርፖሬሽን በቅርቡ በኢቴቪ ያስተላለፈውን ማስታወቂያ ሰምታችሁልኛል? (ብትሰሙማ እስካሁን ስቃችሁም አታባሩ ነበር!) የመብራት ሃይል ማስታወቂያ ምን መሰላችሁ? ከሌሊቱ 6 ሰዓት በኋላ ኃይል ስለሚቋረጥ “የክብር ደንበኞቹን” የቅድምያ ይቅርታ የሚጠይቅ ነው፡፡ (የይቅርታም ቀብድ አለው ለካ?) እናላችሁ … ቁጭ ብለን መብራት እንዳሻው ቦግ እልም ሲል ያልቀረበ ይቅርታ ከተኛን በኋላ ለሚጠፋው ይቅርታ መጠየቁ ግርም ያሰኛል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ አሰራር ግን ለደንበኞች አይሰራም- ምናልባት “ለክብር ደንበኞች” እንጂ፡፡
እኔ የምላችሁ … የአሁኑ ሳይሆን የወደፊቱ የጦቢያ የኃይል ዕጣ ፈንታ ምን እንደሚሆን የሚነግረን “አዋቂ” ጠፋ አይደለ?! (“ኃይል” ስል “ሥልጣን” ማለቴ አይደለም!) ከምሬ ነው … ከኮርፖሬሽኑ ዋና ስራ አስፈፃሚ እስከ አገሪቱ ጠ/ሚኒስትር ድረስ ይሄን ነገር እኮ አያውቁትም (እነሱ ጠንቋይ - አይቀልቡ!) እናላችሁ … በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚታወቁ ፕሮፌሽናል የዕጣ ፈንታ ተንባዮችን (Fortunetellers) በኢንተርኔት ማሰስ ጀምሬያለሁ። ግን ዕድሜ ለቴሌኮም! አሁን ተቋርጧል (ቢሮዬ ኢንተርኔት ከእነ አካቴው ከጠፋ ሁለት ሳምንቱን ሊይዝ ነው!)
የሆኖ ሆኖ ግን ፍለጋዬ ይቀጥላል (“ፍለጋው አያልቅም” አለ ዘፋኙ!) እኔ የምላችሁ … “የምርጥ ከተሞች ፍለጋው” እንዴት እየሄደ ነው? በባህር ዳር እየተከበረ ያለውን “የከተሞች ሳምንት” ማለቴ ነው፡፡ መቼም “Top 10 Cities” በሚል አስሩን የኢትዮጵያ ምርጥ ከተሞች ማወቅ የምንችልበት በዓል እንደሚሆን “ቁርጠኛ እምነት” አለኝ፡፡ በነገራችሁ ላይ እኔ “የከተሞች ሳምንት” መክፈቻ በዓልን የተመለከትኩት በኢቴቪ ነበር - ከባልንጀራዬ ጋር፡፡ እናላችሁ … ባልንጀራዬ አክሮባት ሲሰሩ የነበሩ የባህርዳር ታዳጊዎችን አይቶ “የደርግን 10ኛ ዓመት የአብዮት በዓል አስመሰሉት እኮ!” አይል መሰላችሁ! (እኔ ደሞ ክው አልኩላችኋ!) እናም እንዲህ አልኩት “አይሁን እንጂ መምሰሉ ችግር የለውም!” (ደንግጬ እኮ ነው!)  የይምሰል ፈገግታ አሳየኝና የጨዋታ ርዕሰ ጉዳዩን ቀየረ - ባልንጀራዬ፡፡ የዚያኑ ዕለት አንድ የመንግስት ከፍተኛ ሃላፊ ስለ ከተሞች ቀን በእንግሊዝኛ አጭር “ማብራሪያ” ሰጥተው ነበር (ማብራሪያው ሌላ ማብራሪያ ይፈልጋል!) እናም ባልንጀሬ ገብቶት እንደሆነ ስጠይቀው ምን አለኝ መሰላችሁ? “ተሸውደሃል እንግሊዝኛ የተናገሩ መስሎህ ነው?” አለኝ እየሳቀብኝ፡፡ በጣም ተናድጄ “እና ምንድነው ታዲያ?” አልኩት፡፡ “እኔ ምን አውቃለሁ” ብሎ እንደገና ሳቀብኝ፡፡ እኔ ግን ይሄው እስከዛሬ የተናገሩትን የሚፈታልኝ አላገኘሁም፡፡ (ፍለጋው ግን አያልቅም!)
