Print this page
Saturday, 02 November 2013 11:36

ሕዝባዊ መሰረት ያለው ፓርቲ ህዝቡን አይሰልልም!

Written by  ኤልያስ
Rate this item
(11 votes)

አሜሪካ ያልሰለለችው “እግዚአብሔርን” ብቻ ነው!
የመብራት መጥፋት ዋናው ችግር የ”ጠባቂነት” ባህል ነው!
የኤሌክትሪክ ኃይል በየግቢያችን ልናመነጭ ነው!

እውነቱን ልንገራችሁ አይደል----ያሳለፍነው ሳምንት የአግራሞት ነው፡፡ የአሜሪካንን የስልክ ጠለፋና የስለላ ጦስ ሰማችሁልኝ አይደል? እንዴ --- አንድዬን ብቻ እኮ ነው ያልሰለለችው! (የሚጠለፍ ስልክ የለማ!) እኔማ ምን እንደመሰለኝ ታውቃላችሁ? በቃ -- በልጅነቴ እሰማው የነበረው 8ኛው ሺ የገባ ነው የመሰለኝ፡፡ እስቲ አስቡት---የጀርመኗ ቻንስለር አንጌላ መርከል፤ለአስር ዓመት ስልካቸው እየተጠለፈ ተሰልለዋል፡፡ እሺ--- መሪዎቹስ እርስ በእርስ ይተዋወቁ ይሆናል፡፡ 30 ሚሊዮን የፈረንሳይ ዜጎች፣ 60 ሚሊዮን የስፔይን ዜጎች ስልካቸው ተጠልፎ መክረሙ ምን ይባላል? ግን አሜሪካ ከስልክ ጠለፋ ውጭ ሥራ የላትም ማለት ነው ? አንድ ነገር ግን ፈርቻለሁ፡፡ ይሄ የፀረ-ሽብርተኝነት ዘመቻ ዓለምን አካክዶ መተማመን ታሪክ ሆኖ እንዳይቀር! አሁን አንጌላ መርከል ዳግም ለአሜሪካ ልባቸውን የሚሰጡ ይመስላችኋል? (10 ዓመት እኮ ነው የተሰለሉት!) ወይ አሜሪካ---ሽብርተኝነትን እዋጋለሁ ብላ ዓለሙን ሁሉ በሽብር ሞላችው! (እሾህን በእሾህ አሉ !)
ከሁሉም የገረመኝ ደግሞ ኦባማ ስለስልክ ጠለፋው ምንም የማውቀው የለም አሉ መባሉ ነው፡፡ እኔ የምለው ግን ----- ምነው ቻይና ድምጿ ጠፋ? (መንገድ ብቻ ነው የምጠልፈው ለማለት ነው?) “ኃያል መንግስትን ማመን ቀብሮ ነው” አለች- ጀርመን! እንዴ--- እዚህም አገር እኮ ኢህአዴግ የተቃዋሚዎችን ስልክ ይጠልፋል ተብሎ እንደጉድ ተወርቶ ነበር፡፡ እሱ እንኳን ያምርበታል። የጀመረውን ልማት ሳይጨርስ በጎዳና ላይ ነውጥ ከሥልጣን ሊያወርዱኝ ይፈልጋሉ ብሎ የጠረጠራቸውን ይሆናል የጠለፈው፡፡ (ይሆናል እኮ ነው!) ቢያንስ ቢያንስ ኢህአዴግ እንደ አሜሪካ--- የ60 ሚሊዮን ህዝብ ስልክ ይጠልፋል ብዬ አላስብም (ቴክኖሎጂውም እኮ መከራ ነው!) “የአሜሪካ ሬዲዮ ድምፅንም “ጃም” ያስደረገው በቻይና ድጋፍ ነው” የሚሉት ምቀኞች ሳይሆኑ አይቀሩም፡፡ ለነገሩ ህዝባዊ መሰረት ያለው ፓርቲ እኮ ህዝቡን አይሰልልም! (በጆሮ ጠቢና በካድሬ አልወጣኝም!) ሞባይልና ኢሜይላችንን በመጥለፍ ማለቴ ነው! ቢሰልልስ ከእኛ ምን ያገኛል? ኢህአዴግ የማያውቀው ኑሮ ከየት እናመጣለን፡፡ እሱ ሰፍሮ የሰጠንን እኮ ነው የምንኖረው፡፡ (የህዝቡን ገበና የሚያውቅ ፓርቲ አይሰልልም!)
አሁን ከስለላ ወደ ኢቴቪ ልውሰዳችሁ፡፡ እውነቱን ልንገራችሁ አይደል --- ምን ቢያበግነኝ ኢቴቪን ጠልቼ አልጠላውም፡፡ (ምርጫ የለኝማ!) ማታ ማታ ኤልፓ ካልጠመመብኝ በቀር --- ብቸኝነቴን የሚያረሳሳኝ ኢቴቪ እኮ ነው፡፡ እኔ የምለው… ኢቴቪ ከዜናና ከፕሮፓጋንዳ በስተቀር ሌሎቹን ፕሮግራሞች በሙሉ ለ”ልማታዊ” ባለሃብቱ ሊቸበችበው ነው የሚባለው እውነት ነው እንዴ? (ኢህአዴግ “ልብ ገዛ” በሉኛ!) ትንሽ ፍራቻ ግን አለኝ! “የቴሌቪዥን ጣቢያውን ኒዮሊበራሊስቶች በእጅ አዙር ቢቆጣጠሩትስ?” የሚል፡፡ (መሠረተ ቢስ ፍራቻ ከሆነ እታረማለሁ!)
ባለፈው ማክሰኞ ማታ በኢቴቪ ያየሁትን አስገራሚ ነገር ልንገራችሁ፡፡ (ሳምንቱ የአግራሞት ነው ብዬ የለ!) ኢቴቪ ፊት ለፊት ጉብ ብዬ የለመድኩትን በፕሮፓጋንዳ ቅቤ የታሸ ዜና እኮመኩማለሁ፡፡ (“እንደምን አመሻችሁ ዲሽ የሌላችሁ?” አልቀረም እንዴ?) ልክ ዜናው ሲጠናቀቅ የአየር ትንበያ መጣ፡፡ የነገውን የአየር ትንበያ ለመስማት አሰፍስፌ ሳለ የትንበያ ማረምያ ሰማሁ -“ትላንት ያቀረብነው የአየር ትንበያ ስህተት ስለሆነ ይቅርታ እንጠይቃለን!” የሚል፡፡ ይሄ ለትያትር ግብአት እንጂ ለReal life አይመችም፡፡ ነገርዬውን የበለጠ ኮሚክ ያደረገው ደግሞ ምን መሰላችሁ? ከይቅርታው በኋላ “አሁን ወደ እለቱ የአየር ትንበያ እናልፋለን” መባሉ ነው፡፡ ለነገሩ አብዛኞቻችን ከቤት የምንወጣው ሰማዩን አንጋጠን አይተን እንጂ የአየር ትንበያን ሰምተን አይደለም፡፡
አንዱ የሸገር ሰው ነው አሉ፡፡ የነገውን የአየር ሁኔታ ለማወቅ ይፈልግና ወደ አየር ትንበያ ቢሮ ስልክ ይመታል “ጌታዬ… የነገውን የአየር ትንበያ ለማወቅ ፈልጌ ነበር… ሊነግሩኝ ይችላሉ?”
ስልኩን ያነሳው የአየር ትንበያ ባለሙያም፤ “የነገውን ነው የፈለከው አይደል?” መልሶ ጠየቀው።
“በትክክል ጌታዬ!” ይላል ፤ትሁቱ የአየር ትንበያ ጠያቂ፡፡
“ወይ ይዘንባል ወይ አይዘንብም!” ብሎት እርፍ አለ፤ የአየር ትንበያ ቢሮው ሠራተኛ፡፡ (ሳይንስ ቀለጠች አትሉም!)