እናንተ … በሳኡዲ ያሉ ዜጐቻችን ላይ የተፈፀመው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት በጣም ያሳዝናል አይደል? (ሳኡዲ እንዲህ ሲኦል ናት እንዴ?) ወገኖቻችን ከደህና አገራቸው ወጥተው መከራቸውን በሉ እኮ!! (ገንዘብ አጣን እንጂ አገር እኮ አለን!) “ገንዘብ የለም እንጂ ገንዘብ ቢኖርማ … ወይ አገር ወይ አገር ወይ አገር ጦቢያ” … ለማለት ዳድቶኝ ነበር። በነገራችሁ ላይ እስካሁን ወደ 12ሺ ገደማ ስደተኛ ኢትዮጵያውያን ወደ አገራቸው ተመልሰዋል፡፡ መረጃው የውጭ ጉዳይ ሚ/ር ነው (ቃል በቃል የተቀዳ!) የመ/ቤቱ ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ፤ “አሁን የዜጐቻችንን ደህንነት ለመታደግ ሙሉ ትኩረታችንን ስደተኞችን ወደ አገራቸው በመመለስ ተግባር ላይ አድርገናል። የደረሰባቸውን በደልና ጉዳት በተመለከተ ዜጐች ከተመለሱ በኋላ የምናጣራው ይሆናል” ነው ያሉት ሰሞኑን በሰጡት መግለጫ፡፡ እኔም በዚህ እስማማለሁ (ባልስማማም ለውጥ አላመጣማ!) እንዲያም ሆኖ ግን አንዳንድ ወሳኝ ጥያቄዎችን መሰንዘራችን አይቀርም (ኢህአዴግ የታገለለት ህገመንግስታዊ መብታችን ነዋ!) እናም ጥያቄያችን … “ይሄ ሁሉ ቀውጢ (Chaos) እስኪፈጠር በሳኡዲ የሚገኘው ኤምባሲያችን የማንን ጐፈሬ ሲያበጥር ነበር?” የሚል ነው፡፡ ችግሩ ከመከሰቱ በፊትስ መከላከል አይቻልም ነበር? (የማይቻል ነገር የለም አቦ!) “ከልብ ካለቀሱ …” ነው ነገሩ፡፡  
ከጥቂት ወራት በፊት እዚሁ ጋዜጣ ላይ በወጣ ዘገባ፤ በሳኡዲ የሚገኙ ህገወጥ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች፤ ህጋዊ ለመሆን የሚያስችላቸውን ፈቃድ ለማግኘት እዚያ የሚገኘውን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ፓስፖርት ቢጠይቁም ሊሰጣቸው ባለመቻሉ የሳኡዲ መንግስት ያስቀመጠው ቀነ ገደብ እየደረሰ መሆኑን ገልፀው ነበር (እንደ አቤቱታ!) ኤምባሲው ምላሽ ሲሰጥ ምን አለ? “ከአገር ቤት ፖስፖርት ታትሞ አልመጣልኝም!” (“የሚያጠግብ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል” አሉ!) ኤምባሲው ለታላቁ ህዳሴ ግድብ ገንዘብ ካላዋጣችሁ ፓስፖርት አናድስም እንዳላቸው የገለፁ ስደተኞች እንደነበሩም አይዘነጋም፡፡ እንደውም አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ይሄን በተመለከተ ተጠይቀው ሲመልሱ፤ በግዳጅ ገንዘብ አዋጡ የሚለው አሰራር ህገ ወጥ እንደሆነ መግለፃቸው ይታወሳል፡፡ በእነዚህ ሁሉ ችግሮች ተከበው ነው የሳኡዲ መንግስት ህገወጥ ስደተኞች ህጋዊ እንዲሆኑ የሰጠው የጊዜ ገደብ (የይቅርታ ጊዜ) የተጠናቀቀው፡፡ እናም ዜጐቻችን ለሞት፣ ለእስር፣ ለድብደባና ለዘረፋ የተጋለጡት፡፡ ሙሉ በሙሉ ተጠያቂው ኤምባሲው ነው ለማለት ተጨማሪ መረጃና ጥናት ያስፈልጋል፤ ሆኖም መጠየቁ ግን አይቀርም (ሃላፊነት አለበታ!) እርግጥ ነው እያንዳንዱ ስደተኛ ወዶ ለገባበት ምርጫ ተጠያቂ እንደሚሆን የታወቀ ነው፡፡ ግን ደግሞ የተሰደዱት ከድህነት ለማምለጥ መሆኑም ሊጤን ይገባል (ራሱ ኢህአዴግ ድህነትን ተረት አደርጋለሁ ይል የለ!) ለነገሩ ራሱ ኢህአዴግም ያልተሰደደው እኮ ሥልጣን ላይ ስለሆነ ነው!