እኔ የምላችሁ… ባለፈው ቅዳሜ የመቀሌው “አሽጎዳ የነፋስ ኃይል” ሲመረቅ ተመልክታችኋል? (በኢቴቪ Live ነበር እኮ!) እኔን ግን ከነፋስ ኃይሉም የበለጠ ያስደመመኝ ምን መሰላችሁ? የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ምህረት ደበበ የተናገሩት፡፡ “የዓመቱ ተጠቃሽ ንግግር” ልትሉት ትችላላችሁ፡፡
“ይሄን ያህል ምን ቢናገሩ ነው?” ብላችሁ ይሆናል፡፡ (የመብራት መቆራረጥና መጥፋት ችግር ቁርጥ ምላሽ ያገኘበት ታሪካዊ ንግግር ነበር!) እናላችሁ… ዋና ሥራ አስፈፃሚው፤ ተደጋጋሚ እሮሮና አቤቱታ የበዛበትን የመብራት መቆራረጥና መጥፋት በተመለከተ እንዲህ አሉ -“ችግሩ የኃይል አቅርቦት አይደለም፤ የ“ጠባቂነት” ባህል ነው” (“እቺ ናት አገርህ” የምትለዋ ግጥም ትዝ አለችኝ) ለካስ እስከዛሬ “የመልካም አስተዳደር ችግር ነው”፣ “የሴረኞች ደባ (Sabotage) ነው” ወዘተ… የተባለው ሁሉ ቀብድ ነው - ሃቋን እስክንሰማ! ይኼው ሥራ አስፈፃሚው እግዜር ይስጣቸውና በእለተ ቅዳሜ ከመቀሌ ምድር ”የመንግስት መብራት ጠባቂ” መሆን እንደሌለብን በማይጎረብጥ አንደበታቸው እቅጯን ነገሩን፡፡ (ደፋር አይጥፋ!)
አንዳንዴ የኢህአዴግ ሹማምንት “ወጣቶች የመንግሥት ሥራ ጠባቂ መሆን የለባቸውም!” ሲሉ ሰምታችሁ አታውቁም? ሥራ አስፈፃሚውም እንደዚያ ነው ያሉን፡፡ “የመንግስት መብራት አትጠብቁ!” እቅጩን መናገራቸው ቢያስደስተኝም ትንሽ ቅር ያለኝ ነገር አለ፡፡ “ከመብራት ጠባቂነት” እንዴት እንደምንላቀቅ ትንሽ ፍንጭ እንኳን አልሰጡንም፡፡ በጀነሬተር ይሁን በነፋስ ኃይል አሊያም በፀሃይ ብርሃን ወይም በእንፋሎት ወይም በባዮጋዝ-- አልነገሩንም፡፡ (“ፍንጭ ጠባቂ” ሆንኩባችሁ?)
የሆኖ ሆኖ ግን ጠባቂ መሆን የለባችሁም ተብለናል፡፡ እናም---በየአካባቢያችን በጥቃቅንና አነስተኛ ተደራጅተን ---- ወንዞችና ኩሬዎችን እየፈለግን ሃይል ማመንጨት አለብን! ወንዝና ኩሬ የሌለበት ሰፈር ሲሆን ደግሞ የነፋስ ኃይል ማመንጨት ነው (የግድ እኮ የአባይ ዓይነት ግድብ አያስፈልገንም!)
አንድ ቀን ደግሞ የኢትዮ-ቴሌኮም ኃላፊ ተነስተው “ህብረተሰቡ የመንግሥት ኔትዎርክ ጠባቂ መሆን የለበትም” ማለታቸው አይቀርም፡፡ እናም --- እንደምንም ከ“ኔትዎርክ ጠባቂነት” መላቀቅ አለብን ባይ ነኝ! (አሁንማ እስኪነገረን አንጠብቅም!)