እኔ የምለው ግን … በየአገሩ ያሉ ዲፕሎማቶቻችን ለወገኖቻቸው የሚቆረቆሩ ይመስላችኋል? (ነገር መጠምዘዝ አያስፈልግም!) ለመሆኑ ኢህአዴግ አምባሳደሮችን ሲሾም በምን መስፈርት ነው? (የፖለቲካ ታማኝነቱ እንደተጠበቀ ሆኖ ማለቴ ነው!) አንዳንድ ሃሜቶች ግን ይናፈሳሉ… የአምባሳደርነት ሹመት ለኢህአዴግ አባላት እንደ እረፍት የሚቆጠር ነው የሚሉ፡፡ ከረዥም አመት የመንግስት ሃላፊነት (አገልግሎት) በኋላ የሚታደል እንደማለት፡፡ እናም ሃሜቱ ድንገት እውነት ከሆነ ደግሞ … በአምባሳደርነት የሚሾሙት የደከማቸው ባለስልጣናት ናቸው ማለት ነው (የመተካካት ተረኞች!) መቼም ለምን ደከማቸው አይባልም አይደል? እንዴ 17 ዓመት በትግል ሜዳ፣ ከ20 ዓመት በላይ ደግሞ በልማት ሜዳ “የፈጉ” እኮ ናቸው፡፡ እናም በስደት ላይ የሚገኙ ዜጐቻቸው ጉዳይ ብዙም ባያሳስባቸው አይፈረድባቸውም፡፡ ጥፋተኛው ግን ሿሚው ነው (ራሱ ኢህአዴግ!)
በነገራችሁ ላይ … በመላው ዓለም ያሉ የጦቢያ ልጆች በሳኡዲ የተፈፀመውን ኢ-ሰብዓዊ ድርጊቶች በሰልፍ መቃወማቸው ያኮራል፡፡ በአዲስ አበባ የተሞከረው ተቃውሞ መክሸፉ ደግሞ ቅር ያሰኛል። አንዳንድ ለተቃውሞ የወጡ ሰልፈኞች “ለዚህ ለዚህማ ሳኡዲ ይሻላል!” እንዳሉም ሰምተናል። ፖሊስ በበኩሉ፤ የሳኡዲን ኤምባሲ ሰብረው እንዳይገቡ ያደረግሁት ጥንቃቄ ነው ብሏል (ያለ ዱላ መጠንቀቅ አይቻልም ነበር) ደሞም እኮ ተመሳሳይ ተቃውሞ በተደረጉባቸው የዓለም አገራት ሁሉ የሳኡዲ ኤምባሲዎች አሉ፡፡ እዚያም ተቃውሞው ተካሂዷል፤ ሰልፈኞችም ኤምባሲ ሰብረው አልገቡም፡፡ (መንግስታችን “ኢትዮጵያዊ ጨዋነታችንን” ዘነጋው ልበል?!) ለማንኛውም ግን ህገ መንግስታዊ መብታችን እንደ ቴሌኮም ኔትዎርክ ባይቆራረጥ ይመከራል፡፡ (ይመረጣልም!) ያለዚያ ግን እኛም ለኢህአዴግ “የክብር ህዝቦች” መባላችን አይቀርም - እንደ ቴሌኮም “የክብር ደንበኞች!” አንዳንድ የኢህአዴግ ካድሬዎች “ብትሆኑ ምን ችግር አለው?” ይሉ ይሆናል፡፡ ግን ከባድ ችግር አለው፡፡ (“አደጋ አለው” አሉ!) ለምን መሰላችሁ? “የክብር ህዝቦች” ግብር አይከፍሉማ! ያለ ግብር ደግሞ ኢህአዴግ አንዲትም ቀን አያድርም፡፡ (ያለ ግብር የኖረ መንግስት የለማ!)

Read 3515 times