ከጥቂት ሳምንት በፊት የዳቦ ዘር ጠፍቶ አዳሜ መንግስት መንግስትን ሲያይ ነበር፡፡ ሰሞኑን ስንዴ በሽበሽ መሆኑን ጠ/ሚኒስትሩ በኢቴቪ ሲናገሩ ሰማሁ፡፡ የትጉህ ገበሬዎችን ማሳ የጎበኙት ጠ/ሚኒስትሩ፤ በድል አድራጊነት ስሜት ተጥለቅልቀው “ስንዴ የምንሸጥበት የውጭ ገበያ እናፈላልጋለን” ብለዋል፡፡ (“በቆሎም ኤክስፖርት እናደርጋለን ተብሎ ነበር” እንዳትሉኝ!) በነገራችን ላይ ስንዴ ለውጭ ገበያ እናቀርባለን ማለት እኮ አገሩ በዳቦ ይጠግባል ማለት አይደለም፡፡ እናላችሁ---የስንዴ እጥረት ተፈጥሮ “የመንግስት ስንዴ ጠባቂ አትሁኑ!” የሚል ተግሳፅ ሳይደርሰን በፊት በየጓሮአችን የአቅማችንን ያህል ስንዴ የመዝራት ባህል ማዳበር አለብን ባይ ነኝ፡፡
አያችሁ… ለአንዳንድ ነገሮች ከወዲሁ ቅድመ ዝግጅት ማድረግ ሳያስፈልገን አይቀርም፡፡ በአንድ ወቅት እንደተከሰተው አይነት የዘይት እጥረት ቢፈጠር ምን ይውጠናል? መንግስት እንደሆነ እንኳንስ ዘይት መብራትም ቢሆን እራሳችሁ አምርቱ እንጂ እኔን ጠባቂ መሆን የለባችሁም ብሎ ተፈጥሟል፡፡ እናም… መፍትሄው ምን መሰላችሁ? አሁኑኑ በየቤታችን ዘይት መጭመቅና ማምረት መጀመር አለብን፡፡ የ“መንግስት ዘይት ጠባቂ” መሆን እኮ አይፈቀድም፡፡ በነገራችሁ ላይ --- ሰሞኑን ሸንኮራ አገዳ ጓሮዬ ለመትከል አስቤአለሁ። የራሴን ስኳር የማምረት እቅድ አለኝ፡፡ “የመንግስት ስኳር ጠባቂ” ላለመሆን!
እውነቱን ልንገራችሁ አይደል --- የመብራት ኃይል ኮርፖሬሽኑ ሃላፊ ባለፈው ቅዳሜ የነገሩንን ነገር ትንሽ ቀደም ቢያደርጉልን ኖሮ፣ እስካሁን የምንም ነገር “ጠባቂ” አንሆንም ነበር፡፡ ነጋ ጠባ በትራንስፖርት ችግር ከመማረር ይልቅ የራሳችንን የትራንስፖርት አማራጭም እንፈጥር ነበር። ግዴለም አሁንም ቢሆን… የታክሲው እጥረት አልተፈታምና በየእድራችን፣ ማህበራችን ወዘተ እንምከርበት፡፡ አንድ ቀን የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ “ችግሩ የህዝቡ ታክሲ ጠባቂ መሆን ነው!” ማለቱ አይቀርማ፡፡ ይሄውላችሁ---ከበረታን ምንም የማንፈታው ችግር የለም፡፡ ትንሽ የሚያስቸግረን ምን መሰላችሁ? የውጭ ምንዛሪ እጥረት ነው፡፡ (ዶላር እንደ ስንዴ ጓሮ አይመረትም!) በነገራችሁ ላይ --- በየአካባቢያችን የየራሳችንን የአየር ትንበያ መጀመር እንዳለብንም አንድ ወዳጄ ሹክ ብሎኛል። ለምን መሰላችሁ? “የመንግስት የአየር ትንበያ ጠባቂ” ላለመሆን ነው፡፡ እንደሰሞኑ የትንበያ ስህተት ሲፈጠርም ጣታችንን መንግስት ላይ ከመቀሰር ይገላግለናል፡፡
እግረ መንገዴን ---- ተቃዋሚዎችም እንደኛ በሁለት እግራቸው መቆም ይለምዱ ዘንድ እመክራቸዋለሁ (ነፃ ምክር እኮ ነው!) አያችሁ---የፖለቲካው ምህዳር ጠቧል፣ዲሞክራሲው ቀጭጯል፣ህገመንግስታዊ መብቶች እየተደፈጠጡ ነው፣ኢህአዴግ ሥልጣን የሙጥኝ ብሏል ወዘተ---የሚሉ ብሶቶች የሚተረጎሙት እንደጠባቂነት ነው፡፡ እናም አንድ ቀን ኢህአዴግ “የተቃዋሚዎች ችግር የጠባቂነት ነው” ማለቱ አይቀርም፡፡ እስቲ አሁን እንኳ ወግ ደርሷቸው ይቅደሙት! በነገራችሁ ላይ ---- ዜጎች (እኛ) ከመንግስት ጠባቂነታችን ሙሉ በሙሉ ስንላቀቅ ከመንግስት ጋር ያለንም ውል ይፈርሳል፡፡ መንግስት ላያስፈልገን ሁሉ ይችላል፡፡ (መብራት ከራሳችን፣ ስንዴ ከጓሮአችን፣ ኔትዎርክ በብልሃታችን፣ሰላምና ፀጥታ በማህበረሰብ ፖሊሳችን---)

Read 3240 times